1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በኦሮሚያ የብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና

Merga Yonas Bulaሐሙስ፣ ሚያዝያ 6 2008

በተለያዩ የኦሮሚያ ክልሎች በተካሄደዉ የተቀዉሞ እንቅስቃሴ ምክንያት ምክንያት በክልሉ የመማር -ማስተማር ሂደት መቋረጡ ተዘግቧል።

https://p.dw.com/p/1IUnG
Oromo Proteste in Äthiopien
ምስል Oromia Media Network

[No title]

በመጭዉ ግንቦት ወር የ8ኛ፣ 10ኛ እና 12ኛ ክፍል ተማሪዎች ለአገር አቀፍ ፈተና ቅፅ ስለሞሉ ፈተናዉን መፈተን ግዴታ መሆኑን መንግስት እያሳሰበ ይገኛል። ሆኖም ግን ተማሪዎቹ በቂ ዝግጅት ስላላደረግን ፈታና መፈተን አንችልም ማለታቸዉ ተሰምቷል።


በኦሮሚያ ክልል ከፍተኛ የተቃዉሞ እንቅስቃሴ በነበረበት በጉሊሶ ከተማ የመማር -ማስተማር ሂደቱ ተስተጓጉሎ እንዳለ እና ትምህርት ቤት እሚሄዱት ተማሪዎችም ከጠቅላላ ተማሪዎች 20 ከመቶ እንደማይሞሉ ስማቸዉ እንዳይጠቀስ የፈለጉት የከተማዋ ነዋሪ ለዶቼ ቬሌ ተናግረዋል። በተቃዉሞዉ ወቅት ወደ ቤተሰብ የተመለሱት በእስር ፍራቻ ወደትምህርት ቤት እንዳልተመለሱ እና የተመለሱትም ለፈተናዉ ራሳቸዉን ዝግጁነት ስላላደረጉ እንደማይወስዱ መላልሰዉ ቅሬታቸዉን እያሰሙ እንደ ሆነ እንደምከተለዉ አብራርተዋል፣ <<ለምሳሌ በነጆ አካባቢ የሚገኝ አባይ ኤባ የተባለዉ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የሚገኙት የ8ኛ ክፍል ተማሪዎች ትምህርት ሳንማር እንዴት አገር አቀፍ ፈተና መዉሰድ እንችላለን ብለዉ ጥያቄ ሲያቀርቡ፣ በአስተማሪዎች ትታችሁ መሄድ ትችላላችህ ሲባሉ፣ ከአንደኛ እስከ ሰባተኛ ክፍል ያሉት ተማሪዎች ጥያቄያቸዉን እንደግፋለን ብለዉ ሰላማዊ ሰልፍ በመዉጣት ትምህርት አቋርጠዉ ቤት ነዉ ያሉት። ሌሎች ትምህርት ቤቶች እንደ እነ ሶንቦ ሳዳን እና ግዳ ማርያም የሚባሉት የዚህን ዓመት ፈተና እንደማይወስዱ እና ሙሉ በሙሉ ፍላጎት እንደሌላቸዉ እየተናገሩ ይገኛሉ። እስከ አሁንም ለተነሱት ጥያቄዎች መንግሥት ከመስማት ዉጭ መልስ እየሰጠ አይደለም።>>


የ8ኛ ክፍል ተማሪዎች በዚህ ፈተና ቢወድቁ በመጭዉ ዓመት መልሰዉ በመማር ከመደበኛ ተማሪዎች ጋር ሊፈተኑ ይችላሉ ካሉ በኋላ ለ10ኛ እና 12ኛ ክፍል ተማሪዎች ግን ከዚህ የተለየ እንደሆነም ገልጸዋል። ተቃዉሞዉ ሳይጀመር በፊት የመፈተኛ ቅጽ የ10ኛ እና 12ኛ ክፍል ተማሪዎቹ ሞልተዉ ስለነበር በዚህ ዓመት ፈተናዉን ካልወሰዱ በሁሉም የትምህርት ዓይነቶች F እንደሚያገኙ እና በሚቀጥለዉ ዓመት በመደበኛ ተማሪነት መፈተን እንደማይችሉ እየተነገረ እንደሆነም እኝህ የከተማዋ ነዋሪ አስረድተዋል። ይህ ሊያስከትል የሚችለዉን ተፅዕኖም እንደምከተለዉ ያብራራሉ፣ <<የ10ኛ እና 12 ኛ ክፍል ተማሪዎች አሁን ባለዉ ሁኔታ ወደ ፈተና መግባት ማለት በምግብ ላይ አሸዋ መበተን ወይም የመሄጃ መንገድን በእሾህ ዘጋ ወይም ገመድ አንገት ላይ እንደማጥለቅ ነዉ። ምክንያቱም ላለፉት አምስት ወራት ተማሪዎቹ ትምህርት አልተማሩም፣ ጭንቅላታቸዉ ከወንድም ወይም ከትምህርት ጓደኛ መታሠር እና መሞት ጋር ተይዘዋል። መጭዉ ዓመት የ10ኛ ክፍል ተማሪዎች በግል የሚፈተኑ ከሆነ የማለፊያ ነጥቡ ከፍ ሊል ስለሚችል ያሰቡት ቦታ መድረስ አይችሉም።»


ይህም ከተማሪዉ አልፎ ደክመዉ ያስተማሩ ቤተሰብም እና የአካባቢዉ ኅብረተሰብ ላይም ተጽኖ እንደሚኖረዉም ይናገራሉ። በተወሰነ ቦታ እና ጊዜ የመማርና ማስተማር ሂደት መስተጓጎሉን የሚናገሩት በኦሮሚያ የትምህርት ቢሮ የትምህርት ባለሙያ አቶ ደረጀ መኮንን አሁን ግን ተማሪዎች እንደተመለሱ እና የመማር ማስተማር ሂደቱም እንደቀጠለ ይገልጻሉ። ተማሪዎቹን ለመልቀቂያ ፈተና ለማዘጋጀትም ቅዳሜ እና እሁድን ጨምሮ መምህራን ያላቸዉን ነፃ ጊዜ እየተጠቀሙ እንደሆነም አቶ ደረጀ ለዶቼ ቬሌ ተናግረዋል። ተማሪዎቹ ፈተናዉን ለመፈተን በቂ ዝግጅት አላደረገንም በሚል ቅሬታ እያሰሙ መሆኑን ያረጋገጡልን አቶ ደረጀ መፍትሄ ለመፈለግ በቢሯቸዉ በኩል እየተደረገ ያለዉን እንደሚከተለዉ ያብራራሉ፤ <<በቢሯችን በኩል ይህ ጉዳይ እየታየ ይገኛል፣ ታይቶዋልም። በአንድ በኩል በተወሰነ ጊዜ ትምህርት ተቋርጦ በነበረባቸዉ ትምህርት ቤቶች፣ ለምሳሌ የ8ኛ ክፍል ተማሪዎች ፈተና በተመለከተ እንዴት ብናደርግ ይሻላል ተብሎ በቢሯችን ደረጀ እየታሰበበት ነዉ፤ ግን ገና አልተወሰነም። ወይም የሚቻል ከሆነ ችግሩ ያጋጠማቸዉ ቦታዎች ፈተናዉን ሊራዘምላቸዉ የሚቻልበት መንገድ ይኖራል። ይህን በሚመለከት የሚመለከተዉ አከልበይፋ ሲወስን የተጎዱት ተማሪዎች ለፈተናዉ ሊዘጋጁ የሚችሉበት መንገድ ሊኖር እንደሚችል እኛም እናዉቃለን።>>

Berlin Demonstration von Oromo-Aktivisten
ምስል DW/H. Kiesel


ይህን ጉዳይ በተመለከተ በዶቼ ቬሌ የፌስ ቡክ ደረ ገጽ ላይ በተደረገዉ ዉይይት አብዘኞቹ ተሳታፊዎች በተቃዉሞዉ ምክንያት ለፈተና መዘጋጀት ያልቻሉትን የክልሉን ተማሪዎች መንግስት ልዩ ማእቀፍ በማዘጋጀት ፈተናዉን እንዲፈተኑ ማድረግ ቢችል እንደሚበጅ መክረዋል። ይህ ካልሆነ ግን ጉዳዩ የሌላ ተቃዉሞ ምክንያት እንዳይሆንም አሳስበዋል።

መርጋ ዮናስ

ሸዋዬ ለገሠ