1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በሶርያ የቀጠለው የኃይል ተግባር

ረቡዕ፣ ጥር 2 2004

የዐረብ ሊግ የታዛቢ ቡድን ሶርያ የፈረመችውን የሰላም ውል ተግባራዊ መሆኑን ለመቆጣጠር ከተሠማራ ካለፉት አሥር ቀናት ወዲህ አራት መቶ ሰዎች መገደላቸውን የተመድ አስታወቀ።

https://p.dw.com/p/13hoZ
ምስል Reuters

ድርጅቱ ይህን የሚያረጋግጥ ዘገባ እንደደረሰው በፀጥታ ጥበቃ ምክር ቤት ውስጥ የፖለቲካ ጉዳይ ምክትል ዋና ፀሐፊ ቢ ሊን ፓስኮ መግለጻቸውን በኒው ዮርክ ዲፕሎማቲክ ምንጮች አመልክተዋል። ይህ ዘገባ ሶርያ ውስጥ ሰው የሚገደልበት ርምጃ ታዛቢው ቡድን ከመግባቱ በፊት ከነበረው እንደሚበልጥና ሶርያ በሰላሙ ውል የገባችውን ግዴታ መጣሷን እንደሚያሳይ በተመድ የዩኤስ አሜሪካ አምባሳደር ሱዘን ራይስ አስታውቀዋል።
« ይህ የሶርያ መንግሥት በፈረመው ውል አማካኝነት በሀገሩ የቀጠለውን የኃይል ተግባር ለማብቃት ለዐረቡ ሊግ በገባው ቃል በመጠቀም ፈንታ፡ የኃይሉን ርምጃ ይበልጡን እያባባሰ መሄዱን የሚያሳይ ግልጽ ምልክት ነው። »
በተመድ ግምት መሠረት፡ በሶርያ ፕሬዚደንት በሺር ኧል አሳድ መንግሥት አንጻር ተቃውሞ ከተጀመረ ካለፉት ዘጥኝ ወራት ወዲህ ወደ አምስት ሺህ ተገድሎዋል። ይህ በዚህ እንዳለ፡ ፕሬዚደንት በሺር ከብዙ ጊዜ በኋላ ትናንት በቴሌቪዥን ባሰሙት ንግግር የሕዝቡን ዓመፅ እንደሚደምስሱ በማስታወቅ፡ ዓመፁን ያባባሱት ሀገሪቱን ለማናጋት የሚጥሩ የውጭ ኃይላት ናቸው ሲሉ ወቅሰዋል።
ይህ በዚህ እንዳለ፡ አንድ ለሶርያ ከሩስያ የተላከ የጦር መሣሪያ ቁሳቁስ ጭና ስትጓዝ የነበረች አንዲት መርከብ በቆጵሮስ ባህር ጠረፍ አቅራቢያ እንዳስቆሙ የቆጵሮስ መንግሥት ቃል አባይ ስቴፋኖስ ስቴፋኑ አስታውቀዋል። እንደሚታወቀው፡ የአውሮጳ ህብረት፡ ዩኤስ አሜሪካ እና ቱርክ በሶርያ ላይ የጦር መሣሪያ ዕገዳ አሳርፈዋል።