1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጋራ መግባባት እንዴት?

እሑድ፣ መስከረም 7 2010

የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር በምህጻሩ ኢህአድግ ሥልጣን ላይ ከቆየበት ከ26 ዓመታት በኋላ ዛሬም በብሔር ብሄረሰቦች መካከል የድንበር ግጭቶች መከሰታቸው በዚህ ሰበብም የሰዎች ህይወት መጥፋት እና የንብረት ውድመት መቀጠሉ እንዲሁም በየአካባቢው ድንበር ማካለሉ እያነጋገረ ነው።

https://p.dw.com/p/2k4xS
Karte Äthiopien Amhara, Tigray, Oromia Englisch

በኢትዮጵያ የጋራ መግባባት እንዴት?

ኢትዮጵያ አዲሱን ዓመት 2010ን ከተቀበለች 7 ቀናት ተቆጠሩ ። የኢትዮጵያ መንግሥት በአዲሡ ዓመት የሀገሪቱ ሰላም እንዲረጋገጥና የመልካም አስተዳደር ችግሮች እንዲፈቱም በርትቶ እንደሚሰራ ገልጿል። አዲስ ዓመት በመጣ ቁጥር ይህን የመሳሰሉ እቅዶች ቢወጡም በእስካሁኑ ጉዞ እንደታየው መንግሥት ህዝብን የሚያረካ ፖሊሲ ሲያወጣም ሆነ እርምጃ ሲወስድ አይታይም የሚሉ ትችቶች ይቀርቡበታል። የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር በምህጻሩ ኢህአድግ ሥልጣን ላይ ከቆየበት ከ26 ዓመታት በኋላ ዛሬም በብሔር ብሄረሰቦች መካከል የድንበር ግጭቶች መከሰታቸው በዚህ ሰበብም የሰዎች ህይወት መጥፋት እና የንብረት ውድመት መቀጠሉ እንዲሁም በየአካባቢው ድንበር ማካለሉ እያነጋገረ ነው። በአንዳንድ ሁኔታዎች ዜጎች ደህንነታቸው ለአደጋ መጋለጡ በመንግሥት ላይ እምነት እንዲያጡ ማድረጉ ይነገራል። ተቃዋሚዎች ፣ጋዜጠኞች፣ የመብት ተሟጋቾች በነጻነት መንቀሳቀስ መሥራት አለመቻላቸው በሠፊው እየተነገረ ነው።ነፃ ምርጫ የለም ብለው የሚከራከሩም አሉ። በዚህም ምክንያት ሐገሪቱ ለዘላቂው የሚበጅ ብሔራዊ መግባባት ያስፈልጋታል ባዮች ተበራክተዋል።  የግጭቱም ሆነ በመንግሥት ላይ እምነት የማጣቱ መንስኤ ቋንቋን መሠረት ያደረገው የፌደራሊዝም ስርዓት ነው ይህም የኢትዮጵያን ህልውና ለአደጋ እያጋለጠ ነው ሲሉ የሚከራከሩ ወገኖች አሉ። ሌሎች ግን ይህን አይቀበሉም። መንግሥት የሚከተለው የቋንቋ ፌደራሊዝም ለሐገሪቱ እድገትና ልማት አምጥቷልና ሀገሪቱን የሚጠቅም ስርዓት ነው ሲሉ ይሟገታሉ። በኢትዮጵያ የሀገር አንድነትን እና የኤኮኖሚ እድገትን እውን ለማድረግ የጋራ መግባባት እንዴት መፍጠር ይቻላል ? የዛሬው እንወያይ ርዕስ ነው። ሙሉውን ውይይት የድምጽ ማዕቀፉን በመጫን ያዳምጡ።

Äthiopien Stadt Jijiga
ምስል DW/T. Waldyes

ኂሩት መለሰ

ልደት አበበ