1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ማዲባ የድቡብ አፍሪቃውያን አባት

ዓርብ፣ ኅዳር 27 2006

እንደ ወጣት በእልሕ፥ እንደ ወታደር በነፍጥ፥ እንደ ሕግ አዋቂ በፍርድ ቤት ታገሉ።እንደ ወንጀለኛ ታሠሩ።እንደ ዲፕሎማት ተደራደሩ፥ እንደ ፖለቲከኛ የሕዝብ እኩልንነትን አስርፀዉ ሐገር መሩ።እና እንደ ሰዉ የምድር ሩጫቸዉን ትናንት ጨረሹ።ዘጠና አምስት አመታቸዉ ነበር።

https://p.dw.com/p/1AUUW
ምስል picture-alliance/dpa

የሕዝብ ነፃነት፥ ፍትሕ፥ እኩልነትን ሚሊዮነ-ሚሊዮናት ይፈልጉ-ይመኙታል ። መቶ ሺሕ ዎች ይታገሉ ወይም ለመታገል ይሞክሩታል።ሺዎች ትግሉን ያጋምሱ ወይም ይሰዉለታል።ዓላማ ትግሉን ከግብ የሚያደርሱት ግን፥- እኒያ ጥቂት በጣም ጥቂት ቆራጦች፥ ብልሆች፥ ታጋሾች፥ ስልት አዋቂዎች፥ እና እድለኞች ብቻ ናቸዉ።ኔልሰን ሆሊሻሻ ማንዴላ ከበጣም ጥቂቶቹ አንዱ ናቸዉ።ዛሬ ነበሩ-ነዉ የሚባለዉ-በርግጥ።እንደ ወጣት በእልሕ፥ እንደ ወታደር በነፍጥ፥ እንደ ሕግ አዋቂ በፍርድ ቤት ታገሉ።እንደ ወንጀለኛ ታሠሩ።እንደ ዲፕሎማት ተደራደሩ፥ እንደ ፖለቲከኛ የሕዝብ እኩልንነትን አስርፀዉ ሐገር መሩ።እና እንደ ሰዉ---«አፈርነሕና» እንዳለዉ መፅሐፉ----የምድር ሩጫቸዉን ትናንት ጨረሹ።ዘጠና አምስት አመታቸዉ ነበር።

« የነጮች የበላይነትን ታግያለሁ ። የጥቁሮች የበላይነትንም ታግያለሁ ። ስዎች ሁሉ በእኩልነትና በሰመረ ግንኙነት አብረው የሚኖሩበትን የዴሞክራሲያዊና ነፃ ማህበረሰብ ሃሳብ መርህ በጥብቅ ስሜት አራምጃለሁ ። ይህን ዓላማ እንግቤ ለመኖር ና ለመፈፀም ተሰፋ አለኝ ። አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ለዚህ እምነቴ ህይወቴን አሳልፊ ለመሰጠት ዝግጁ ነኘ ። »

ኔለሰን ማንደላ በዘር አድሎው ስርዓት የ 3 አስርት ዓመት እስር ሲበየንባቸው ለመሃል ዳኛው የሰጡት ታሪካዊ መልስ ፤ ከ27 ዓመታት እስር በኋላ እጎአ በ 1990 ሲለቀቁም ደጋፊዎቻቸው ፊት ለማምንበት ዓላማ ለመሞት ዝግጁ ነኝ ሲሉ ዳግም የተናገሩት ዝነኛ አባባል ። በጎርጎሮሳውያኑ ሐምሌ 18 ,1918 ማንዴላ ሲወለዱ አባታቸው ጋዴላ Rolihlahla ሆሊሻሻ ብለው ስም ሲያወጡላቸው ልጃቸው ጠንካራ ባህርይ እንዳለው ታውቋቸው ነበር ።

Bildergalerie Leben Nelson Mandela
ማንዴላና ዴክለርክምስል picture-alliance/AP

ሆሊሻሻ ትርጉሙ በሾዋና ቋንቋ ቅርንጫፎች ዘንጣፊ ማለት ነው ። በሌላ አባባል ሰዎችን የሚያናድድ ማለት ነው ። ማንኛውም የቆዳ ቀለም ባላቸው ደቡብ አፍሪቃውያን የሚጠሩበት የፍቅርና የአክብሮት ስሙ ማዲባ ከራሱ ጎሳ የተሰጠው ስም ነው ። ማንዴላ የዘር መድልዎ ሰርዓት የነበራትን ደቡብ አፍሪቃን የሚያናድድ ተግባር የሚፈፀም ሆነ ። በወጣትነት እድሜው አንዱን ወይንም ሌላኛውን ቅርንጫፍ መጣሉን ተያያዘ ። የባላባት ልጅ እንደመሆኑ ተቀማጥሎ ያደገው ማንዴላ በዩኒቨርሰቲ የተማሪዎች ተቃውሞ መሪ ሆነ ። ከጊዜ በኋላም እንዳይዳር በምሥራቅ ኬፕ ከምትገኘው ከትውልድ መንደሩ ከኩኑ ኮብሎሎ ወደ ጆሃንስበርግ ገብቶ የፖለቲካ ንቃተ ህሊናውን አዳበረ ። ከዚያም በጎሮጎሮሳውያኑ 1944 ማንዴላ የአፍሪቃ በሔራዊ ምክር ቤት ANC አባልሆኑ ። በ1948 ብሔረተኛው የነጮቹ ፓርቲ ሥልጣን ያዘና የዘር መድልዎ ስረዓቱን ዘረጋ ። ከዚያም ህዝባዊ ተቃውሞና የሲቪል አመፅ ተከተለ ። በዚህም ዘመቻ ማንዴላ አብይ ድርሻ ነበራቸው ። ANC በ 1960 ከታገደ በኋላ «ኡምኮንቶ ሲዝዌ »የተባለውን የድርጅቱን ወታደራዊ ክንፍ አቋቋሙ ። ማንዴላ ዋና አዛዥ ሆኖ የደፈጣ ውጊያ በመምራት የመንግሥት ተቋማት እንዲመቱ አደረጉ ።

« የትጥቅ ትግል ጥሪ ያደረኩበትን መግለጫ አውጥቻለሁ ። ምክንያቱም መንግሥት ምንም ምርጫ አልተወልንም ነበርና ። »

እጎአ በ 1962 ለANC ካድሬዎች የገንዘብ ድጋፍ ለማሰባሰብ በድብቅ ከሃገር ወጡ ። ሲመለሱም ታስረው ሪቮንያ በተሰየመው ችሎት ተፈረደባቸው ። ማንዴላ 18 ት ዓመት በቅጣት የደቡብ አፍሪቃዋ አልካትራትስ በምትሰኘው

Bildergalerie Jürgen Schadeberg
ማንዴላ በሮቢኑ ደሴት እስር ቤትምስል J. Schadeberg

ከኬፕታውን ትይዩ ፈንጠር ብላ በምትገኘው ድንጋያማዋ የሮቢን ደሴት ታሠሩ ።

የታሠረበት ቤት ቁጥር 5 ፣ አሁን ወደ ደቡብ አፍሪቃ ለሚሄድ አገር ጎብኚ ትልቅ መስህብ ነው ። ማንዴላ ከ 1988 አንስቶ ሊፈቱ እንደሚችሉ ያውቅ ነበር ። ከዚያ ቀደም ሲል ANC የኃይል እርምጃን እርም ቢሎ ቢተው ምህረት እንደሚደረግላቸው ቢጠቆምም አልተቀበሉትም ነበር ። እጎአ የካቲት 1990 የደቡብ አፍሪቃው የነጸነት አርማ ከ 27 ዓመት እስራት በኋላ ነፃነታቸውን አገኙ።

«ከ 27 ዓመታት እሥራት በኋላ ኔልሰን ማንዴላ ነፃ ወጥተዋል ።»

የአፍሪቃው ማርቲን ሉተረ ኪንግ ዘረኛነቱ ስርዓት እንዲነሳ ብርቱ ግፊት በማድረግ በሚያዚያ ወር 1994 የመጀመሪያው ነፃ ምርጫ እንዲከናውን አበቁ ። ግንቦት 10 1994 ኔልሰን ማንዴላ የመጀመሪያው የደቡብ አፍሪቃ ጥቁር ፐረዝዳንት በመሆን ቃለ መሃላ ፈፀሙ ።

« ይህ በሃገራችን ታሪክ እጅግ ጠቃሚ ክሆኑት መዕራፎች አንዱ ነው ። ክፊታችሁ የቆምኩት በጥልቅ ኩራትና ደሰታ ተሞልቼ ነው ። የዚህች አገር ጨዋ ህዝብ ይህችን ሃገር መልሳችሁ በእጃችሁ ለማስገባት በርጋታና በትዕግሥት ቁርጠኘነታችሁን አሳያታችኋል ብዮ አስባለሁ ። ከግድግዳ እሰከ ጣሪያ ድረስ የራሳችሁ ንብረት መሆኑን አስመሰክራችኋል ። በመጨረሻም ነፃነት ተጎናፅፈናል ። »

Nelson Mandela Rede im Bundestag
ማንዴላ በጀርመን ምክር ቤትምስል picture-alliance/dpa

ከዚያ በኋላ ኔልሰን ማንዴላ የተለያየ የቆዳ ቀለም ባለው ህዝብ መካከል እርቀ ሰላም እንዲወርድ ፣ ከዚያም በዘር መድልው ስርዓት የተሰራው ወንጀል እንዲመረመርና የእውነት አጣሪና የእርቅ ኮሚሽን እንዲመሰርት አደረጉ ። በ 1999 በትጋት በፖለቲካው መሳተፉን ትተው ከተሰናበቱ በኋላ ማዲባ የማህበራዊ ኑሮ ሃላፊነታቸውን ለመወጣት ተሰማሩ ልባቸው የላቀ ርህራሄ ያሳየው ለልጆችና ለ HIV AIDS ህሙማን ሆነ ። የሚወዷት ዜናኒ የተባለችው የልጅ ልጃቸው በድንገተኛ አደጋ ከሞተች በኋላ ማንዴላ በአደባባይ ከመታየት ተቆጠቡ ። ያኔ ከጆሀንስበርግ ወደተወለዱበት መንደር ኩኑ የተዛወሩት ማንዴላ ባለፈው ዓመት በሰኔ ወር ፕሪቶሪያ ሆስፒታል በገቡበት ወቅት ፍፃሜያቸው ተቃርቧል ተብሎ ነበር ። ይሁንና ከፍተኛ ህክምና ከተደረገላቸው በኋላ በዚህ ዓመት መስከረም ከሆስፒታል ወጡ ። ከሆስፒታል በወጡ በ 3ተኛ ወራቸው ትናንት አረፉ ። ትልቁ የኬፕ አዛውንት ማንዴላ የተለያየ ዘር በአንድ ላይ ለሚኖርባት ደቡብ አፍሪቃ የሰጡት ይህ ማሳስቢያ ዘወትር ከሚታወሱባቸው መልዕክቶች አንዱ ነው ።

« በማንኛውም መልኩ የሚንጸባረቀውን የዘር አድልዎ ሰርዓት ለማጥፋትና የዚህን ሃገር ሰዎች የተዛባ አመለካከት መቀየር በአንድ ለሊት የሚከናወን አይደለም ። እንደሚመስለኝ በሂደት የሚሆን ነው ። አገሪቱን ለገጠማት የማህበራዊ ኑሮና ኤኮኖሚያዊ ችግሮች መፍትሄ ለማግኘት ራዕዩ ሊኖርን ይገባል »

ሉድገር ሻዶምስኪ/ ኂሩት መለሰ

ተክሌ የኋላ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ