1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሶማሊያና የፖለቲካ ተንታኞች አስተያየት

ረቡዕ፣ የካቲት 23 2003

«መታወቅ ያለበት ሞቃዲሾ ዉስጥ ጠንካራ ማዕከላዊ መንግሥት መመሥረት በሶማሊያ ሁኔታ አይሠራም።የሚያስፈልገዉ ሥልጣኑን ለአካባቢ መስተዳድሮች የሚያጋራ መንግሥት ነዉ።የሽግግር መንግሥቱ ማድረግ ያለበትም ይሕንን ነዉ

https://p.dw.com/p/R5jO
የሸሪፍ መንግሥት «ያጣጣራል»ምስል AP

የሶማሊያ የሽግግር መንግሥት ሥልጣኑን ለአካባቢ አስተዳደሮች ካላጋራ በቀላሉ እንደሚወድቅ Crisis Group የተሰኘዉ አለም አቀፉ የፖለቲካ ጥናንት ተቋም አስጠነቀቀ።ተቋሙ ባለፈዉ ሳምንት ይፋ ባደረገዉ ጥናቱ እንዳስታወቀዉ ከፊል ሞቃዲሾን ብቻ የሚቆጣጠረዉ ሶማሊያ የሽግግር መንግሥት አሁን ባለበት ሁኔታ መቀጠሉ አጠራጣሪ ነዉ።በCrisis Group የአፍሪቃ ቀንድ ጉዳይ ሐላፊ ኢጄ ሆኽንዶርም እንደሚሉት የሽግግር መንግሥቱ ሥልጣኑን ለአካባቢ መስተዳድሮች ያጋራ ዘንድ አለም አቀፉ ማሕበረሰብ ግፊት እንዲያደርግበትም ጠይቀዋል።ነጋሽ መሐመድ ሆሕንደርምን በስልክ አነጋግሮ ያጠነካረዉ ዘገባ አለ።


የሶማሊያ ፌደራላዊ የሽግግር መንግሥት ሕልዉና «በይሕወት መደጋፊያ መሳሪያ ላይ ነዉ» ይላል የክራይስስ ግሩፕ ጥናታዊ ትንታኔ።«እያጣጣረ ነዉ» ነዉ ባጭሩ።የአጥኚዉ ተቋም የአፍሪቃ ቀንድ ጉዳይ ሐላፊ ኢጄ ኾኽንዶርም እንደሚያምኑት የሽግግር መንግሥቱን ቃሬዛ የተሸከመዉ ደግሞ እዚያ የሠፈረዉ የአፍሪቃ ሕብረት ጦር ነዉ።

«የሶማሊያ ፌደራላዊ ሽግግር መንግሥት፥-እዚያ የሠፈረዉ ስምንት ሺሕ የአፍሪቃ ሕብረት ሠራዊት ባይጠብቀዉ ኖሮ-ወዳቂ ነበር።»

አለም አቀፉ ማሕበረሰብ ለፕሬዝዳንት ሼኽ ሸሪፍ መንግሥት ከዚያ በፊት ከነበሩት መንግሥታት ሁሉ የተሸላ ድጋፍና እገዛ እየሰጠ ነዉ።እንደ መንግሥት የሚንቀሳቀሰዉ ግን አንድም ቪላ ሞቃዲሾ ቤተ-መንግሥት፥ አለያም ከቤተ-መንግሥቱ እስከ አዉሮፕላን ማሪያ በሚወስደዉ ጎዳና ብቻ ነዉ።ሁለት አመቱ።
የሽግግር መንግሥቱ ድጋፍ፥ ርዳታዉን ተጠቅሞ አስተዳደሩን እንዲያስፋፋ የተሰጠዉን ምክር ግን ገቢር አላደረገም ባይ ናቸዉ ኾኽዶርም።

«የሆነዉ ምንድነዉ-የሽግግር መንግሥቱ ባለፉት ሁለት አመታት ከዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ ጠንካራ ድጋፍ ተሰጥቶታል።አስተዳደሩን ከሞቃዲሾ ዉጪ ወዳሉ አካባቢዎች እንዲያስፋፋም በተደጋጋሚ ተመክሮ ነበር።ገቢር ግን አላደረገዉም።»

የክራይስስ ግሩም የመሰንበቻዉ ጥናታዊ ትንታኔም «ምክረዉ፥ ምክረዉ እንቢኝ ካለ----» አይነት ነባር ብሒልን አስታዋሽ ነዉ።

«እኛ ለማድረግ የሞከርነዉ፣ የሽግግር መንግሥቱ ባለሥልጣናት የአስተዳደር ሥርዓታቸዉን ማሻሻሉ ለነሱ ለራሳቸዉ እንደሚጠቅማቸዉ መልዕክት ማስተላለፍ ነዉ።ሥርዓታቸዉን ካላሻሻሉ ግን አለም አቀፉ ማሕበረሰብ የሚሰጣቸዉን ድጋፍ እንዲያጤነዉ ነዉ።»

የሼኽ ሸሪፍ መንግሥት መከራ መክሮት ወደቀም-ቀጠለ-አሁን ያለዉ አይነት የመንግሥት መዋቅር ለሶማሊያ እስካሁን እንዳልጠቀመ ሁሉ ወደፊትም አይፈይድም።ለሶማሊያ የሚበጀዉ ይላሉ ኾኽዶርም ያልተማከለ መንግሥት ነዉ።

«መታወቅ ያለበት ሞቃዲሾ ዉስጥ ጠንካራ ማዕከላዊ መንግሥት መመሥረት በሶማሊያ ሁኔታ አይሠራም።የሚያስፈልገዉ ሥልጣኑን ለአካባቢ መስተዳድሮች የሚያጋራ መንግሥት ነዉ።የሽግግር መንግሥቱ ማድረግ ያለበትም ይሕንን ነዉ-ብለን ነዉ-የምናስበዉ።»

የተማከከለዉን ሥልጣን ለአካባቢ መስተዳድሮች ማከፋፈሉ አል-ሸባብን የመሳሰሉ ሐይላትን ለመዋጋት ይረዳል ባይናቸዉ ኾኽዶርምና ባልደረቦቻቸዉ።
ነጋሸ መሐመድ
ሒሩት መለሰ