1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል
ኤኮኖሚ

Merga Yonas Bula
ማክሰኞ፣ ጥር 2 2009

በትናንትናዉ ዕለት ጠቅላይ ሚንስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በወቅታዊ ጎዳዮች ላይ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ መንግስት አዲስ የሙስና ጉዳዮች መርማሪ መስሪያ ቤት መከፈቱን ገልፀዋል።

https://p.dw.com/p/2VaFg
Äthiopien Ministerpräsident Hailemariam Desalegn
ምስል Getty Images/AFP/Z. Abubeker

Corruption in Ethiopia - MP3-Stereo

በፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን የሚመራው ይህ አዲስ መስሪያ ቤትም በከባድ ሙስና የተጠረጠሩትን ግለሰቦችንና ተቋማትን እንደሚመረምርም ጠቅላይ ሚንስትሩ ጠቅሰዋል። ጠቅላይ ሚንስትሩ «የፀረ/ሙስና ትግል ተቋማት» ስሉም ጠርተዋል።

ሙስናን ተከታትሎ መጦቀም ለመንግስት ብቻ የሚተዉ አይደለም የሚሉት ጠቅላይ ሚንስትሩ ኃይለማርያም ደሳለኝ ማህበረሰቡም የመረጃ ቴክኖሎጂ ተጠቅሞ መጠቆም እንደሚችሉም ይጠቅሳሉ። «ዋናዉ ጉዳይ ግልፅነትን ማስፈን» ነዉ ካሉ በኋላ ግልፅነት ስጎል ሙስና ይስፋፋል ሲሉም አሳስበዋል።

ጠቅላይ ሚንስትሩ ሙስናን ለመታገል መንግስታቸዉ ዝግጁ መሆኑን የተናገሩትን መግለጫ እንዴት ይመለከቱታል ብለን ከማህበረሰቡ አንድ አንድ ሰዎችን አነጋግረን ነበር።  ስማቸዉ  እንዳይጠቀስ የጠየቁን አንድ የባህርዳር ነዋሪ ፣ ጠቅላይ ሚንስትሩ ወደፊት የሚሰራ ስራ ሳይሆን እስካሁን መንግስታቸዉ ትላልቅ ሙስናን በተመለከተ የወሰደው ርምጃና ያከናወነው ስራ ካለ እዚያ ላይ መግለጫ መስጠት ነበረባቸዉ ይላሉ።

መግለጫቸዉ ወደ ተግባር የሚለወጥ ከሆነ ጥሩ ነዉ የሚት ሌላዉ የኮንሶ ነዋሪ ግን እዉን መሆኑን በጣም ይጠራጠራለዉ ። የሙስና ምርመራዉ ከተጀመረ ከጠቅላይ ሚንስትሩ መጀመር አለበት ሲሉም ተናግረዋል።

አዲሱ ኮሚሽን ሙስናን ለመታገል ካሁን ቀደም ከተቋቋመው መስሪያ ቤት የተሻለ ስራ ማከናወን ስለመቻል አለመቻሉ አስተያየታችሁን እንድያጋሩንም የዶይቼ ቬሌ ፌስቡክ ደህረ/ገፅ ተከታታዮችን ጠይቀን ነበር። አስተያየታቸዉን ከሰጡን መካከልም «ጉልቻ ቢለዋወጥ ወጥ አያጣፍጥም እንደሚሉት ነዉ፣ መምሪያ ማውጣትና ተቋም መቀያይሩ ውጤት ሊሆን አይችልም፣ የውሸት ጋጋታ እስከመቼ ነዉ?» ስሉ የጠየቁ አሉ። ሌሎች ደግሞ ይህ መግለጫ «አንደኛዉን አንጃ ለመምታት» የታቀደ ነዉ ካሉ በኋላ «አሁንም ከፕሮፖጋንዳና የአፈንጋጮች መምቻ ከመሆን ዉጪ ጥቅም አይኖረዉም» ብለዋል። 

መርጋ ዮናስ

አረያም ተክሌ