1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሃያኛዉ አመት የጀርምን ዉሕደት በዓል በብሬመን

እሑድ፣ መስከረም 23 2003

በስነ-ስርዓቱ ላይ የአገሪቱ ፕሬዚደንት ክሪስቲያን ቩልፍና መራሄ-መንግሥት ቻንስለር አንጌላ ሜርክልም ሲገኙ ሁለቱ ባለሥልጣናት ቀደም ሲል ለክብረ-በዓሉ በተዘጋጀው በከተማቱ የወርቅ መዝገብ ላይ ፊርማቸውን አስፍረው ነበር---ዕለቱ ጀርመን በአንደኛው የዓለም ጦርነት በአሽናፊዎቹ መንግሥታት የተጣለባትን ካሣ ክፍያ በይፋ ያጠናቀቀችበት ቀንም ነው።

https://p.dw.com/p/PTBv
ድግሱ በብሬመንምስል picture-alliance/dpa

ጀርመናውያን ከአራት አሠርተ-ዓመታት ክፍፍል በኋላ መልሰው የተዋሃዱበት ሃያኛ ዓመት መታሰቢያ ዕለት አከባበር ሰሜናዊቱ ወደብ ከተማ ብሬመን ውስጥ በተካሄደ መንፈሣዊ ስነ-ስርዓት ዛሬ ማለዳ ላይ ተከፍቷል። የኦስናብሩክ ከተማ ሊቀ-ጳጳስ ፍራንስ-ዮዜፍ-ቦደ ከሺህ በሚበልጡ ተጋባዥ እንግዶች ፊት ባደረጉት ስበካ ባለፉት ሃያ ዓመታት የአንድነት ሂደት ውስጥ ታላቅ ዕርምጃ ቢደረግም ሁሉም ነገር የተሳካ እንዳልነበርም በመጥቀስ ትችት አዘል አስተያየት ሰንዝረዋል። በስነ-ስርዓቱ ላይ የአገሪቱ ፕሬዚደንት ክሪስቲያን ቩልፍና መራሄ-መንግሥት ቻንስለር አንጌላ ሜርክልም ሲገኙ ሁለቱ ባለሥልጣናት ቀደም ሲል ለክብረ-በዓሉ በተዘጋጀው በከተማቱ የወርቅ መዝገብ ላይ ፊርማቸውን አስፍረው ነበር። ዛሬ ከቀትር ጀምሮ ሃያኛው ዓመት የውሕደት ቀን በይፋ የሚከበር ሲሆን ፕሬዚደንት ክርስቲያን ቩልፍ ንግግር ያሰማሉ። በዓሉ የሚከበረው ከፍተኛ የጸጥታ ቁጥጥር በሰፈነበት ሁኔታ ነው። በዓሉን ምክንያት በማድረግ የደስታ መግለጫ መልዕክት ካስተላለፉት የመንግሥታት መሪዎች መካከል የሩሢያና የአሜሪካ ፕሬዚደንቶችም ይገኙበታል። የሩሢያው ፕሬዚደንት በዚሁ መልዕክት አገራቸው ለጀርመን ውሕደት ለአውሮፓ አንድነት ያደረገችውን አስተዋጽኦ ከፍ ሲያደርጉ ባራክ ኦባማ ደግሞ የጀርመን ክፍፍል በሰላም ማብቃቱንና የበርሊኑን ግንብ መገርሰስ ታሪካዊ ብለውታል።

በጀርመን የዛሬው ሰንበት ከውሕደቱ ሃያኛ ዓመት በዓል ባሻገር ሌላም ታላቅ ትርጉም የተሰጠው ሆኖ ውሏል። ዕለቱ ጀርመን በአንደኛው የዓለም ጦርነት በአሽናፊዎቹ መንግሥታት የተጣለባትን ካሣ ክፍያ በይፋ ያጠናቀቀችበት ቀንም ነው። ጀርመን የጦር ካሣ እንድትከፍል የተወሰነው በጦርነቱ ፍጻሜ በ 1918 ዓ.ም. ፈረንሣይ፤ ቨርሣይ ላይ በተደረገ ውል እንደነበር ይታወሣል። ውሉን ተከትሎ በ 1953 የሰፈነ ስምምነት ደግሞ ጀርመን መልሳ ከተዋሃደች ወለድም ጭምር መክፈል እንዳለባት መደንገጉ አይዘነጋም። ይሄው ወለድ አገሪቱ የዛሬ ሃያ ዓመት በተዋሃደችበት ወቅት 240 ሚሊዮን ዶቼ ማርክ ይጠጋ ነበር። ፌደራል ሬፑብሊክ ጀርመን የሁለተኛ ዓለም ጦርነት ካሣዋንም በውሕደቱ ዋዜማ በ 1988 ከፍላ ማጠናቀቋ ይታወሣል።