1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሞዛምቢክ እና የሰላሙ ተስፋ

ሰኞ፣ ሐምሌ 28 2006

በሞዛምቢክ የጦር መሳሪያ የታጠቁ ተዋጊዎች ያሉት ትልቁ የተቃውሞ ቡድን፣ በፈሬሊሞ ፓርቲ በሚመራው መንግሥት አንፃር ሬናሞ እአአ ከጥቅምት 2013 ዓም ወዲህ ውጊያ በማካሄድ ላይ ነው።

https://p.dw.com/p/1Cng9
Mosambik RENAMO Rebellen im Gorongosa Gebirge 2012
ምስል Jinty Jackson/AFP/Getty Images
ይኸው ውጊያ በቅርቡ ያለፈ ታሪክ ሊሆን እንደሚችል ተቀናቃኞቹ ወገኖች እየተናገሩ ነው። ምክንያቱም፣ መንግሥት እና ሬናሞ ከአዳጋች ድርድር በኋላ በሚቀጥለው ሳምንት ሰኞ የሰላም ውል ሊፈራረሙ እንደሚችሉ የሁለቱ ወገኖች ተደራዳሪ ቡድናት መሪዎች አስታውቀዋል። ይኸው ይፈረማል የሚባለው የሰላም ውል ዘላቂ ይሆናል? አይሆንም? ብዙዎችን እያነጋገረ ነው።

ሰሜን እና ደቡብ ሞዛምቢክን የሚያገናኘው ዋነኛው ብሔራዊ መንገድ በአሁኑ ጊዜ ባልተለመደ ሁኔታ መረጋጋት ይታይበታል። በዚሁ መንገድ በሚተላለፉት መኪኖች፣ አውቶቡሶች እና የጭነት ተሽከርካሪዎች ላይ ባለፉት ጊዚያት አንድም ተኩስ አልተከፈተም፣ እርግጥ፣ መረሳት የሌለበት፣ በዚሁ መንገድ በኪል የሚተላለፉት መኪኖች በጦር ተሽከርካሪዎች ታጅበው መሆኑን ነው። ይህ ግን፣ በቅርቡ ያለፈ ጊዜ ታሪክ ሊሆን እንደሚችል ነው የፖለቲካ ተንታኞች የሚናገሩት።

Mosambik Afonso Dhlakama Führer der Oppositionspartei RENAMO 2012
ምስል Getty Images/AFP

በሞዛምቢክ ከብዙ ዓመታት ወዲህ የሚወዛገቡት ተቀናቃኞቹ ፓርቲዎች፣ ማለትም፣ ገዢው የፍሬሊሞ ፓርት እና ትልቁ የተቃውሞ ፓርቲ ፣ ሬናሞ ካለፉት በርካታ ወራት ወዲህ በመካከላቸው እንዳዲስ የፈነዳውን ጦርነት በድርድር ሊያበቁ የሚችሉበት ስምምነት ላይ ለመድረስ መቃረባቸውን አስታውቀዋል። ውዝግቡ የተጀመረው እአአ ጥቅምት 2013 ዓም የመንግሥቱ ጦር የሬናሞ ዓማፅያን መሪ አፎንሶ ድላካማ ጽሕፈት ቤትን ባጠቃበት እና ሬናሞም እአአ በ1992 ዓም ከፍሬሊሞ ጋ የተፈራረመውን ውል እንደማያከብር ባስታወቀበት ጊዜ ነው። በዚሁ ውጊያ፣ ዶይቸ ቬለ ባገኘው መረጃ መሠረት፣ ቢያንስ 54 ሰዎች ሕይወታቸውን አጥተዋል። የሞዛምቢክ መንግሥት የተደራዳሪዎችን ቡድን የመሩት ኾዜ ፓቼኮ ከ66ኛው የድርድር ዙር በኋላ ሁለቱ ወገኖች የፊታቸeን ሰኞ ይፈራረሙታል ተብሎ በሚጠበቀው የሰላም ውል ላይ የሠፈሩትን ሀሳቦች እንዲህ ዘርዝረዋቸዋል።

Kohlemine Minas Moatize
ምስል DW/J. Beck

« ይኸው ሰነድ ወሳኝ የሚባሉትን ነጥቦች ሁሉ ይዞዋል። በዚሁ መሠረት፣ አንደኛ፣ የጦር ጥቃት በጠቅላላ መቆም አለበት፣ ሁለተኛ፣ የሬናሞ ዓማፅያን በሀገሪቱ ጦር እና ፖሊስ ኃይል ውስጥ መዋኃድ አለባቸው። ሦስተኛ፣ የሬናሞ አባላት በማህበራዊው እና ኤኮኖሚያዊው ዘርፍ ውስጥ እንደገና የሚዋኃዱበት ሁኔታ መመቻቸት ይኖርበታል። አራተኛ፣ ይኸው ሂደት ከተጠናቀቀ በኋላ የትኛውም ፓርቲ የታጠቀ የጦር ቡድን ሊኖረው እንደማይገባም ተስማምተናል። »

ፍሬሊሞ እና ሬናሞ አዲስ በሚፈራረሙት ውል ላይ ሁለቱም ወገኖች ከሞላ ጎደል መስማማታቸውን የተቃዋሚውን ሬናሞ የተደራዳሪ ልዑካን ቡድን መሪ ሳይመን ማክዌኒ አስታውቀዋል።

« ድርድሩ ለሀገራችን ዘላቂ ሰላም እና መረጋጋት ለማውረድ የምንችልባቸውን ሀሳቦች ሁሉ ያጠቃለለ ነው። እነዚህኑ ሀሳቦች በቀጣዩ የድርድር ዙር ላይ እናቀርባለን። ይኸው የድርድር ዙር ባለፉት ቀናት እንዳካሄድናቸው ውይይቶች በቀና መንፈሥ ይከናወናል ብለን ተስፋ አድርገናል። »

Mosambik Kommunalwahlen
ምስል Nelson Carvalho Miguel

መልስ ላላገኙት ጥያቄዎችም እስከፊታችን ሰኞ ድረስ መልስ እንደሚገኝላቸው ማክዌኒ ተስፋቸውን ገልጸዋል።

ከጥቂት ጊዜ በፊት በሞዛምቢክ የታዩት ሁኔታዎች ውዝግቡን ይበልጡን እንዳያባብሱ አሥግተው እንደነበር ይታወሳል። እንደሚታወቀው ሬናሞ ባንድ በኩል ባለፈው ሰኔ ወር የተኩስ አቁም ደንብ እንደደረሰ አስታውቆ፣ በሌላ ወገን ግን በማዕከላይ ሞዛምቢክ ጥቃቱን አጠናክሮ ነበር፣ ይህ ሲታሰብ ታድያ፣ አሁን ድንገት በሀገሪቱ ሰላም የሚወርድበት ጊዜ ተቃርቦዋል መባሉ ብዙዎችን አስገርሞዋል። ለዚህም አንዳንድ የፖለቲካ ተንታኞች እንደሚገምቱት የፊታችን ጥቅምት ወር በሀገሪቱ የሚደረገው ምክር ቤታዊ እና ፕሬዚደንታዊ ምርጫ ምክንያት ሊሆን ይችላል። እንደሚባለው የሬናሞ መሪ አፎንዞ ድላካማ በፕሬዚደንታዊው ምርጫ ላይ በዕጩ ተወዳዳሪነት ለመቅረብ ዕቅድ አላቸው። በዚህም የተነሳ የምርጫ ዘመቻውን እንደሚፈለገው ለማካሄድ በብሔራዊው ጎሮንጎዛ ፓርክ አቅራቢያ ካለው መሸሸጊያ ቦታac,ው መውጣት ይኖርባቸዋል። ምክንያቱም፣ ባለፈው ህዳር 2013 ዓም በሀገሪቱ በተካሄደው የከተሞች አስተዳደር ምክር ቤታዊ ምርጫ ላይ ሬናሞ አልተሳተፈም ነበር፣ በዚያን ጊዜው ምርጫም ሌላው ራሱን የዴሞክራቲክ ሞዛምቢክ ንቅናቄ ብሎ የሚጠራው እና ከሬናሞ የተገነጠሉ ዓማፅያን ያቋቋሙት ተፎካካሪ ተቃዋሚ ፓርቲ የብዙ መራጭ ድምፅ ማግኘት ችሏል። ይኸው ውጤትም ሬናሞን እና መሪውን አላስደሰተም።

Silvério Ronguane
ምስል privat

ከዚህ ሌላም እንደ ፖለቲካ ተንታኞች ግምት፣ ገዚው የፍሬሊሞ ፓርቲ ውዝግቡ ቶሎ እንዲያበቃ የሚፈልግበት የራሱ ምክንያት አለው። እንደሚታወቀው በውዝግቡ ሰበብ የሀገሪቱ ኤኮኖሚ ዕድገት ላይ ጉዳት እያደረሰ ነው ያለው። የሀገሪቱ የከሰል ድንጊያ ማዕድን ዓማፅያኑ በሚሰነዝሩዋጭው ጥቃቶች ወደ ውጭ የሚላክበት ሂደት ባለፉት ጊዚያት በተደጋጋሚ ተስተጓጉሎዋል። ቱሪስቶችም ወደ ሞዛምቢክ የሚሄዱበት ሁኔታም ከሞላ ጎደል ተቋርጦዋል። እምነት ያጡት ዓለም አቀፍ ባለወረቶችም ገንዘባc።ውን በሀገሪቱ ከማሰራት ወደኋላ ብለዋል። ከዚህ ሌላም ሞዛምቢክ ከፖርቱጋል ቅኝ አገዛዝ ነፃ ከወጣች ወዲህ ሀገሪቱን በመምራት ላይ ያለው ፍሬሊሞ መራጩ ለተቃዋሚው ወገን የሚሰጠው ድምፅ በሬናሞ እና በየዴሞክራቲክ ሞዛምቢክ ንቅናቄ መካከል እንዲከፋፈል እና ሬናሞ ብቻውን ጠንካራ እንዳይሆን ነው የሚፈልገው። የሞዛምቢክ ተወላጅ የሆኑት የፖለቲካ ተንታኝ ሲልቬርዮ ሮንግዋን እንደሚሉት ፣ በዚያም ሆነ በዚህ በሞዛምቢክ መንግሥት እና በሬናሞ መካከል የፊታችን ሰኞc ይፈረማል ተብሎ የሚጠበቀው የሰላም ውል ዘላቂ ሰላም ማስገኘት አለማስገኘቱ እአአa የፊታችን ጥቅምት 15፣ 2014 ዓም በሀገሪቱ በሚደረገው ምክር ቤታዊ እና ፕሬዚደንታዊ ምርጫ ሂደት ላይ ጥገኛ ይሆናል።

« ፍትሕ መኖር አለበት፣ በሁለቱ ፓርቲዎች መካከል ጥሩ መግባባት ሊኖር ይገባል፣ ምርጫውም ግልጽ መሆን አለበት። የምርጫው ሂደት ትክክለኛ በሆነ መንገድ እስከተከናወነ ፣ ግልጽ ሕጎች እስከተከተለ እና ጥሩ ውጤት ለማግኘት ጥረት የሚያደርጉ ሁሉ ይህን ዕድል እስካገኙ ድረስ የሞዛምቢክ ዜጎች የምርጫውን ውጤት፣ ሽንፈትንም ጭምር በፀጋ መቀበል እንደሚችሉ እርግጠኛ ነኝ። »

ዮሐንስ ቤክ/አርያም ተክሌ
ማንተጋፍቶት ስለሺ