1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

መፍትሔ ያልተገኘለት የቡሩንዲ ውዝግብ

ቅዳሜ፣ ሚያዝያ 1 2008

በቡሩንዲ ሁከቱ ጨርሶ ያበቃ ይመስላል። ይሁንና፣ ውዝግቡ ከውጭ ለሚያየው ያለቀለት ቢመስልም ውስውስጡን መቀጠሉን ጠበብት አስጠንቅቀዋል።

https://p.dw.com/p/1ISD1
nach Putschversuch - Präsident Pierre Nkurunziza zurück im Amt
ምስል Reuters/G. Tomasevic

[No title]

የቡሩንዲ ፕሬዚደንት ፒየር ንኩሩንዚዛ ባለፈው ሚያዝያ ወር የሀገሪቱን ሕገ መንግሥት ሽረዉ ለሶስተኛ ዘመነ ሥልጣን እንደሚወዳደሩ ባስታወቁበት ጊዜ በሀገሪቱ ተቀስቅሶ የነበረው ግጭት እና ሁከት አሁን አብቅቶ መረጋጋት የሰፈነ እንደሚመስል የአፍሪቃ ህብረት ዲፕሎማት ካሲሚ ባምባ ገልጸዋል።

«የቡሩንዲ ሁኔታ በወቅቱ የተረጋጋ እንደሚመስል ለመናገር እፈልጋለሁ። መረጋጋት አለ ቢባልም ግን ሰዎች ይገደላሉ፣ እርግጥ ቁጥራቸው እንደበፊቱ ባይሆንም። በተለይ፣ የመንግሥቱ ተቃዋሚዎች በሚኖሩባቸው አካባቢዎች ላይ ጠንካራ ርምጃ ይወሰዳል። አንዳንድ ወጣቶች በፀጥታ ኃይላት ይታገታሉ። እድል አድርገው ካልተለቀቁ በስተቀር። አልፎ አልፎ አስከሬናቸው የሆነ ቦታ ተጥሎ ይገኛል።»

Burundi Polizeigewalt - Polizei schlägt Jungen
ምስል picture-alliance/dpa/D. Kurokawa

ዲፕሎማቱ ይህንን ያስታወቁት የጀርመናውያኑ የሀይንሪኽ በል የፖለቲካ ጥናት ተቋም ከዶይቸ ቤለ እና ከኔትዎርክ አፍሪካ ጋር በመተባበር ሰሞኑን በበርሊን « በቀውስ አፋፍ ላይ ለምትገኘው ቡሩንዲ ሰላማዊ መፍትሔ የማስገኘቱ ዕድል ይኖር ይሆን? » በሚል ርዕስ ባዘጋጀው የውይይት መድረክ ላይ ነበር። እንደሚታወሰው፣ በቡሩንዲ ከሚያዝያ፣ 2015 ዓመ በኋላ በቀጠሉት በርካታ ወራት በተካሄደው ደም አፋሳሽ ሁከት ቢያንስ 400 ሰዎች ተገድለዋል፣ 3,500 ታስረዋል፣ 220,000 ደግሞ ወደ ጎረቤት ሃገራት ሸሽተዋል።

ከውጭ ለሚያየው ሁኔታዎች የተረጋጉ ቢመስልም ውዝግቡ ውስውስጡን እንደቀጠለ የሚያስጠነቅቁት አንዳንድ ጠበብት፣ በሀገሪቱ በቅርቡ ሰላም የሚወርድበት ዕድል ዝቅተኛ መሆኑን ይናገራሉ። እርግጥ፣ የዓለም አቀፉን ማህበረሰብ እውቅና ያላገኙት ፒየር ንኩሩንዚዛ የሚመሩት የቡሩንዲ መንግሥት በመላ ሀገሪቱ የሰላም ድርድር የሚመራ አንድ ኮሚቴ አቋቁሞዋል። ይሁንና፣ የኮሚቴውን ውጤታማነት፣ እንደ ጋዜጠኛ ቦብ ሩጉሪካ፣ ብዙዎችም ተጠራጥረውታል።
«ይህ ውይይት በማን እና ማን መካከል ነው የሚካሄደው? ምክንያቱም ብዙዎቹ ተቃዋሚዎች በሙሉ በስደት ላይ ነው የሚገኙት። ዋነኞቹ የሲቭል ማህበረ ሰብ መሪዎች በስደት ላይ ናቸው።»

«ራድዮ ፒውብሊክ አፍሪኬን» የተባለው የግል ራድዮ ጣቢያ የቀድሞ ዋና ስራ አስኪያጅ ሩጉሪካ የመንግሥት ደህንነት ክትትልን ሸሽቶ ስደት የገባው ባለፈው ዓመት ነበር። የአፍሪቃ ህብረት ዲፕሎማት ካሲሚ ባምባም የሚደራደረው ተቀናቃኝ ወገን በሌለበት መንግሥት ብቻውን ድርድር ሊመራ አይችልም የሚለውን የሩጉሪካን አባባል ይጋሩታል። ሁሉን የሚያሳትፍ ድርድር ከቡሩንዲ ውጭ ሊካሄድ እንደሚገባ በተደጋጋሚ የቀረበውን ሀሳብ የቡሩንዲ መንግሥት ውድቅ እንዳደረገው ባምባ አስታውቀዋል።

Burundi Podiumsdiskussion DW
የበርሊኑ የውይይት መድረክምስል DW/D. Pelz

ብዙው የቡሩንዲ ሕዝብ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ሰላም አስከባሪ ጓድ እንዲልክ ተስፋ ቢያደርግም፣ የተመድ ፀጥታ ጥበቃ ምክር ቤት ባለፈው ዓርብ አንድ የፖሊስ ኃይል ወደዚችው የምሥራቅ አፍሪቃ ሀገር ለመላክ መወሰኑ ቅር እንዳሰኛቸው ሩጉሪካ አመልክተዋል። በተመድ የቡሩንዲ አምባሳደር መግለጫ መሰረት፣ የሚላኩት ፖሊሶች ቁጥር ከ20 እስከ 30 ብቻ በመሆኑ፣ ዓለም አቀፉ የፖሊስ ጓድ ለመላክ የተያዘው እቅድ ሀገሪቱን በማረጋጋቱ ላይ ትልቅ ሚና ይኖረዋል የሚል ተስፋ እንደሌላቸው ሩጉሪካ ገልጸዋል፣ ምክንያቱም ይኸው ንዑሱ የፖሊስ ጓድ የቡሩንዲን ውዝግብ ማስወገድ የሚችልበበት አቅም የለውም።

Burundi Journalist Bob Rugurika
ምስል Getty Images/C. de Souza

ይሁን እንጂ፣ ምንም እንኳን በበቡሩንዲ ሁከቱ አሁንም ውስጥ ለውስጥ መብላላቱን ቢቀጥልም፣ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ በሀገሪቱ በ1994 የተነሳው ዓይነት የጎሳ ጭፍጨፋ ይዳግም ይፈጠራል የሚል ስጋት የለውም፣ እንደ ጀርመናዊትዋ የበርሊን ፖሊቲክ ኡንድ ቪስንሻፍት» የተባለው የፀጥታ ጥናት ተቋም ባልደረባ ክላውዲያ ዚሞንስ ግምት።
«መሰረቱ፣ ሰፊው የቡሩንዲ ሕዝብ ራሱን ጎሳን መለኪያ ባደረገ መስመር ለማደራጀት ፈቃደኛ እንዳልሆነ በግልጽ እያሳየ ነው። ይህ ግን ፣በተለይ፣ ባለፉት አስር ዓመታት ውስጥ በቡሩንዲ የርስበርስ ጦርነት ወቅት ተወያይቶ ሀቀኛ እርቀ ሰላም በመፍጠሩ ረገድ አንዳችም ስራ አለመሰራቱ ሲታሰብ፣ ጎሰኝነት በወቅቱ አንዳችም ሚና አይጫወትም ማለት አይደለም።»

እርግጥ፣ የጎሳ ጥያቄም ሀገሪቱ ለምተገኝበት ቀውስ አንዱ ምክንያት ቢሆንም፣ በጀርመን ፌዴራዊ ምክር ቤት፣ ቡንድስታግ የተወከለው የተቃዋሚው የአረንጓዴዎቹ ፓርቲ እንደራሴ ኮርዱላ ሹልስ አሸ እንዳስረዱት፣ አንድ ንዑስ የገዢው መደብ ክፍል ብቻ ከሀገሪቱ ፖለቲካ እና ኤኮኖሚ ተጠቃሚ መሆኑ ለቀውሱ መባባስ ሰፊ ድርሻ ማበርከቱ ሊረሳ አይገባም። ሹልስ አሸ እና አንዳንድ የምክር ቤት እንደራሴዎች ለውዝግቡ የራሳቸውን አስተያየት ለመያዝ በ2015 ዓም ወደዚችው ሀገር ተጉዘው ነበር።

«በዚያን ጊዜ ከቡሩንዲ የምክር ቤት አቻዎቻችን ጋር ተወያይተናል፣ እና የሚያስገርመው፣ ሁሉም ያጎሉት በወቅቱ የጎሳ ጥያቄ ውጥረት አለመፍጠሩን ነበር።»

DEU Karte Burundi

የቡሩንዲን ውዝግብ ላንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ ለማብቃትም ሁሉን ከሚያሳትፍ የሰላም ድርድር የተሻለ ሌላ አማራጭ እንደሌለ ያስረዱት ሹልስ አሸ አስረድተው፣ የአውሮጳ ህብረት ከአፍሪቃ ህብረት ጋር በመተባበር በቡሩንዲ ላይ ጫና እንዲያሳርፍ አሳስበዋል። በቅርቡ ሰላም ካልወረደ በስተቀር፣ በቡሩንዲ አዲስ ግጭት እና ሁከት የሚፈነዳበት ስጋት ከፍተኛ ነው በሚለል በተሰነዘረው ሀሳብ ላይ መደቀኑን በበርሊኑ የውይይት መድረክ የተሳተፉት የፖለቲካ ተንታኞች እና ፖለቲከኞች ተስማምተውበታል፣ እንደ ክላውዲያ ዚሞንስ እንዳስጠነቀቁትም፣ ውዝግቡን በዘለቄታ ለማስወገድ ካልተቻለ ሀገሪቱ ትልቅ አደጋ ላይ የምትወድቅበት ስጋት ተደቅኖባታል።

«በቡሩንዲ በአሁኑ ጊዜ መረጋጋት ቢታይም የተረጋጋ ሁኔታ ቢታይም፣ ይህ ቀጣይ ይሆናል ማለት አይደለም። ለቡሩንዲ ቀውስ የፖለቲካ መፍትሔ እስካልተገኘለት ድረስ ሁኔታዎች በቀጣዮቹ ዓመታት ከቁጥጥር ውጭ ሊሆኑ ይችላሉ።»

አርያም ተክሌ

ማንተጋፍቶት ስለሺ