1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሽልማት ለጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ

ረቡዕ፣ ጥር 21 2006

የዓለም የዜና እና ጋዜጣ አሳታሚዎች ማኅበር የ2014 የነጻነት ወርቅ ብዕር ሽልማቱን ለጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ መስጠቱን ስታወቀ። የማህበሩ የፕረስ ነፃነት ዳሬክተር እንደሚሉት፤ ማህበሩ ይህን ሽልማት ለጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ለመስጠት በመወሰኑ፤ ለኢትዮጵያ መንግሥት ግልፅ የሆነ መልዕክት ያስተላልፋል፣ እውነታውንም አጉልቶ ያሳያል።

https://p.dw.com/p/1AzBH
Federhalter - Füller
ምስል Fotolia/matttilda

የዓለም የዜና እና ጋዜጣ አሳታሚዎች ማኅበር ከሁለት ቀን በፊት ባወጣው መግለጫ “በጸረ ሽብር ሕግ” ምክንያት በወጣው አዋጅ የ 18 ዓመት እስራት የተበየነበት ኢትዮጵያዊ ጋዜጠኛና አምደኛ እስክንድር ነጋ የዓመቱ የነጻነት ወርቅ ብዕር ተሸላሚ እንደሚሆን ገልጿል። ጋዜጠኛው የዓመቱ ብቸኛ ተሸላሚ ሲሆን፤ ማህበሩ ለምን እስክንድር ነጋን ለመሸለም እንደወሰነ የዓለም የድርጅቱ የፕረስ ነፃነት ዳሬክተር ኤለሰን ሚስተን እንዲህ ያብራራሉ፤

Zentralgefängnis von Abidjan Elfenbeinküste
ምስል DW/S. Martineau

«የነጻነት ወርቅ ብዕር ሽልማት፤ በዓለም አቀፍ የመገናኛ ብዙኃን ዘንድ እውቅና ያለው የመጀመሪያው ሽልማት ነው። ለፕረስ ነፃነት ከፍተኛ አስተዋፅዎ ላበረከቱ ግለሰቦችም ሆነ ድርጅቶች እውቅና ይሰጣል። እና እስክንድር ነጋ በኢትዮጵያ ነፃ ፕረስ እንዲስፋፋ ጥረት አድርጓል የሚል እምነት አለን፤ ለዛም ነው የዚህ ዓመት የወርቅ ብዕር ተሸላሚነቱ አስፈላጊ ሆኖ ያገኘነው።»

ወይዘሮ ኤለሰን ሚስተን በርግጥ ከጋዜጠኛ እና አምደኛ እስክንድር ነጋ በተጨማሪ በእስር ላይ የሚገኙ እንደ ጋዜጠኛ ሰሎሞን ከበደ፣ ውብሸት ታዬ፣ ርዕዮት ዓለሙ፣ ዩሱፍ ጌታቸው እና ሌሎችም እስረኞች እንዳሉ እንደሚያዉቁ፤ የኢትዮጵያ መንግሥትም ከእስር እንዲፈታቸው ጥሪ አንዳደረጉ ይናገራሉ። ነገር ግን ይላሉ ወይዘሮዋ፤

«ነገር ግን ለእስክንድር ነጋ እውቅና ስንሰጥ፤ አሳታሚ፣ ጋዜጠኛ እና አምደኛ ለሆነ ሰው፤ እንዲሁም በኢትዮጵያ ለረዥም ዓመታት ለነፃ ፕረስ ለታገለ ሰዉ እዉቅና ሰጠን ማለት ነዉ። በ90ዎቹ ዓመተ ምህረት መጀመሪያ አካባቢ ያሳትመው የነበረው ጋዜጣ ተዘግቷል። የጋዜጠኝነት የሥራ ፈቃዱን ተነጥቋል፣ እና ይህ ሰው ለረዥም ዓመታት ለፕረስ ነፃነት የተሟገተ ነው። ለዛ ነው ለዚህ ሽልማት እውቅና ያገኘው።»

Zeitungen Äthiopien
በኢትዮጵያ የሚታተሙ ጋዜጦጥምስል DW

የነጻነት ወርቅ ብዕር ሽልማት እኢአ ከ2061 ጀምሮ በአመት አንዴ የሚሰጥ ሽልማት ነው። የሽልማቱም ሥነ ሥርዓት ሰኔ 2 ቀን 2006 ዓም በቶሪኖ -ኢጣሊያ እንደሚካሄድ የማህበሩ መግለጫ ያመለክታል። ይህ ሽልማት ለጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እንዲሰጥ መወሰኑ ጋዜጠኛው ከእስር እንዲለቀቅ ግፊት ለማድረግ ያለመ እንደሆነ ነዉ ወይዘሮ ሚስተን የሚገልፁት፤

ይህንን ሽልማት ለእስክንድር በማበርከታችን ለኢትዮጵያ መንግሥት ግልፅ የሆነ መልዕክት ያስተላልፋል ብለን ተስፋ እናደርጋለን። በተለይ ደግሞ “በጸረ ሽብር ሕግ” ሰበብ ጋዜጠኞችን ወደ ወህኒ ቤት መወርወር፤ ማንኛውንም የዓለም አቀፍ ስምምነት የጣሰ ነዉ። እናም በመንግሥት ላይ ትችት የሚያቀርቡትን ዝም ለማስባል ሲባል ኢትዮጵያ ጋዜጠኞች እንደሚታሠሩ እውነታውን አጉልቶ ያሳያል ብለን እናምናለን።»

ማህበሩም ከሌሎች ተቋማት ጋር በመተባበር እስክንድር እና ሌሎች ጋዜጠኞች እንዲፈቱ የበኩሉን እንደሚያደርግ ሚስተን ገልጸዋል። ኤለሰን ሚስተን ባለፈው ኅዳር ወር ከዓለም አቀፍ የፕረስ ተቋም ጋር በመሆን ማህበሩ የኢትዮጵያ መንግሥት ተወካዮችን ለማነጋገር በተደጋጋሚ ቢሞክርም የመንግስት ባለስልጣናቱ ፍቃደኛ እንዳልነበሩ አመልክተዋል። በመቀጣይም በቀጥታ ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማሪያ ደሳለኝ፤ ከሳቸውም ጋር ይሁን ከተወካዮቻቸው ጋር መወያየት እንዲችሉ ጥያቄ እንደሚያቀቡ ዳሬክተሯ ገልፀውልናል።

ልደት አበበ

ሸዋዬ ለገሰ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ