1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሰሜን ኮሪያና ዩናይትድ ስቴትስ

ሐሙስ፣ የካቲት 22 2004

በኑክሌር ቦምብ መስራት ሰበብ ለበርካታ አመታት እየጦዘ-የሚረግበዉ የሰሜን ኮሪያና የዩናይትድ ስቴትስ ዉዝግብ፥አተካራ ሰሞኑን የመርገቢያዉ ተራ የደረሰ መስሏል።የሁለቱ ሐገራት ባለሥልጣናት ባደረጉት ድርድር ሰሜን ኮሪያ የኑክሌር ቦምብ የመሥራት

https://p.dw.com/p/14ClC
የሰሜን ኮርያ የኑክልየር አርማምስል AP

እንቅስቃሴዋን ለተወሰነ ጊዜ ልታቆም፥ ዩናይትድ ስቴትስ ደግሞ ለሰሜን ኮሪያ ርዳታ ልትሰጥ ተስማምተዋል።ስምምነቱ በየጊዜዉ እየተደረገ ከሚፈርሰዉ ተመሳሳይ ስምምነት የተለየ አይደለም።ታዛቢዎች እንደሚሉት ስምምነቱ ትንሽ ግን ለመስማማት የመስማማት ምልክት ነዉ።ሸዋዬ ለገሰ የዋሽግተኑ ወኪላችን አበበ ፈለቀን አነጋግራዋለች።--

-----

አዲሱ የሰሜን ኮርያ አመራር ማዕድኑን ዩሬንየምን የማብላላት ተግባሩን እና የኑክልየር እና የረጅም ጦር መሣሪያ ሙከራ ለማቋረጥ፡ እንዲሁም፡ የተመድ ተቆጣጣሪዎች ስምምነቱ መከበሩን እንዲቆጣጠር ዝግጁ መሆኑን አስታወቀ። ቻይና፡ ጃፓን፡ ደቡብ ኮርያ፡ የተመድ እና የአውሮጳ ህብረት ይህንኑ የፒዮንግያንግ ርምጃ አሞግሰዋል። ሰሜን ኮርያ ይህን ውሳኔ የደረሰችው ተደራዳሪዎችዋ ባለፈው ሣምንት ከዩኤስ አሜሪካ ጋ ከተወያዩ በኋላ ነው። በምላሹ ዩኤስ አሜሪካ ለሰሜን ኮርያ ሰብዓዊ ርዳታ እንደምታቀርብ አስታውቃለች። የዩኤስ አሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ሂለሪ ክሊንተን የውይይቱን ውጤት ቢያደንቁም፡ ተግባራዊነቱን ጠብቆ ማየት አስፈላጊ እንደሚሆን ገልጸዋል።
« የዛሬው ማስታወቂያ ወደ ትክክለኛው መንገድ የሚያመራ የመጀመሪያ አነስተኛ ርምጃ ነው። እኛ በርግጥ ሂደቱን በቅርብ እንከታተላለን፤ ስለ አዲሱ የሰሜን ኮርያ አመራር የሚኖረን አመለካከትም በተግባሩ ይወሰናል። » ሰሜን ኮርያ በአከራካሪው የኑክልየር መርሀግብርዋ ሰበብ የተፈጠረውን ውዝግብ ለማብረድ አሁን ያሳየችው ዝግጁነት ግን በሁለቱ የኮርያ መንግሥታት እና በቻይና፡ በጃፓን፡ በሩስያና በዩኤስ አሜሪካ መካከል የስድስትዮሹ ድርድር ይቀጥላል ማለት አለመሆኑን የፖለቲካ ታዛቢዎች አስታውቀዋል። ከሰሜን ኮርያ የተገኘውን አዎንታዊ ርምጃን ተከተሎ የተመድ ዋና ፀሐፊ ፓን ኪ ሙን በሰጡት መግለጫ ውዝግቡ የሚመለከታቸው ወገኖች ሁሉ ሰላማዊ መፍትሔ እንዲያፈላልጉ ጥሪ አቅርበዋል።

አበበ ፈለቀ

ሸዋዬ ለገሠ