1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሰፊ ህዝባዊ ተቃውሞ በካይሮ

ዓርብ፣ ነሐሴ 10 2005

ግብፅ ውስጥ ከዛሬው የዕለተ ዓርብ (ጁምዓ) ጸሎትና ስግደት በኋላ አዲስ የተቃውሞ ማዕበል የተቀሰቀሰ ሲሆን፤ ከካይሮ በስተሰሜን 130 ኪሎሜትር ራቅ ብሎ በሚገኘው ፣ ካፍር ኧል ሼክ በተሰኘው ክፍለ ሀገር፣ በፖሊስና በታጠቁ የሙስሊም ወንድማማች ማኅበር ደጋፊዎች በተደረገ ግጭት 10 ሰዎች ሲሞቱ ከዚያ ቁጥራቸው ከፍ ያለ ቆስለዋል።

https://p.dw.com/p/19Q68
ምስል Reuters

ከካይሮ በስተደቡብ፣ ፋዩም በተሰኘችው ሌላ ከተማ 5 ሰዎች ተገድለዋል። ከሥልጣን የተወገዱት ፕሬዚዳንት ሙሐመድ ሙርሲ ደጋፊዎች፤ የዛሬው ዕለት «ቁጣ የሚገለጽበት ቀን» ነው ሲሉ ማስታወቃቸው ተነግሮአል። ከ 2 ቀናት በፊት ካይሮ ውስጥ፤ ጦር ኃይሉ ፣ 2 የተቃውሞ ምሽጎችን በኃይል ሲያፈራርስ ከ 600 በላይ ሰው መገደሉና በሺ የሚቆጠሩ መቁሰላቸው ተነግሯል።
ቀደም ሲል ፣የሙርሲ ተቃዋሚዎች ጭምር አደባባይ እንደሚወጡ የተነገረ ሲሆን፤ የሀገር አስተዳደር ሚንስቴሩ፣ ፖሊስ በጥይት መጠቀሙ አይቀርም ሲል አስጠንቅቆ እንደነበረ ተመልክቷል።
በግብፅ የኃይል እርምጃ ለረጅም ጊዜ ሲካሄድ የሚቆይ ጉዳይ ይሆን? ስለ እስልምና ሳይንሳዊ ምርምር ያደረጉት ፤ ጀርመናዊው ምሁር ዑዶ ሽታይንባኽ--

Ägypten Räumung des Mursi Anhänger Lagers in Kairo 14. August 2013
ምስል Reuters


«አዎ፤ የኃይል እርምጃ ይቀጥላል። በዚህ ላይ ወደ ሲና ልሳነ-ምድር በማፈግፈግ በዚያ የሚመሽጉ ያኖራሉ። በትክክል እነማን ይሆናሉ ማወቅ ያስቸግራል። የሚታወቅ ቢኖር፤ በዛ ያሉ አክራሪዎች ፣ የግብፅን መንግሥትና እሥራኤልን የመውጋት አጀንዳ ያላቸው መኖራቸውን ነው። እነዚህም ወገኖች አሁን ተጨማሪ አጠናካሪ ድጋፍ ማግኘታቸው አይቀርም።» ይህ በአንዲህ እንዳለ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታ ጥበቃው ም/ቤት ፤ በግብፅ የተፈጸመውን የኃይል እርምጃ አውግዟል።
ብዙ ሰዎች የተገደሉበትን ድርጊት ፣ ከሰሞኑ ካወገዙት የዓለም መሪዎች መካከል፣ የዩናይትድ እስቴትስ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ይገኙበታል።
«ዩናይትድ ስቴትስ ፣ የግብጽ የሽግግር መንግሥትና የጸጥታ አስከባሪ ኃይሎች የወሰዱትን ርምጃ በጥብቅ ታወግዛለች። በሲብሎች ላይ የተወሰደው የኃዕል እርምጃ አሳዝኖናል። ለሰብአዊ ክብር መሠረት የሆነውን ዓለም አቀፍ ሰብአዊ መብት እንደግፋለን። በሰላማዊ መንገድ ተቃውሞ ማሳየትን ጭምር!የሲቭሎችን መብት፣ ግለሰባዊ ነጻነትን ፤ በፀጥታ ማስከበር ስም የሚደፈልቀውን ወታደራዊ አዋጅን የሙጥኝ ማለትን እንቃወማለን። ዩናይትድ እስቴትስ፣ የቤተሰብ አባሎቻቸው የተገደሉባቸውን፣ እንዲሁም የቆሱሉባቸውን መጽናናት ይስጣቸው ትላለች። »

Ägypten Räumung des Mursi Anhänger Lagers in Kairo
ምስል picture-alliance/dpa


ይህ በእንዲህ እንዳለ ፤ በስልክ ሐሳብ የተለዋወጡት፣ የጀርመን መራኂተ-መንግሥት አንጌላ ሜርክልና የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ፍራንሷ ዖላንድ፣ የአውሮፓው ኅብረት ውጭ ጉዳይ ሚንስትሮች፣ በመጪው ሳምንት ተሰብስበው ፤ ኅብረቱ በምን ዓይነት ሁኔታ ከግብፅ ጋር ትብብር እንደሚኖረው ይመክሩ ዘንድ ፍላጎታቸው መሆኑን አስታውቀዋል። ሁለቱ መሪዎች ሁከት ባስቸኳይ ተግትቶ፤ ሁሉንም ግብጻውያን የሚወክል ውይይት እንዲጀመር ማሳሰባቸውም ተመልክቷል ።
ጀርመን በተጨማሪ ፤ ዜጎቿ ፣ ለዕረፍት ወደ ግብፅ ዝር እንዳይሉ አስጠንቅቃለች።

የግብፅ የፖለቲካ ኃይሎች ሁሉ፤ ወደ ውይይት መድረክ እንዲመለሱና የሚስፋፋውን የኃይል እርምጃ ለመግታት እንዲደራደሩ ጥሪ እንስተላልፋለን። ከእንግዲህ ፣ በግብጽ ተጨማሪ ደም እንዳይፈስ መገታት ይኖርበታል። »

የተቃውሞ ሰልፈኞችና የፀጥታ አስከባሪ ኃይሎች፤ ለተወሰደው የኃይል እርምጃ፤ አንዱ ሌላኛውን ጥፋተኛ ብሏል። የሀገር አስተዳደር ሚንስቴር በፖሊስ ላይ ተኩስ የከፈቱት የተቃውሞ ሰልፈኞች ናቸው ባይ ነው። የሙስሊም ወንድማማች ማኅበር በበኩሉ ፣ ጭፍጨፋ ነው የተካሄደው ብሏል።

የግብፅ የሽግግር መንግሥት፣ በሀገሪቱ በመላ ሁከት ማገርሸቱን መንስዔ በማድረግ ፣ የአንድ ወር የአስቸኳይ ሁኔታ አዋጅ ማውጣቱን አስታውቋል።

ተክሌ የኋላ

ሂሩት መለሰ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ