1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በስጳኝ በተፈጸመው ጥቃት 14 ሰዎች ተገድለዋል፤ወደ መቶ ገደማ ቆስለዋል

ዓርብ፣ ነሐሴ 12 2009

ስጳኝ በባርሴሎና ከተማ የራስ ራምባላስ አውራ ጎዳና በተሽከርካሪ 13 ሰዎችን በመግጨት ገድሏል ተብሎ የሚጠረጠረዉ የ18 ዓመት ታዳጊ ሳይገደል እንዳልቀረ ተዘገበ። ተጠርጣሪው ሙሳ ኡካቢር አገር ጎብኚዎች በሚያዘወትሩት ጎዳና ሰዎችን ለመግጨት የተጠቀመበትን ተሽከርካሪ በወንድሙ ሰነዶች ሳይከራይ አልቀረም ተብሏል።

https://p.dw.com/p/2iU1X
Barcelona Anteilnahme mit Opfern des Anschlags
ምስል picture alliance/ZUMAPRESS.com

የሽብር ጥቃት በባርሴሎና

 ፖሊስ ከጥቃቱ ጋር ግንኙነት ሳይኖራቸው አይቀርም ያላቸውን አራት ግለሰቦች በቁጥጥር ሥር አውሏል። ትናንት ምሽት በተፈጸመው ጥቃት 14 ሰዎች ሲሞቱ ወደ አንድ መቶ ገደማ ቆስለዋል። የጥቃቱ ሰለባዎች ከ30 በላይ የሚሆኑ አገራት ዜጎች ናቸው። ለባርሴሎናው ጥቃት ራሱን "እስላማዊ መንግሥት" ብሎ የሚጠራው ታጣቂ ቡድን ኃላፊነት ወስዷል። ጥቃቱን ያወገዙት የስፔኑ ጠቅላይ ሚኒሥትር ማርያኖ ራኾይ የሦስት ቀናት ብሔራዊ ሐዘን አውጀዋል። የጠቅላይ ሚኒሥትሩን ውግዘት የተለያዩ አገራት መሪዎችም ተጋርተዋቸዋል። የሐዘን መግለጫ መልዕክት ትናንት ምሽት ልኪያለሁ ያሉት የጀርመኗ መራሒተ-መንግሥት አንጌላ ሜርክል ጥቃቱን አውግዘዋል።
"እነዚህ ደም አፍሳሽ ጥቃቶች የእስላማዊ ሽብርተኝነት ለሰዎች ያለውን አጠቃላይ ጥላቻ በድጋሚ አሳይተውናል። በዚህ ሰዓት ስፔናውያን ፤ጀርመኖች እና ነፃ ሰዎች ሁሉ ምን ያክል ምን ያክል የተሳሰርን እንደሆንን ተሰምቶናል። በመጀመሪያ ደረጃ በእንዲህ ያለ ቆንጆ በጋ ምን አልባትም በእረፍት ቀናቸው ሰዎች ህይወታቸው በመነጠቃቸው በጥልቅ ሐዘን ተሳስረናል።"

የስጳኝ ፖሊስ በካምብሪልስ ከተማ ዛሬ ማለዳ በሌላ ተሽከርካሪ ጥቃት የፈጸሙ አምስት ተጠርጣሪዎችን ተኩሶ መግደሉን አስታውቋል። ከሟቾቹ አንዱ ትናንት ባርሴሎና ዉስጥ ሰዎችን በመኪና ገጭቶ የገደለና ያቆሰለዉ ወጣት እንደሆነ ስጳኝ መገናኛ ዘዴዎች ዘግበዋል።ፖሊስ እንደሚለው ተጠርጣሪዎቹ ሰባት ሰዎች በተሽከርካሪ ገጭተው ሲያቆስሉ ከተጎጂዎች መካከል አንዲት ወ/ሮ ቆየት ብሎ ህይወታቸው አልፏል። በተጠርጣሪዎቹ ተሽከርካሪ ውስጥ መጥረቢያ፤ ስለት እና የሐሰት የቀበቶ ፈንጂ ማግኘቱን ፖሊስ ጨምሮ ገልጧል። በዚያው በስፔን አልካናር የተባለች ከተማ ቦምብ ፈንድቶ አንድ ሰው የሞተ ሲሆን ከሁለቱ ጥቃቶች ጋር ስለመገናኘቱ ለማወቅ ባለሥልጣናት ምርመራ ላይ ናቸው። የካታሎኒያ ፖሊስ ተጠርጣሪዎቹ መጠነ-ሰፊ ጥቃት የመፈጸም እቅድ ነበራቸው ብሏል።