1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በሳይንስ የኖቤል ተሸላሚዎችና ምርምራቸው

ረቡዕ፣ ታኅሣሥ 2 2006

ትናንት ፤ በእስቶክሆልም ፤ ስዊድን ፣ በኔልሰን ማንዴላ የመጨረሻ የስንብት ሥነ ሥርዓት ሳቢያ ታላላቅ ዓለም አቀፍ እንግዶች ተመናምነው ፣ ሆኖም ከ 1,300 በላይ ታዳሚዎች በተገኙበት ስብሰባ ፣ በ3 ቱም የተፈጥሮ ሳይንስ ዘርፎች ውድድር ፣ የዘንድሮዎቹ አሸናፊዎች ሽልማታቸውን ተቀብለዋል።

https://p.dw.com/p/1AXHU
Nobelpreis 2013 Francois Englert Peter Higgs
ምስል picture-alliance/AP Photo

ለጀርመን ዓመታዊ የምርምር ከፍተኛ ሽልማት ለፍጻሜ የደረሱ 3 እጩ ተሸላሚዎች ፕሮጀክቶች ፤ ከብርሃን ጋር ግንኙነኅት ያላቸው ሲሆን፤ በተለይ ከየናው ፣ የፍሪድሪኽ ሺለር ዩንቨርስቲ ፣ ከ ቦሽና በ ሽራምበርግ ከተማ ከሚገኘው በ LASER(Light Amplification by Stimulated Emission of Radiation) ምርምር ላይ ካተኮረው ተቋም ጋር ተባብረው ለኢንዱስትሪ የሚበጅ እጅግ ኃይለኛ ሙቀት በማመንጨት ፣ የብረታ ብረት ፣ መስታውት፣ ፕላስቲክም ሆነ ሌላ ፣ እጅግ በተቀላጠፈ ሁኔታ የሚፈለገውን ቅርጽ እንዲይዝ ለማድረግ በማብቃታቸው በአንደኛነት 250,000 ዩውሮ ለመሸለም በቅተዋል። አንዳች ትርፍ ስብርባሪ ነገር ሳይኖር ፣ ምንም ሳይባክን መሥራት የሚያስችለው ልዩ LASER፤ ረቂቅ ሞተር ፤ የቤት ማሞቂያና የህክምና መሣሪያዎችን ማምረት የሚያስችል ነው። የ LASER ሥነ ቴክኒክ፤ ለዘመናዊ ቴሌቭዥን ፣መነጽር ፣ የእጅ ስልክና ለመሳሰሉ መሳሪያዎች የተቀላጠፈና ምንም የሚባክን ነገር ለሌለበት ሥራ እጅግ የሚበጅ መሆኑ ተመሥክሮለታል።

Nobelpreis für Chemie 2013
ማርቲን ካርፕሉስ፣ማይክል ሌቪት እና አርየኽ ዋርሼልምስል Jonathan Nackstrand/AFP/Getty Images

ትናንት ፤ በእስቶክሆልም ፤ ስዊድን ፣ በኔልሰን ማንዴላ የመጨረሻ የስንብት ሥነ ሥርዓት ሳቢያ ታላላቅ ዓለም አቀፍ እንግዶች ተመናምነው ፣ ሆኖም ከ 1,300 በላይ ታዳሚዎች በተገኙበት ስብሰባ ፣ በ3 ቱም የተፈጥሮ ሳይንስ ዘርፎች ውድድር ፣ የዘንድሮዎቹ አሸናፊዎች ሽልማታቸውን ተቀብለዋል። የኖቤል ኮሚቴ ፤ የቁጠባ እርምጃ በመውሰድ ላይ በመሆኑ ፣ ለእያንዳንዱ የዕውቀት ዘርፍ የተመደበው ሽልማት ፣ አምና ከነበረው 1,5 ሚሊዮን ዶላር ወደ 1,2 ሚሊዮን ዶላር ዝቅ

ብሏል። የኖቤል ድርጅት ፤ ንብረቱም ሆነ ወረቱ ፣ ከሞላ ጎደል 450 ሚልዮን ዶላር ነው። ሽልማት ከተቀበሉት መካከል፣ በፊዚክስ ፣ ግዝፈት ስላላቸው ጠጣር ነገሮች ወይም ቁሳቁሶች ምንጭ ለማወቅ ግንዛቤ እንዲኖረን ፣ በንዑሳኑ ክፍልፋይ የአቶም ቅንጣቶች ላይ ሰፊ ምርምር ያካኼዱት፣ የብሪታንያው ተወላጅ ፒትር ዌር ሒግስና ቤልጂጋዊው ፍራንሷ ኦንግሌርት ናቸው።

ለፍጥረተ ዓለም ቁስ አካል ኢምንት መሠረት ስለሚሰኘው «ሒግስ-ቦሰን» (የእግዚአብሔር ቅንጣት)ነባቤ ቃል ያሠፈሩት ፒትር ዌር ሒግስ ፤ በአውሮፓው የኑክልየር ምርምር ተቋም(European Organization for Nuclear Research) በግዙፍ አቶም ጭፍላቂ መሣሪያ Large Hadron Collider አማካኝነት ምሥጢሩ ተደረሰበት እንደተባለ ፣ ምን እንደተሰማቸው ሲናገሩ እንዲህ ነበረ ያሉት።
«በዚህ አስደናቂ ግኝት የተሳተፉትን ሁሉ እኔም እንኳን ደስ አላችሁ እላለሁ። ለእኔ፤ ይህ በእውነት በሕይወት ዘመኔ የተከሠተ ተዓምራዊ ጉዳይ ነው።»

የ CERN ዋና ሥራ አስኪያጅ ጀርመናዊው Rolf-Dieter Heuer በሐምሌ ወር 2004 ዓ ም የአቶም ኢምንት ቅንጣት (ሂግስ- ቦሰን) በቤተ ሙከራ መገኘቱ እንደተገለጠ በበኩላቸው እንዲህ ማለታቸው የሚታወስ ነው።

«እንደሚመስለኝ፤ ትልቅ ግኝት ነው። የአቶም ኢምንት ቅንጣት አግኝተናል። እንደምገምተው50 ዓመት ያህል ስንፈልገው የነበረ ነው። ይህ ስንፈልገው የነበረው፤ እጅግ ኢምንቱ የአቶም ኢምንት ቅንጣት ነው፣ አይደለም፥--እኛ ከሚፈለገው የአቶም ቅንጣት ጋር ተመሳሳይነት ያለውን ለማግኘት በቅተናል። »

በሥነ ቅመማ ፤ Martin Karplus, Michael Levitt, እና Arieh Warshel የተባሉት ተመራማሪዎች ናቸው፣ ትናንት የተመደበላቸውን ሽልማት የተቀበሉት። የተሸለሙበት ምክንያት ፣ በኮምፒዩተር ሞዴል፤ እንደ ምስለ-በረራ፣ የንጥረ ነገሮችን ምሥጢራዊ ፈጣን ጉዞ በማሳየት፣ በሰውነት አካላት ውስጥ፣ ንጥረ ነገሮች እንዴት እንደሚንሸራሸሩ የሚያስረዳ ሲሆን፣ መድኃኒቶችንና የፀሐይ ብርሃንና ሙቀት ተቀባይ ስስ ጡቦችን አሠራር ለማሻሻል የሚበጅ ነው።

Kombibild Nobelpreisträger Medizin 2013
ጀምስ ሮትማን ፣ራንዲ ሼክማን ና ቶማስ ዙድሆፍምስል picture-alliance/dpa

በህክምናው ዘርፍ ደግሞ ፣ የኅዋሳትን የማጓጓዣ ሥርዓትን ፣ ከአንድ ኅዋስ ወደ ሌላው ንጥረ ነገሮች የሚመላለሱበትን መንገድ በምርምራቸው በማስረዳት ነው ፤ ጄምስ ኢ ሮትማን ራንዲ ደብልዩ ሼክማን፣ እና ቶማስ ሲ ሱድሆፍ ለሽልማት የበቁት።

በኢንዱስትሪ የበለጸጉም ሆኑ በማደግ ላይ የሚገኙ አገሮች፣ በኤኮኖሚ የዕድገት እመርታ ለማግኘት፣ ለዕድገቱ መሠረት የሚሆነውን ምርምርም ሆነ ሥነ ቴክኒክ ለማጠናከር ከመጣር አይቦዝኑም ። በተለይ በኢንዱስትሪ የገሠገሡት አገሮች ለሳይንስና ሥነ-ቴክኒክ ዐቢይ ግምት ያላቸው መሆኑ ከቶውንም አያጠራጥርም። ከዚሁ ደረጃ ለመድረስ ያበቃቸው ፤ ወደፊትም ወደላቀ እመርታ የሚያሸጋግራቸው መሆኑን ጠንቅቀው ያውቃሉና!

ለሳይንስና ሥነ ቴክኒክ ምርምር መንግሥታት በተናጠልም በኅብረትም ነው የሚያካሂዱት።

ለምሳሌ ያህል ፤ 27 አገሮችን ያቀፈው የአውሮፓው ኅብረት ፣ «አድማስ 2020 » በተሰኘው የ 7 ዓመታት የምርምር መርኀ-ግብሩ 70 ቢሊዮን ዩውሮ በጀት ለመመደብ ሳይስማማ እንዳልቀረ ነው የተነገረው።

ጀርመን ለምርምር የምታወጣው ገንዘብ ፤ ከመንግሥት፤ ከተለያዩ ኩባንያዎች፤ ከተቋማትና ከአካባቢያዊ መስተዳድሮች ነው የሚገኘው። አምና ፤ 80 ቢልዮን

CERN Generaldirektor Rolf-Dieter Heuer
ሮልፍ ዲተርምስል Fabrice Coffrini/AFP/Getty Images

ዩውሮ ፤ ለምርምርና ልማት ውሏል። ዘንድሮ ብቻ፤ ፌደራሉ መንግሥት፤ በአጠቃላይ 14,4 ቢልዮን ዩውሮ ነው ወጪ ያደረገው። ይህም እ ጎ አ በ 2005 ከነበረው መጠን ጋር ሲነጻጸር ፣ የ 60 ከመቶ ዕድገት ነው ያሳየው። ሃቻምና ኩባንያዎች፤ ከዚያ በፊት ያልተከሠተ በዛ ያለ ገንዘብ ነበረ የመደቡት። ያኔ 50,3 ቢሊዮን ዩውሮ በመመደብ ፤ ከዚያ በፊት ከነበረው በ 7,2 ከመቶ ከፍ እንዲል አድርገዋል። አብዛኛውን ወጪ የመደበው የአውቶሞቢሉ እንዱስትሪ ነው። አምና መንግሥት የመደበው ወጪም የ 2,88 ከመቶ ዕድገት አሳይቷል።

ባለፈው ዓመት ፤ የጀርመን ፌደራል መንግሥት ፤ ፌደራል ክፍላተ ሀገርና ማዘጋጃ ቤቶች 110,3 ቢሊዮን ዩውሮ ነው ለትምህርት ብቻ ያወጡት። ከሃቻምናው ጋር ሲነጻጸር የ 4,7 ቢሊዮን ዩውሮ ጭማሪ መገኘቱን የፌደራሉ መንግሥት የመዘርዝር ጥናት ክፍል ያመለክታል ። እ ጎ አ በ 2010 ፤ የግሉ የኤኮኖሚ ዘርፍ 234,5 ቢሊዮን ዩውሮ ሳያወጣ አልቀረም። ይህም ፤ ከሀገሪቱ አጠቃላይ ያልተጣሪ ብሔራዊ ገቢ 9,5 ከመቶ ገደማ መሆኑ ነው። ፌደራሉ መንግሥትና የፌደራል ክፍላተ ሀገር መስተዳድሮች፤ ለምርምር የሚመደበው ገንዘብ፤ ከብሔራዊው ያልተጣራ ገቢ መካከል 10 ከመቶ ይሆን ዘንድ ነው ጥረት የሚያደርጉት።

የጀርመን ትልቁ የተፈጥሮ ሃብቷ ፣ የተለያዩ የተፈጥሮ ማዕድናት ሳይሆኑ ፤ ዐቢይ ትኩረት የሰጠችው የሳይንስና ሥነ ቴክኒክ ምርምሯ ነው። በመሆኑም ለብዙ ዓመታት ፤ በተለይ በፊዚክስ አያሌ የኖቤል ሽልማት ለማግኘት መብቃቷ አይዘነጋም።

ተክሌ የኋላ

ነጋሽ መሐመድ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ