1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ማዳጋስካር እና የገጠማት አዲስ ውዝግብ

ቅዳሜ፣ ሰኔ 6 2007

በአፍሪቃ የትልቋ ደሴት ማዳጋስካር ፕሬዚደንት ኤሪ ራዣኦናሪማምፒያኒና እንዲወርዱ የሀገሪቱ ምክር ቤት እአአ ግንቦት 26፣ 2015 ዓም ድምፅ ከሰጠ ወዲህ ጉዳዩ የሀገሪቱን ፖለቲከኞች ማወዛገቡን ቀጥሎዋል።

https://p.dw.com/p/1FgUP
Bildergalerie Herausforderungen für Madagaskars neuen Präsidenten Verfassungsgericht
ምስል DW/P. Hille

[No title]

ፕሬዚደንት ራዣኦናሪማምፒያኒና የምክር ቤቱ ውሳኔ ፣ የድምፅ አሰጣጡ ስነ ስርዓት ትክክለኛ አልነበረም በሚል ጉዳዩን ለሕገ መንግሥታዊው ፍርድ ቤት አቅርበዋል። በድምፅ አሰጣጡ ጊዜ በምክር ቤት ከነበሩት 125 እንደራሴዎች መካከል 121 ፕሬዚደንቱ እንዲወርዱ የጠየቀውን ሀሳብ መደገፋቸውን የተቃውሞ ቡድኖች ቢያስታውቁም፣ የፕሬዚደንቱ ደጋፊዎች በድ ምፅ አሰጣጡ ወቅት የነበሩት 102 እንደራሴዎች ብቻ መሆናቸውን ነው ያመለከቱት። የፕሬዚደንቱ ጠበቃ ፍርድ ቤቱ በሀገሪቱ እርቀ ሰላም የሚያወርድ ውሳኔ እንዲሰጥ ሲማፀኑ፣ የተቃዋሚ ቡድኖች ጠበቃ ደግሞ የምክር ቤቱን ውሳኔ እንዲያረጋግጥ ጠይቀዋል። ፍርድ ቤቱ የተቀናቃኞቹን ወገኖች መከራከሪያ ሀሳብ በጥሞና እንደሚመለከት ቢያስታወቅም፣ ውሳኔ የሚሰጥበትን ዕለት አልገለጸም። የማዳጋስካር ሕገ መንግሥታዊ ፍርድ ቤት ትክክለኛውን ውሳኔ በመስጠት ውዝግቡን እንደሚያበቃ ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ወይዘሮ ቤአትሪስ አታላ ላ ተስፋቸውን ገልጸዋል።

« አሁን ባለን መረጃ መሠረት፣ ሕገ መንግሥታዊው ፍርድ ቤት ውሳኔውን ከጥቂት ቀናት በኋላ ይሰጣል። ውሳኔውን ለፍርድ ቤት ብልህነት እተወዋለሁ። »

Beatrice Atallah
ቤአትሪስ አታላምስል imago/Xinhua

እአአ በ2009 ዓም ከተካሄደው የመጀመሪያ መፈንቅለ መንግሥት በኋላ በደሴቲቱ እአአ በ2013 ዓም በሰላማዊ ሂደት የተመረጡት ፕሬዚደንት ራዣኦናሪማምፒያኒና በምርጫው ዘመቻ ወቅት የገቡትን ቃል አልጠበቁም፣ የሀገሪቱ ኤኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ አገልግሎት ሰጪ ዘርፎች አስተዳደራቸውም ላይ ብዙ ጉድለቶች እየታዩ ነው፣ እና ሀይማኖታዊ ጉዳዮችንም በሀገር ፖለቲካ ውስጥ ለማስገባት ሞክረዋል በሚል ተቃዋሚዎቻቸው አብዝተው ይወቅሱዋቸዋል። አሁን በፕሬዚደንቱ እና የተቃዋሚ ፖለቲካ ቡድኖች መካከል የተነሳው ውዝግብ ከብዙ ዓመታት ቀውስ በኋላ ራሷን መልሳ ለመገንባት ጥረት በማድረግ ላይ ያለችውን በማዕድን ሀብት የታደለችውን ሀገር መረጋጋት እንደገና ችግር ውስጥ እንዳይጥል ማስጋቱን ያካባቢውን ፖለቲካ የሚከታተሉ የፖለቲካ ጥናት ተቋማት ተንታኞች ገልጸዋል። ይሁንና፣ ከዓለም አቀፉ ንግድ ጎን ፣ በተለይ ካለፉት ጥቂት ዓመታት ወዲህ በፀጥታ ጥያቄዎች ላይ የያዘችው ሚና ከፍተኛ ትኩረት እያገኘች የመጣችው በሕንድ ውቅያኖስ የምትገኘዋ ደሴቲቱ ማዳጋስካር ውስጥ አዲስ ቀውስ ሊፈጠር ይችል ይሆናል በሚል የተሰነዘረውን ስጋት ባለፈው ማክሰኞ እአአ ሰኔ ዘጠኝ፣ 2015 ዓም በበርሊን በተካሄደው የሕንድ ውቅያኖስ ፖለቲካዊ፣ ኤኮኖሚያዊ እና ስልታዊ ትርጓሜን በተመለከተው ጉባዔ ላይ የተካፈሉት የማዳጋስካር ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ወይዘሮ ቤአትሪስ አታላ መሠረተ ቢስ ሲሉ አጣጥለውታል።

« እርግጥ፣ ዴሞክራሲን በመትከሉ ሂደት ላይ ገና ጀማሪዎች ነን። ይሁንና፣ በወቅቱ የሚታየው ሁኔታ ሀገራችንን ወደ አዲስ ቀውስ እያመራት ነው በሚል የሚሰማውን አስተያየት በፍፅም አልቀበለውም። በኔ አመለካከት በሀገራችን ውጥረት እና አለመረጋጋት ለመፍጠር ሙከራዎች ናቸው። ይህ እንዳይሆን ውይይት ለመጀመር ዕቅድ አለ። የማዳጋስካር ሕዝብ ጥረት መና እንዳይቀር ውዝግቡ የሚመለከታቸውን ተቀናቃኝ ወገኖች ሁሉ ለድርድር ጋብዘናል። በዚሁ ጥረታችን ላይ ወዳጆቻችን ስለሚደግፉን ተደስቻለሁ። የማዳጋስካር ፖለቲከኞች ይህን ጥረት እንዲደግፉ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብም ጥሪ አስተላልፎዋል። »

አርያም ተክሌ

አዜብ ታደሰ