1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ስጋት ላይ የወደቀዉ የአፍሪቃ የኤኮኖሚ አንቀሳቃሽ ሞተር

ቅዳሜ፣ ኅዳር 13 2007

የጀርመኑ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፍራንክ ቫልተር ሽታይንማየር የጀርመን የቅርብ አጋር የሆነችዉን አፍሪቃዊት ሃገር ደቡብ አፍሪቃን ጎብኝተዋል። በደቡብ አፍሪቃ የጀርመኑ ኢንዱስትሪ ዘርፍ የኤኮኖሚ አለመመረጋትና ደካማ ጎኖች አሉት በሚል ስጋት ላይ በመዉደቁ፤ የጀርመን የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር የፍራንክ ቫልተር ሽታይን ማየር ላይ ከፍተኛ ተስፋ ተጥሎአል።

https://p.dw.com/p/1DrYq
Bundesaußenminister Frank-Walter Steinmeier in Südafrika
የጀርመኑ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፍራንክ ቫልተር ሽታይንማየርምስል picture-alliance/dpa

ስጋት ላይ የወደቀዉ የአፍሪቃ የኤኮኖሚ አንቀሳቃሽ ሞተር በሚል የዶቼ ቬለዉ ክላዉስ ሽቴከር ከፕሪቶርያ በላከዉ ዘገባ የጀርመኑ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፍራንክ ቫልተር ሽታይን ማየር በደቡብ አፍሪቃዉ ጉብኝታቸዉ አንድ ምልክትን ማሳረፍ እንደሚፈልጉ በዘገባዉ አትቶአል።

የጀርመኑ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፍራንክ ቫልተር ሽታይንማየር ወደ ደቡብ አፍሪቃ ጎራ እንደሚሉ ሳይሰማ ነዉ፤ ጉብኝታቸዉን በድንገት የጀመሩት። የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከፕሪቶርያ ብዙም ከማይርቀዉ « ዋተር ክሎፍ» በተሰኘዉ የጦር አዉሮፕላን ማረፍያ ሲደርሱ በደቡብ አፍሪቃ እንደተለመደዉ፤ አንድ ታዋቂ ፖለቲከኛ በፖሊስ አቀባበልና አጃቢ እንደሚኖረዉ ሁሉ፤ የጀርመኑ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሽታይና ማየር አጃቢ ፖሊሶች አልነበሩዋቸዉም፤ አልመጣላቸዉምም። የዚህ ምክንያቱ ምን ይሆን? የአሰራር ጉድለት ወይስ ደቡብ አፍሪቃ ከቻይናና ከ«BRICS» ማለት በኤኮኖሚ በማደግ ላይ የሚገኙት የአምስቱ ሀገራት ጥምረት ሃገራት መንግስታት ጋር ያለዉ ግንኙነት የተሻለ ሆኖ በመገኘቱ? እንድያም ሆኖ የጀርመኑ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፍራንክ ቫልተር ሽታይን ማየር ይህን ሁኔታ ትልቅ ትኩረት አልሰጡትም። ምንም እንኳ ሽታይን ማየር እየሩሳሌም እና ሞስኮ ላይ የሚደርጉት ድርድር አንዱ መረሃ-ግብራቸዉ እንዲሁም ስለኢራን የአቶም ጉዳይ ለመደራደር ወደ ቬና መሄድ ቢኖርባቸዉም የአፍሪቃዉን ጉዳይ በማስቀደም ወደ አፍሪቃ ተጉዘዋል። በግዜ እጥረት ምክንያት ወደ ኬንያ፤ ኮንጎ እና ሩዋንዳ አቅደዉንት የነበረዉን ጉዞ ቢሰርዙም ወደ ደቡብ አፍሪቃ መጓዛቸዉን እንደ ተጠበቀ ሆኖ ወደ ደቡብ አፍሪቃ አቅንተዋል። ጀርመን አጋሮችዋ ከሆኑት የአፍሪቃ ሃገራት መካከል ለደቡብ አፍሪቃ ቀዳሚዉን ቦታ ሰታለች። ሽታይን ማየር በዚህ ጉዞአቸዉ በድጋሚ የገለፁት ባለፈዉ ግዜ የነበረዉ አሰራር መቀየር እንዳለበት ነዉ። ማለትም አስቸኳዩ ጉዳይ የአዉሮጳና የጀርመን ከአፍሪቃ ጋር ያለዉ ወዳጅነት ቅድምያ ሊሰጠዉ ይገባል ነዉ ያሉት። ስለዚህም ምንም እንኳ የጊዜ እጥረት ቢኖርባቸዉም ወደ ደቡብ አፍሪቃ መምጣታቸዉ በድጋሚ ገልፀዋል። « በእዉነቱ ከሆነ አሁን አሁን ወደ አፍሪቃ መጓዝ ያስፈልጋል አያስፈልግም የሚለዉ ጥያቄ መታሰቡ አይቀርም ። ግን እንደኔ እንደኔ ቀደም ሲልም ሁኔታዉ እንዲሁ ነበር። ሁሌም ቢሆን አዉሮጳና ጀርመን ከአፍሪቃ ጋር ካላቸዉ ግንኙነት ይልቅ ለሌላዉ ነበር ክብደት ይሰጠዉ ነበር። እንደኔ እምነት ይህን አያያዝና ሁኔታ መቀየር ይኖርብናል። ለዚህም ነዉ በዚህ ግዜ ወደ አፍሪቃ መጓዝ ያስፈለገዉ። »

Deutschland Präsident des Markenverbands Franz-Peter Falke
የካልሲ እና ስቶኪንግ ፋብሪካ ፔተር ፋልከ ዋና ተጠሪምስል picture-alliance/dpa/W. Kumm

ሽታይን ማየር በደቡብ አፍሪቃ በሚያደርጉት ጉብኝት በሁለቱ ሃገራት መካካል ያለዉን ግንኙነት በአዲስ መልክ ለማጠናከር አቅደዋል። «ባለፉት ዘመናት አዉሮጳም ሆነች ጀርመን ከአፍሪቃ ጋር ያላቸዉ ግንኙነት ሌላ መልክና ባሕሪ ነበረዉ ያሉት ሽታይን ማየር እንዲሕ አይነቱ አስተሳሰብ ባሁኑ ወቅት መለወጥና መወገድ አለበት ብለዋል። በዚሕ ወቅት በአፍሪቃ የማደርገዉ ጉብኝትም በአዲሱ መንፈስ ላይ የተመሠረተ ነዉ» ሲሉ ሽታይን ማየር አክለዋል።

የጀርመኑ ዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሽታይን ማየር በጆሃንስበርግ በሚገኙ የጀርመን ባለወረቶች ፊት ቀርበዉ ባደረጉት ንግግር የጀርመን ደቡብ አፍሪቃ ባህላዊ ትስስርን አወድሰዋል። የጀርመኑ የሲመንስ ድርጅት በኬፕታዉን ከተማ በ 160 ዓመታት ጥሩ ተስፋን ማሳየቱም ተመልክቶአል። በደቡብ አፍሪቃ 600 የጀርመን ባለወረቶች የተለያዩ ድርጅቶችን ያቋቋሙ ሲሆን ድርጅቶቹ ለ 90 ሺ ሰራተኛ የስራ እድልን ፈጥረዋል። ጀርመን ለደቡብ አፍሪቃ ከቻይና ቀጥላ ዋንኛ የንግድ አጋር ሀገር መሆንዋም ይታወቃል። ደቡብ አፍሪቃ ለጀርመን ባለወረቶች አማላይ ናት ሲሉም ሽታይንማየር በንግግራቸዉ ሀገሪቱን አሞካሽተዋል። እንዲያም ሆኖ በስምምነት ረገድ ደቡብ አፍሪቃ ላይ እንከን መታየቱ አልቀረም። የጀርመን የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሽታይን ማየር ጉብኝት ላይ የተጠበቁት የጉታንግ አዉራጃ ተጠሪ ጊዜ በማጣታቸዉ ምክንያት ተወካይን ነበር የላኩት። ይህ ታድያ አጋር ሃገር ጀርመንን ከማክበር ረገድ እንዴት ይታይ ይሆን?

በደቡብ አፍሪቃ የጀርመን ባለወረቶች ማኅበር በሃገሪቱ በሚታየዉ የፖለቲካ አለመረጋጋት ምክንያት መዋለ ንዋይ ለማፍሰስ ችግር ፈጥሯል ሲሉ ቅሪቸዉን ያሰማሉ። ጃኮብ ዙማ የሚመሩት የደቡብ አፍሪቃ መንግሥት የሃገሪቱን የኤኮኖሚ ፖሊሲ በተሳሳተ አቅጣጫ እየመራ ነዉ» ሲል በደቡባዊዉ አፍሪቃ የጀርመን የኤኮኖሚን አንቀሳቃሽ ተቋም በጽህሮቱ «ሳፋሪ» ወቀሳዉን ያሰማል። ሳፍሪ በአረቀቀዉ ጽሑፍ ጎታች ናቸዉ ያላቸዉን ሰባት እክሎች ጠቅሶአል። ከነዚህ መካከል ደግሞ አዲስ የፀደቀዉ የጥገኝነት ህግ ይገኝበታል። ሌላዉ በሃገሪቱ የባለወረቶች ስራን በተገቢ መመርያዎች አለመጠበቁ ነዉ። የጀርመን መንግስት በአፍሪቃ በሚገኙ 39 ሃገራት ለባለወረቶች ከለላ ለመስጠት የሁለትዮሽ ስምምነትን መድረሱ ይታወቃል። ከአንድ ዓመት ግን በፊት ደቡብ አፍሪቃ ይህን ዉል አፍርሳለች። ሃገሪቱ በምትኩ ያፀደቀችዉ የብሄራዊ ህግ ደግሞ ከዉጭ ለሚመጡ ባለወረቶች ከፍተኛ ፈተናና አደጋን መደቀኑ ነዉ የተነገረዉ።

የካልሲ እና ስቶኪንግ ፋብሪካ ፔተር ፋልከ ተጠሪ እንደሚሉት በዚህ ረገድ የአሰራር ሂደት ስህተት እንዳለ አመላካች ነዉ። «ይህ በእዉነቱ አስደንጋጭ ምልክት ነዉ። በርካታ ባለወረቶች በደቡብ አፍሪቃም ሆነ በሌሎች የአፍሪቃ ሃገራት ገንዘብን አፍሰዋል። በደቡብ አፍሪቃ በማዕከላዊነት መንቀሳቀስ የሚፈልጉት ግን በአንፃሩ እጅግ ስጋት ላይ ወድቀዋል፤ እናም ስራ ላይ ያዋሉትን ወረታቸዉን ይዘዉ መመልስን ነዉ የሚሹት» በኬፕታዉን የሚገኘዉ ፋክቶ የተሰኘዉ ካልሲና ስቶኪንግ አምራቹ ድርጅት ስራዉን ከጀመረ 45 ዓመታትን አስቆጥሮአል። በሀገሪቱ አሁን እንደሚታየዉ የአሰራር አካሄድ ከሆነ አምራች ድርጅቱ ብዙም ዘለቂታዊ ስራን ባልያዘ ነበር።

የፖለቲካ አለመረጋጋት ለጭንቀት መፈጠር ምክንያት ነዉ። ከጥቂት ቀናቶች በፊት አንድ የምክር ቤት አባል ፕሪዚደንት ዙማን «ሌባ» በማለቱና የምክር ቤት ፕሪዚዳንትዋን በትክክል ሳይጠራ በመቅረቱ ብሔራዊ ምክር ቤት ስብሰባ ላይ ታጣቂ ፖሊሶች ተገኝተዉ ሊያስወጡት መጥተዉ እንደነበር ተገልጾአል። በደቡብ አፍሪቃዉ 20 ኛ ዓመት ዲሞክራሲ ይህን ማየት እጅግ አስደንጋጭ ነዉ ሲሉ በደቡብ አፍሪቃ ምክር ቤት ህገ መንግስታዊ እድገት ጉዳይ ተመልካች እና የሰብዓዊ መብት ተሟጋቹ ላዉሶን ናይዶዉ ገልፀዋል። የማንኛውም ባለወረት ተቀዳሚ ትኩረት፣ አንድ ሀገር የፖለቲካዊ ሁኔታው የተረጋጋ መሆኑ ላይ ነዉ። እኛ መስቀለኛ መንገድ ላይ ቆመን ነዉ ያለነዉ ። የታጠቁ ፖሊሶች ወደተከበረው የፓርላማ አዳራሽ ገብተዉ አንድ የፓርላማ አባልን ሲያስወጡ ማየት በጣም ከፍተኛ ስጋት ላይ ይጥላል። እንዲህ ዓይነቱን ነገር በኛ ዲሞክራሲያዊ ማኅበረሰብ እናያለን ብለን መቼም አስበነዉ አናዉቅም»

Südafrika Parlament in Cape Town Screenshot Chaos
በደቡብ አፍሪቃ ብሔራዊ ምክር ቤት ስብሰባ ላይ ታጣቂ ፖሊሶች የታዩበት ምስልምስል YouTube

የጀርመን ባለወረቶች እና የደቡብ አፍሪቃ የሲቢል ማኅበረሰብ በጋራ የደቡብ አፍሪቃ የኤኮኖሚ ይዞታ ያሳስባቸዋል። ይሄም የፖለቲካ ዉይይት ላደረጉት የጀርመን የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፍራንክ ቫልተር ሽታይንማየር ግልፅ መልክት ሆኖ ቀርቦላቸዋል። የሰብዓዊ መብት ተሟጋቹ ላዉሶን ናይዶ በበኩላቸዉ በደቡብ አፍሪቃ ብሩህ መፃይ እድል መኖሩን ነዉ የተናገሩት።እንደ ላዉሶን ናይዶ የኔልሰን ማንዴላና የዴዝሞን ቱቱን ራዕይ እዉን ለማድረግ የደቡብ አፍሪቃ ዴሞክራሲ ከ 20 ዓመት ወዲህም ቢሆን እንደብረት ጠንክሮ ነዉ የሚገኘዉ። ስለሆነም ጠንካራዉ ኤኮኖሚ አንዳንዴ በሚዋዥቀዉ የፖለቲካ አካሄድ መጽናናቱ አይቀሪ ነዉ።

ፍራንክ ቫልተር ሽታይን ማየር በደቡብ አፍሪቃ በሚያደርጉት ጉብኝት ከፖለቲካ አቻዎቻቸዉ ጋር በሚያደርጉት ዉይይት ስጋት ባልዋቸዉ ነጥቦች ላይ እንደሚነጋገሩ ገልፀዋል። በደቡብ አፍሪቃ የሚገኙት የፋልከ ቡድን የካልሲና ስቶኪንግ አምራች ድርጅት ፋራንዝ ፒተር ፋልክ ተጠሪ በበኩላቸዉ ሚኒስትሩ የሰከነ አቋምና ተግባር ዉጤታማ እንደሚያደርግ መተማመናቸዉን ገልፀዋል። የጀርመኑ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፍራንክ ቫልተር ሽታይን ማየር በጉብኝታቸዉ ደቡብ አፍሪቃ፤ አፍሪቃ ዉስጥ ሠላም ለማስፈን የምታደርገዉ ጥረት በጣም ጠቃሚ እና አበረታች መሆኑን አስታዉቀዋል። እንደ ሽታይንማየር ደቡብ አፍሪቃ ከኮንጎ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ እስከ ሱዳን ያሉ ግጭቶችን ለማስወገድ ከፍተኛ አስተዋፅኦን እያደረገች ነዉ። ሽታይን ማየር በደቡብ አፍሪቃ በሚያደርጉት ጉብኝት በሁለቱ ሃገራት መካካል ያለዉን ግንኙነት በአዲስ መልክ ለማጠናከር እቅድ መያዛቸዉም ተገልፆአል።

አዜብ ታደሰ

ተክሌ የኋላ