1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በርሊን ጥቃት

ማክሰኞ፣ ታኅሣሥ 11 2009

አደጋዉን ያደረሰዉ ወይም ያደረሱት ወገኖች ከአሸባሪ ድርጅቶች ጋር ግንኙነት ይኑራቸዉ አይኑራቸዉ በዉል አይታወቅም። ፖሊስ ቢያንስ አንድ ተጠርጣሪ መያዙን አስታዉቋል።

https://p.dw.com/p/2UZtQ
Deutschland Angela Merkel, Thomas de Maziere und Frank-Walter Steinmeier am Breitscheidplatz
ምስል Reuters/H. Hanschke

በጀርመን ርዕሰ ከተማ በርሊን ላይ በተዘረጋዉ የገና ገበያ ሥፍራ ጥቃት ያደረሰዉን ወገን ባስቸኳይ ለፍርድ እንደሚቀርብ የሐገሪቱ መራሒተ-መንግሥት አስታወቁ። ሜርክል ሐገራቸዉ በጥቃቱ ምክንያት ከእለት፤ ከዕለት እንቅስቃሴዋ እንደማትገታና በፍርሃት እንደማትሸበብ ተናገረዋል። « በአሁኑ ጊዜ ያለንበት ሁኔታዉ ከባድ ቢሆንም በክፉ ነገር ፍርኃት ነግሶ መኖርን አንሻም ሲሉም ሜርክል አስታዉቀዋል። የወንጀሉ ተጠያቂ ቅጣቱን ይቀበላል ሲሉ ተናግረዋልም።« የድንገተኛ አደጋ ሰራተኞች፤ ፖሊሶች፤ የእሳት አደጋ ተከላካዮች፤ ሐኪሞችና የመጀመርያ ህክምና ርዳታ ባለሞያዎች ሁሉ ትናንት ማታ ጥቃቱ በተፈፀመበት ቦታ ለሰጡት ርዳታ ላመሰግናቸዉ እወዳለሁ። ለከባድ ሥራና ተልዕኮአችሁ ላመሰግናችሁ እወዳለሁ ። ከትናንት ምሽት ጀምሮ ይህን ወንጀል የፈፀመዉን ወገን ማንነት በማጣራት ላይ የሚገኙት ሰዎች እያንዳንዱን የወንጀሉን ክፍል አጣርተዉ ይፋ ያደርጋሉ የሚል ትልቅ እምነት አለኝ። ወንጀለኞቹ ሕጋችን እስከፈቀደ ድረስ ጠንካራ ቅጣት ይቀበላሉ። » ጥቃት አድራሹ የ 23 ዓመት የፓኪስታን ስደተኛ ነዉ መባልን ተከትሎ መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል በሰጡት መግለጫ « ጥቃቱን የጣለዉ ጀርመን ከለላ እና ጥገኝነት የጠየቀ ሰዉ ነዉ ተብሎ መረጋገጫ ከመጣ፤ በተለይ ለኛ ይህን ጉዳይ መስማቱ ከባድ ነዉ የሚሆንብን ሲሉ ተናግረዋል። ሜርክል ወንጀሉ እንደሚጣራና ወንጀለኛዉ ለፍርድ እንደሚቀርብ ተናግረዋል። መራሒተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሽታይን ማየር፤ የሃገር ዉስጥ አስተዳደር ሚኒስትር ቶማስ ዴ ሚዜር እንዲሁም የበርሊን ከተማ ከንቲባ ሚሻኤል ሙለር ጥቃቱ የተፈፀመበት ቦታ በመገኘት ለሰለቦች አበባን አኑረዋል። የጀርመኑ ፕሬዚደንት ዮአሂም ጋዉክ፤ ጥቃቱ የበአኗኗራች እምብርት ላይ የተቃጣ ነዉ፤ ጥቃቱ ማኅበረሰባችንን አያሸብርም፤ የጥቃት አድራሹ ጥላቻ እኛን ወደ ጥላቻ አይመራንም፤ በጀርመን መብትና ሰብዓዊነት የተከበረ ነዉ፤ ሲሉ ተናግረዋል።

ነጋሽ መሐመድ

አዜብ ታደሰ