1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በኤርትራ ሰላማዊ ሰልፈኞች ተገድለዋል መባሉ

ዓርብ፣ ጥቅምት 24 2010

በኤርትራ ዋና ከተማ አስመራ በተካሄደ ተቃዉሞ ሰዎች መገደላቸዉና መጎዳታቸዉ ተነገረ። የሟቾቹ ቁጥር በገለልተኛ ወገን ባይጣራም 28 መድረሱን የተለያዩ የዜና አዉታሮች የመንግሥት ተቃዋሚ አካላትን በመጥቀስ ዘግበዋል።

https://p.dw.com/p/2mw93
Eritrea, Hauptstadt Asmara, Busbahnhof
ምስል picture-alliance

protest in Eritrea/final/ - MP3-Stereo

አስመራ ከተማ የሚገኝን አንድ የግል ትምሕርት ቤት መንግሥት ወደ ህዝብ ትምሕርት ለመቀየር ያለውን እቅድ በመቃወም ባለፈው ማክሰኞ በትምህርት ቤቱ የተቃውሞ ሠልፍ መካሄዱን የተለያዩ ዘገባዎች አመልክተዋል። በዚህም የተነሳ የትምሕርት ቤቱን የበላይ ጠባቂ ሀጂ ሙሳ ኑርን ጨምሮ  በርካታ የትምሕትር ቤቱ የኮሚቴ አባላት መታሠራቸውን ነዋሪነታቸው ለንደን የሆነ የኤርትራ ሰብዓዊ መብት አቀንቃኝ አቶ አብዱራህማን ሠይድ ለዶቼቬለ ገልጸዋል። የተቃውሞ ሠልፉን የሀገሪቱ የማስታወቂያ ሚኒስትር አቶ የማነ ገብረ መስቀል በትዊተር ገጻቸው « መጠነኛ እና የሠው ህይወት ያልጠፋበት »ሲሉ ቢገልጹትም ቆይተው የወጡ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት ግን ሠዎች መገደላቸውን እየገለጹ ነው። አዣንስ ፕሬስ የዜና ወኪል አንድ የኤርትራ መንግሥት ተቃዋሚ ፓርቲ መሪን ጠቅሶ እንደዘገበው የሟቾች ቁጥር 28 ደርሷል። የሠብዓዊ መብት አቀንቃኙ አቶ አብዱራህማን ሠይድ  በበኩላቸው ከአስመራ ደረሰኝ ባሉት መረጃ መሠረት ይህንኑ ያጠናክራሉ። ላለፉት 5 ዓመታት መኖሪያውን ኖርዌይ ያደረገው ኤርትራዊው ጋዜጠኛ እና የሰብዓዊ መብት ተሟጋች አቶ ደሳለኝ በረከት የሠው ህይወት በመጥፋቱ ቢስማማም ትክክለኛ የሟቾችን ቁጥር መግለፅ ግን አስቸጋሪ ነው ይላል።ይህ በመንግሥት በኩል እየተወሰደ ያለው እርምጃም አድማው በድጋሚ እንዳይካሄድ ለማስፈራራት የተደረገ ነው ሲል አቶ አብዱራህማን ይናገራል። እንደ አቶ አብዱራህማን ገለጻ በአስመራ ከተማ ሆያ ትምሕርት ቤት የተካሄደው የተቃውሞ አመጽ ጊዜያዊ ሳይሆን ባለፉት 25 ዓመታት በህዝቡ ይደርስ የነበረው ጭቆና ውጤት ነው። በመሆኑም የዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብ ትኩረት ሰጥቶ የሀገሪቱን ህዝብ ሊደግፍ ይገባል ሲየሰብዓዊ መብት አቀንቃኙ አቶ አብዱራህማን አሳስበዋል። ጉዳዩን በተመለከተ ኤርትራ አዲስ አበባ እና ብራሰልስ የሚገኙትን የኤርትራ መንግሥት ተወካዮች በስልክ ለማነጋገር በተደጋጋሚ ብንሞክርም ሊሳካልን አልቻለም። 

ፀሐይ ጫኔ 

ሸዋዬ ለገሠ