1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሠላይና ተሠላይ፤ ወዳጅና ጠላት

ሰኞ፣ ጥቅምት 18 2006

አሜሪካዊ እንደራሴና የሥለላ ጉዳይ አዋቂ ፔተ ሆክስትራን የሚያስደንቀዉ ግን የአሜሪካ ሰላዮች የጀርመንዋ መራሒተ-መንግሥትን ስልክን መጥለፋቸዉ አይደለም።የነፍሬድሪሽ ቁጣና ብስጭት እንጂ።ሆክስትራ እንደሚሉት ካስደነቀ-የሚያስደንቀዉ የጀርመን መሪ ሥልክ መጠለፉን ፍሬድሪሽ የሚመሩት የጀርመን የስለላ ድርጅት አለማወቁ ነዉ።

https://p.dw.com/p/1A7Ty
ARCHIV - US-Präsident Barack Obama und Bundeskanzlerin Angela Merkel unterhalten sich am 18.06.2012 in Los Cabos, Mexiko, beim Familienfoto. Merkel setzt bei der Aufklärung der millionenfachen Datensammlung des Geheimdienstes NSA nun auf eine Reise von Vertretern der Bundesregierung und deutscher Geheimdienste in der nächsten Woche nach Washington. Foto: Peer Grimm dpa (zu dpa "Merkel verspricht größtmögliche Offenheit bei US-Ausspähaffäre" vom 05.07.2013) +++(c) dpa - Bildfunk+++
ወዳጁ ናቸዉምስል picture-alliance/dpa

ለካሳትሮ፥ ለብሬዥነቭ፥ ለማኦ፥ ለ ደጎል፥ ለንጎ በርግጥ አዲስ አልነበረም።አይደለምም።የኤንርኮ ፔና ኔቶ ኢሜል መጠለፍ- ጉድ አሰኝቶ ነበር።የዲልማ ሮሴፍ-ኢሜል መጠለፍ-አስደንቆ ነበር።የሜርክል ሥልክ መጠለፍስ? ጉዱን ጉድ ዘለቀዉ-እንበል ይሆን።የስላላዉ ቅሌት መነሻ፥ዳራዉ ማጣቃሻ፥ የፖለቲካዉ እድምታዉ መድረሻችን ነዉ-ላፍታ አብራችሁኝ ቆዩ።


ሚዚያ ሃያ-አንድ 1943 (ዘመኑ በሙሉ እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር ነዉ።) ፈረንሳይን ከናዚ ጀርመኖች አገዛዝ ነፃ ለማዉጣት የሚዋጋዉ ጦር አዛዥ ጄኔራል ሻርል ደጎል የነፃዋ ፈረንሳይ ባሕር ሐይል ጦርን ለመጎብኘት ከተጠጉባት ብሪታንያ በብሪታንያ አዉሮፕላን ተሳፈሩ።ቆፍጣናዉ፥ ቁጡዉ፥ እልሐኛዉ ረጅሙ ጄኔራል ከትንሿ አዉሮፕላን እንደተሳፈሩ አብራሪዉ (ፓይለቱ) አዉሮፕላንኗን እንደማስነሳት ትንሽ አንገጫገጨና ወዲዚያዉ አቆማት።ጉዞዉ ተዘረዘ።

አዉሮፕላንኗ ስትፈተሽ የሞተሯ አካል በአሲድ መበላሸቱ ታወቀ።አሲዱን አዉሮፕላንዋ አካል ላይ የረጨዉ ወገን ማንነት-እስካሁን ሚስጥር ነዉ።ጄኔራሉ ግን ያኔዉኑ «የብሪታንያ ሰላዮች ሻጥር» ለማለት አላመነቱም።የአዉሮጳ እብሪተኞች የለኮሱት ጦርነት ዓለምን በሚያነድበት በዚያ ዘመን ወዳጅን ከጠላት መለየቱ-ከባድ ነበር።በዚሕም ሰበብ ደ ጎል እንደጠረጠሩት ብሪታንያዎች አድርገዉት ከነበር-ብዙዎችን ብዙም አላስደነቀም ነበር።

ከብዙ አመታት በሕዋላ የደጎልን ቤተ-መንግሥት የተረኩቡት ፕሬዝዳት ኒኮላ ሳርኮዚ ከጀርመንዋ መራሒተ-መንግሥት ከወይዘሮ አንጌላ ሜርክል ጋር የነበራቸዉ ግንኙነት ከመሪዎች-ወዳጅነትም ጠንከር፥ ጠለቅ ያለ-ነበር ይባላል።ሳርኮዚ ከሜርክል ጋር ሥላላቸዉ ግንኙነት ሥለሚያደርጉት ዉይይት ሲጠየቁ፥«ሁሌ እንገናኛለን፥ በስልክ፥ እንነጋገር፥ ኤስ ኤም ኤስ እንለዋወጣለንም» እያሉ የግንኙነት ዉይይታቸዉ ደረጃ ዘርዝረዉ ነበር።

የሜርክል መልዕክት ከሳርኮዚ አይን-ጆሮ በሚደርስበት ፍጥነት ከአሜሪካ ሰላዮች ኮምፒዉተር ላይ ይዘረገፍ ነበር።ይሕን በርግጥ ሳርኮዚም፥ ሜርክልም ከኛ እኩል ያወቁት ሰሞኑን ነዉ።NSA በሚል ምሕፃረ-ቃል የሚጠራዉ የአሜሪካ ብሔራዊ የሥለላ ድርጅት ባልደረባ የነበሩት ቶማስ ድራክ እንደሚሉት ሜርክልን መሠለል ዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲን መጣስ ነዉ።

«ይሕ ዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲን ክፉኛ መጣስ ነዉ።ይሕ ለመራሒተ-መንግሥት ሜርክል የግል ጉዳይ ነዉ።የግላቸዉ ተንቀሳቃሽ ሥልክ ነዉ።(ያን መጥለፍ) ለምን አስፈለገ።ከእዉነኛ ጠላትሕ ጋር በምታደርገዉ ዉጊያ የቅርብ ተባባሪሕን?»

ዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲ፥ ዓለም አቀፍ ሕግ በቀዝቃዛዉ ጦርነት ወቅት ነበር።ዛሬም አለ።አንዴም ግን ተከብሮ አያዉቅም።ሕግ፥ ደንብ፥ ሥምምነቱን የሚጥሰዉ ደግሞ ሕግ-ደንቡን ካወጣዉ፥ አስከብረዋለሁ ከሚለዉ ሐያል ዓለም ሌላ ማንም አይደለም።

በቀዝቃዉ ጦርነት ወቅት ልክ እንደ ዓለም አቀፉ ሕግ ደንብ ሁሉ የሞስኮ፥ ቤጂንግ ተባባሪዎች፥ የለንደን-ዋሽግተን፥የቦን ፓሪስ ተሻራኪዎች ጎራ ለይተዉ አንዱ የሌላዉን ሚስጥር ማጭለጉ የፖለቲካዉ ፈሊጥ፥ የስለላዉ ወግ ነበር።

የሐገር መሪዎችን እንቅስቃሴ መከታተል አይደለም መግደል ማስገደልም የፖለቲካ መርሕን የማጠናከር፥ ርዕዮተ-ዓለምን የማዳን-ማስፋፋት ሥልት አካል ነበር።የአሜሪካዉ ማዕከላዊ የሥለላ ድርጅት CIA ሹም ኮሎኔል ጄ ሲ ኪንግ የኩባዉን ኮሚንስታዊ መሪ ፊደል ካስትሮ-ከማስገደል ሌላ ሌላ አመራጭ እንደለሌ የጠቆሙት በ1959 ነበር።

ያኔ ዓለም አቀፍ ማሕበር ዲፕሎማሲ፥ ሕግም ነበር።ዲፕሎማሲ ሕግ፥ ደንቡ የሚረቀቅ፥ የሚወሰን የሚበየነዉ ደግሞ ከኒዮርክ ነበር፥ ከዩናይትድ ስቴትስ ኦፍ አሜሪካ።የአሜሪካዊ ማዕከላዊ የሥለላ ድርጅት CIA ካስትሮን ለማስገደል ስድስት መቶ ሰላሳ-ስምንት ጊዜ ያደረገዉ ወይም አድርጓል የተባለዉ ሙከራ የብዙ መፅሐፍት፥ የዝነኛ ፊልም ርዕሥም ሆኗል።

አያቱላሆች የቴሕራንን ቤተ-መንግሥት ከተቆጣጠሩበት ከ1979 ጀምሮ ኢራን የእስራኤልም፥ የአሜሪካኖችም አሜሪካኖችን የሚመሩት የምዕራቡ ዓለምም ቀንደኛ ጠላት ናት።በሕዝብ የተመረጡት የኢራን ጠቅላይ ሚንስትር መሐመድ ሞስዳቅሕን በ1953 ከስልጣን ያስወገደዉ ማን ነበር? ፓትሪስ ሉምባ እንዴት-እና ማን ገደላቸዉ።ራፋኤል ሊኒዳስ ትሩሔሎስ፥ ንጎ ዲንሕ ዲየምንስ?

ጥያቄዉ-ጥያቄ ይወልዳል እንጂ ማብቂያ የለዉም።ዓለምን የሚመራዉ ግን ዓለም አቀፉ ሕግ ዲፕሎማሲ ሳይሆን የሐያላን ፍላጎትና ፍቃድ መሆኑ ሐቅ ነዉ።የሐያላኑን ፍላጎት ለማስከበር ደግሞ በግልፅ የሚታወቀዉ ሐያላኑ ወዳጅ ከሚሉት ጋር መተባበር መሻረክ መወዳጀታቸዉ ነበር።እስከ 2007 ድረስ በዩናይትድ ስቴትስ ምክር ቤት የስለላ ጉዳይ ኮሚቴ ሊቀመንበር የነበሩት ፔተ ሆክስትራ እንደሚሉት ግን በስለላዉ ዓለም ከወዳጅም-መሐል ተጠርጣሪ ወዳጅ አለ።

«ይሕ ሊሆን የሚችል ይመስለኛል።በስለላዉ ዓለም ፈረንሳዮች፥ ጀርመኖች፥ እስራኤሎች አሜሪካኖች ሁላችንም ጥሩ ወዳጆች ነን።ግን አንዳችን ሌላችንን የምንሠልልበት ጊዜ ሊኖርም ይችላል-የሚል መግባባት ያለ ይመስለኛል።ይሕ (በሰላዮች ዘንድ) በጣም በጣም የታወቀ ነዉ።»

ኮሚንስቶች የሐቫና፥ የሳንዲያጎ፥ የማናጉዋ የሌሎችንም የደቡብ አሜሪካ ሐገራት አብያተ-መንግሥታትን ሲቆጣጠሩ ወይም ለመቆጣጠር ሲያሰጉ የዩናይትድ ስቴትስዋ የቅርብ ጎረቤት፥ ታማኝ፥ ታዛዥነቷን አጓድላ አታዉቅም።ሜክሲኮ።

ከቀዝቃዛዉ ጦርነት በሕዋላ እነ-ሑጎ ሻቬዝ አሜሪካኖችን የሚቃወም ግንባር ለመፍጠር ሲፍጨረጨሩም ያቺ-የአሜሪካ የቅርብ ጎረቤት በታማኝ ታዛዥነቷ እንደፀናች ነበር።ነዉም።ኤንሪክ ፔና ኒቶ ለፕሬዝዳትነት ሲወዳደሩ-ሲመረጡም እንደ ብዙ ቀዳሚዎቻቸዉ ሁሉ ለሐያል፥ ሐብታም፥ ታላቅ ጎረቤታቸዉ ታማኝ ታዥነታቸዉን እንደጠበቁ ነዉ።

በእጩነት ከተመዘገቡ ጀምሮ በምርጫዉ ካሸነፉ-ለሚንስትርነት የሚሾሙ የሚሽሩትን ፖለቲከኛ ስብዕና ማንነት፥ የሚዘረዝር፥ የምርጫ ዘመቻቸዉን ሥልት የሚያትት መልዕክት ለወዳጅ ተከታዮቻቸዉ ኢሜይል ይፅፋሉ። የNSA ሰላዮች ዋሽግተን ቁጭ ብለዉ የሜክሲኮዉን ፕሬዝዳት ኢሜይል ከፕሬዝዳንቱ ደጋፊ፥ተከታዮች እኩል ያነቡ ነበር።የብራዚሏ ፕሬዝዳት የወይዘሮ ዲልማ ሮሴፍ ኢሜዬልም-እንደዚያዉ ነዉ።

አሜሪካዊዉ ሠላይ ኤድዋርድ ስኖደን ሐገር መስሪያ ቤቱን ክዶ ከኮበለለ ወዲሕ የማይሰማ ጉድ የለም።አንዳድ ዘገቦች እንደሚጠቁሙት የሶቬት ሕብረት ኮሚንስቶች በስታሊን ዘመን የሶቬት ሕብረት ሕዝብ ከሚሠልሉት በላይ የአሜሪካ መንግሥት አሜሪካዉያንን ይሰልላል።ለአሜሪካ ሕዝብ ያልራራ ሥርዓት የፈረንሳይ ኩባንያዮችን፥ የስጳኝ ፖለቲከኞችን፥ የዓለምን ሕዝብ የሜክሲኮ፥ የብራዚል፥ የሌሎች ከሰላሳ በላይ መሪዎችን ቢሰልል-በርግጥ ሊያስደንቅ አይገባም።

ያምሆኖ የጀርመንዋ መራሒተ-መንግሥት የሥልክ መልዕክት መጠለፉን ከአዉሮጳ ሕብረት አባል ሐገራት እስከ ሩሲያ መሪዎች ተቃዉመዋል።የጀርመን ፖለቲከኞች የሜርክል ደጋፊም ሆኑ ተቃዋሚዎችም እኩል አዉግዘዉታል።

«እንደሚመስለኝ ይሕ በጀርመን-አሜሪካኖችን ግንኙነት ያለዉን መተማመን ክፉኛ የሚጎዳ ነዉ።መተማመኑ ዳግም ሊገነባ የሚችለዉ እዉነታዉ በግልፅ ወጥቶ ማየን ከቻልን በኋላ ነዉ።

ይላሉ፥-የዋነኛዉ ተቃዋሚ ፓርቲ የSPD የምክር ቤት እንደራሴዎች አስተባባሪ ቶማስ ኦፐርማን ።ሥለ ጀርመን እና ጀርመንን የሚመለከቱ መረጃዎችን የመሰብሰብ መከታተሉ ሐላፊነት የጀርመን የሥለላ ድርጅት ነዉ።ቡንደስ ናሕሪሽተን ዲንስት።BND በጀርመንኛ ምሕፃሩ። የስለላዉን ድርጅት በበላይነት የሚያስተዳድርና የሚመራዉ ደግሞ የጀርመን ፌደራዊ የሐገር ዉስጥ ጉዳይ ሚንስቴር ነዉ።

የሐገር ዉስጥ ጉዳይ ሚንስትር ሐንስ ፔተር ፍሬድሪሽ ግን የመሪያቸዉን መሰለል እንደማንኛዉም ሰዉ ከመገናኛ ዘዴዎች የሰሙ ያክል ነዉ-የተቆጡት።

«ከአሜሪካኖች ጋር በዚሕ ሁኔታ አንሰራም።መተማመኑ ተበላሽቷል።እና እንደሚመስለኝ የተበላሸዉን መተማመን ለመጠገን ሁነኛ እርምጃ መወሰድ አለበት።»

አሜሪካዊ እንደራሴና የሥለላ ጉዳይ አዋቂ ፔተ ሆክስትራን የሚያስደንቀዉ ግን የአሜሪካ ሰላዮች የጀርመንዋ መራሒተ-መንግሥትን ስልክን መጥለፋቸዉ አይደለም።የነፍሬድሪሽ ቁጣና ብስጭት እንጂ።ሆክስትራ እንደሚሉት ካስደነቀ-የሚያስደንቀዉ የጀርመን መሪ ሥልክ መጠለፉን ፍሬድሪሽ የሚመሩት የጀርመን የስለላ ድርጅት አለማወቁ ነዉ።

«የዋሕነት ይመስለኛል።የጀርመን መንግሥት (ባለሥልጣናት) በወዳጆቻቸዉ ሊሰለሉ እንደሚችሉ ማወቅ ነበረባቸዉ።ነገሩ ከተፈፀመ አስደናቂዉ ነገር የሚመስለኝ፥ (ሥለላዉን) ለማስቆም የጀርመን የስለላ ማሕበረሰብ አስፈላጊዉ አፀፋ-እርምጃ አለመዉሰዱ ነዉ።»

የጀርመንዋ መራሒተ-መንግሥት ስልክ መጠለፉ-መሰላላቸዉም እርግጥ ነዉ።ሜርክል መሰለላቸዉን ፕሬዝዳት ባራክ ኦቦማ ያዉቃሉ-አያዉቁም እያነጋገረ ነዉ።ካወቁ ከመቼ ጀምሮ የሚለዉም ያጠያይቃል። እራሳቸዉ ሜርክል እና የፈረንሳዩ ፕሬዝዳት ፍራንሷ ኦሎንድ የአዉሮጳ ሕብረት ወክለዉ ለኦባማ አቤቱታ ያቀርባሉ። ወደ አንድ ሺሕ የተገመቱ አሜሪካኖች በመንግሥታቸዉ መሠለላቸዉን በአደባባይ ሠልፍ አዉግዘዋል።አቤቱታ፥ ተቃዉሞ፥ ዉግዘት፥ ሰልፉ ምናልባት ይቀጥል ይሆናል፥ መሳለል-መጠላለፉ ያስቆመዋል ባይ ግን የለም።ምክንያት፥-ድሮ እንዲያ ነበር፥ ዛሬ እንዲያ ነዉ።ነገም።በዚሕ ዝግጅት ላይ ያላችሁን አስተያየት ላኩል። ማሕደረ ዜና ቢቃኘዉ ጥሩ ነዉ ብላችሁ የምትገምቱትን ወቅታዊ፥ ብሔራዊ፥ዓለም አቀፋዊ ጉዳይ በተለመደዉ አድራሻችን ጠቁሙን።ለዛሬዉ ነጋሽ መሐመድ ነኝ ቸር ያሰመን።

Titel: Demonstration #stopwatchingus gegen NSA und Überwachung in Washington, DC, USA Schlagworte: NSA, Überwachung, Demonstration, stopwatchingus Wer hat das Bild gemacht?: Monika Griebeler Wann wurde das Bild gemacht?: 26.10.2013 Wo wurde das Bild aufgenommen?: Washington, DC, USA
ተቃዉሞምስል DW/M. Griebeler
US-Bürger demonstrieren am 24.10.2013 nahe dem Kapitol in Washington DC gegen die Überwachung durch Geheimdienste wie die NSA. (Foto: Monika Griebeler / DW) - eingestellt von Andreas Grigo
ተቃዉሞምስል DW
ILLUSTRATION - Ein iPhone, auf dem der fiktive Name Angela Merkel zu sehen ist, liegt am 25.10.2013 in München (Bayern) auf einem Logo der NSA (National Security Agency). Nach Hinweisen auf eine Überwachung des Handys von Bundeskanzlerin Merkel (CDU) durch US-Geheimdienste haben Politiker aller Parteien umgehende Aufklärung gefordert. Foto: Sven Hoppe/dpa
ምስል picture-alliance/dpa
ARCHIV - US-Präsident Barack Obama (r) wischt sich am 19.06.2013 den Schweiß von der Stirn neben Kanzlerin Angela Merkel auf einem Podium vor dem Brandenburger Tor am Pariser Platz in Berlin. Foto: Marcus Brandt/dpa (zu dpa "Obama war angeblich in NSA-Abhörattacken gegen Merkel eingeweiht" vom 27.10.2013) +++(c) dpa - Bildfunk+++
ተሠላይና አሰላይምስል picture-alliance/dpa

ነጋሽ መሐመድ

አርያም ተክሌ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ