1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሌሶቶ፤ የመንግሥት ግልበጣ

ቅዳሜ፣ ነሐሴ 24 2006

በደቡብ አፍሪቃ ንዑስ ግዛት በሌሴቶ ንጉሳዊ አስተዳደር ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት መፈፀሙ ተዘገበ። መፈንቅለ-መንግሥቱን ተከትሎ የሌሶቶ ጠቅላይ ሚንስትር ለሕይወታቸው በመስጋት ሀገር ለቀዉ መዉጣታቸዉም ተዘግቦአል።

https://p.dw.com/p/1D49J
ምስል picture-alliance/dpa

የሌሶቶን መፈንቅለ-መንግስት ተከትሎ ጠቅላይ ሚንስትር ቶም ታባኔ ለሕይወታቸው በመስጋት ወደ ጎረቤት ደቡብ አፍሪቃ መሰደዳቸዉን አዣንስ ፍሯንስ ፕሬስ ዘግቧል። የሀገሪቱ ወታደራዊ ኃይል መፈንቅለ-መንግሥት አልተፈፀመም ሲል አስተባብሏል። ሆኖም የተለያዩ የብዙኃን መገናኛዎች ወታደራዊዉ ኃይል የሀገሪቱን ማዕከላዊ የመንግሥት መስርያ ቤትን እንዲሁም ሁለት የፖሊስ ጣቢያዎችን መቆጣጠሩን ዘግበዋል። የንዑሷ ሌሶቶ ጠቅላይ ሚንስትር ከ BBC ባደረጉት ቃለ-መጠይቅ ከስልጣኔ የተወገድኩት በህዝቡ ሳይሆን ሕገ-ወጥ በሆነ መንገድ በጦር ኃይሉ ነው ሲሉ አማረዋል። ጠቅላይ ሚንስትሩ አያይዘውም ወደ ደቡብ አፍሪቃ የመጡት ለሕይወታቸው ሰግተው መሆኑን፣ ለመገደል ወደ ሌሶቶ እንደማይሄዱ ሆኖም ሕይወታቸው ላይ ያጠላው ስጋት ሲገፈፍ ወደ ሌሶቶ እንደሚያቀኑ በቃለ-መጠይቁ ጠቅሰዋል።

ደ.አፍሪቃ መሀል እንደደሴት የሰፈረችው ንዑሷ ሌሶቶ
ደ.አፍሪቃ መሀል እንደደሴት የሰፈረችው ንዑሷ ሌሶቶ

ቀደም ሲል የግዛቲቱ የስፖርት ሚኒስትር እንደተናገሩት፤ በአካባቢዉ የስልክ መስመሮችና የራድዮ ሞገዶች ሁሉ ተቋርጠዋል። ወታደራዊ ኃይሉ የፖሊስ ጠቅላይ ዕዙን እንደተቆጣጠረ፤ በመዲና ማሴሩ የተኩስ ሩምታ እንደተሰማ፣ ከባድ የጦር መሣሪያ ያነገቡ ታጣቂዎችም በጎዳና ላይ እንደታዩ ተጠቅሷል። በሌሴቶ የፖለቲካ ዉጥረት እና ያለመረጋገት ለዓመታት ስር መስደዱ ተመልክቶአል። ጦሩ የሀገሪቱን የፖሊስ ሠራዊት ትጥቅ ለማስፈታት ዘመቻ በከፈተበት ወቅት ፖሊስ የማዘዣ ዕዙን ጥሎ መውጣቱም ተዘግቧል። ሌሶቶ ደቡብ አፍሪቃ መሀከል እንደ ደሴት ተዘርግታ የምትገኝ ንዑስ ሀገር ናት። በጨርቃ ጨርቅ ምርትና በአልማዝ መዓድን ምርት ገቢ የምትተዳደረዉ ሌሴቶ ወደ ሁለት ሚሊዮን የሚሆን ህዝቧ በድኅነት ዉስጥ ይገኛል።

ማንተጋፍቶት ስለሺ

አዜብ ታደሰ