መልካም አስተዳደር በኢትዮጵያ
ሐሙስ፣ መጋቢት 1 2008
ስማቸዉ እንዲጠቀስ ያልፈለጉ ግለሰብ በሰጡት አስተያየት የመልካም አስተዳደር ችግር ላለፉት 25 ዓመታት የነበረ ነዉ፤ አሁን በአማራና በኦሮሚያ ክልል የተፈጠሩት ችግሮች የሰብዓዊ መብት ጥያቄዎች ናቸዉ ሲሉ ተናግረዋል። እንደ እሳቸዉ ገለፃ ህዝቡን ሊመራ የሚችል እዉቀት ያለዉ አመራር የለም፣ የሚፈለገዉ ታማኝነት ብቻ እንጂ አቅምና እዉቀቱ እንዳልሆነ ተናግረዋል።
ያሬድ ሲራክ የተባለ አንድ አስተያየት ሰጭ በበኩሉ በክልሎቹ የተፈጠሩት ያለመረጋጋቶች የመልካም አስተዳደር ችግሮች ናቸዉ ብሎ መወሰን ብቻ በቂ እንዳልሆነ ተናግሮአል።
በአማራ ክልል የቅማንት ብሔረሰብ ማንነት ጥያቄን በተመለከተም ጠቅላይ ሚንስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ጉዳዩ በሕገ መንግስቱ በግልፅ ምላሽ ያገኘ ነው ሲሉ አብራርተዋል። ይሁን እንጂ አስተያየት ሰጭዉ ያሬድ ሲራክ ሕገ መንግስቱ ምላሽ አልሰጠም ባይነዉ። ምክንያቱ ደግሞ ኅብረተሰቡ የሚነሱት የማንነት ጥያቄዎች በመንግስት ታምቀዉ የቆዩ ናቸዉ ሲል ያሬድ ይናገራል።
በዚህ ጉዳይ በዶይቼ ቬሌ ደረ ገፅ ላይ በተደረገዉ ዉይይት አብዛኞቹ ተመሳሳይ አስተያየታቸዉን አጋርተዉናል። መልካም አስተዳደር ማስፈን ስንት የስልጣን ዘመንን ይፈልጋል? ሲሉ በትችት መልክ ሃሳባቸዉን ያቀረቡም አሉ። ሌሎች ደግሞ ጠቃላይ ሚኒስትሩ ያሉት ትክክል ቢሆንም ለችግሩ መፍቴ እንደሌላቸዉና ችግሩን ለመቅረፍም አቅም የላቸዉም ሲሉ አስተያየታቸዉን አስቀምጠዋል።
መርጋ ዮናስ
ነጋሽ መሐመድ