1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በከፍተኛ ወጭ የሚገነባዉ የኮይሻ ግድብ

Merga Yonas Bulaማክሰኞ፣ ሐምሌ 5 2008

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል በኦሞ ወንዝ ላይ «ኮይሻ» የተባለ ግዙፍ ኤሌክትሪክ ኃይል ማመነጫ ግድብ ሥራን ለጣልያኑ ኩባንያ «ሳሊኒ ኢምፕሪጂሊዮ» ባለፈዉ ግንቦት ወር መሰጠቱ ተዘግቦአል።

https://p.dw.com/p/1JNmK
Äthiopien Omo Fluss Tal Landschaft
ምስል JENNY VAUGHAN/AFP/GettyImages

[No title]

ሳሊን በኢትዮጵያ ግድቦችን በመገንባት ረጅም ታሪክ ያለዉ ኩባንያ ሲሆን ሃገሪቱ «በኤኮኖሚ ለማደግና የሕዝቡን ኑሮ ለማሻሻል» ስትል የምታካሂደዉ ሙከራ ሁሉ በብዙ ፕሮጄክቶች ላይ እየረዳን ነዉ ሲሉ የኩባንያዉ ሕዝብ ግንኙነት ሃላፊ ዥል ካስቶንጌ ለዶይቼ ቬሌ ተናግረዋል። የኮይሻ ግድብ 170 ሜትር ከፍታ ያለዉ በጠንካራ ኮንክሪት እንደሚገነባ ኩባንያዉ ባወጣዉ ጋዜጣዊ መረጃ አትቶአል።

«ግድቡ ኮይሻ አከባቢ ነዉ፣ ለዚህም ነዉ ኮይሻ ግድብ የተባለዉ። ግድቡ 2,5 ብሊዮን ይሮ ያወጣል፤ እናም የግንባታ ሥራዉ ከተጠናቀቀ በዋላ 2200 ሚጋ ዋት ኃይል ማመንጨት አቅም ይኖረዋል። ግድቡ ዉኃ የመያዝ አቅሙ ስድስት ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜቴር ይሆናል።»

ይህ ኮይሻ ግድብ በታችኛዉ የኦሞ ወንዝ ላይ የሚገነባ መሆኑን ዘገባዎች ያሳያሉ። በሳሊኒ ኩባንያ ኦሞ ወንዝ ላይ የተገነባዉ ግቤ ሦስት አካባቢዉ ላይ በሚኖሩ ማኅበረሰብና ተፈጥሮ ላይ እንድሁም በታችኛዉ ቱርካና ኃይቅ ላይ ከፍተኛ ተፅእኖ ያመጣል የሚል ዘገባ መዉጣቱ የሚታወስ ነዉ።

ይህ በአዲሱ ግድብ ግንባታ እንዳይከሰት የኮይሻ ግድብ ሥራ ሳይጀምር «ሳሊኒ ኢምፕሪጂሊዮ» ጥናት ማድረግ አለማድረጉን በተመለከተ ዥል ካስቶንጌ ለቀረበላቸዉ ጥያቄ ሲመልሱ፤
«ሳሊኒ ኢምፕሪጂሊዮ» ተስማምቶ የሚሰራቸዉ ፕሮጄክቶች፣ ግቤ ሦስት ላይ እንዳደረገዉ ኮየሻ ግድብ ላይም ወደ ፊት በአከባቢዉ ማኅበረሰብም ሆነ ተፈጥሮ ላይ ሊከሰቱ የሚችሉ ጉዳቶችን በተመለከተ ጥናት የማድረግ ግዴታ አለበት። የኛ ደንበኛ የሆነዉ የኢትዮጵያ መንግስት ግድቡ በሚገነባበት አካባቢ ሊከተል በሚችለዉ ጉዳት ላይ የራሱን ጥናት ያካሄዳል። እኛ ግድቡ በሚገነባበት አከባቢ ያሉትን ማኅበረሰቦች የመጠበቅ ግዴታ አለብን። በሰራተኛ አያያዝና ክፍያ፣ በሚሰጣቸዉ ስልጠና፣ የሚገነቡ ትምህርት ቤቶች፣ የጤና ተቋማት፣ መንገዶችና የመብራት ኃይል ዝርጋታን በተመለከተ እንዲሁም ለሰራተኞቹ መኖርያ ቤት መገንባትን ሁሉ ያጠቃልላል። እኛ ያለብን ግዴታ አቅራብያችን ላይ ለሚገኙ ነዋሪዎችና አካባቢዉ በተፈጥሮ ላይ ብቻ ነዉ። ለምሳሌ የኮይሻ ግድብ ቤተሰቦች ላይ ችግር የሚያስከትል ከሆነ ከቦታዉ እንዲዘዋዋሩ የምንችለዉን ሁሉ ለማድረግ ዝግጁ ነን።>>

የግድብ ሥራ በጣም ዉስብስብ ነዉ ያሉት ዥል ካስቶንጌ ግድቡ በሚገነባበበት አካባቢ ላይ ጉዳት ሊኖር እንደሚችልና የጉዳቱን መጠን ለመቀነስ ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር በጋራ እየሰራን ነዉ ሲሉ ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ግድቦችን ገንብታ ኤሌክትሪክ በማመንጨት ወደ ጎረቤት አገር መሸጥ ላይ ስትገኝ፤ የኮይሻ ግድብን ጨምሮ ጊቤ ሦስትና የ«ህዳሴ ግድብ» ሥራ ሲጠናቀቅ፤ ኢትዮጵያ ከአፍሪቃ ኤሌትሪክን በማመንጨት አንደኛ ሃገር ያደርጋታል።

Äthiopien Omo Fluss Tal Landschaft Staudamm Gibe III
ምስል JENNY VAUGHAN/AFP/GettyImages

መርጋ ዮናስ

አዜብ ታደሰ