1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በካምፓላው ጥቃት የተጠረጠሩ 32 ሰዎች ለፍርድ ቀረቡ

ሐሙስ፣ ነሐሴ 13 2002

ሃምሌ 4 በካምፓላው የቦምብ ጥቃት እጃቸው እንዳለበት የተጠረጠሩ 32 ሰዎች ትላንት ለፍርድ ቀረቡ። እነዚህ ተጠርጣሪዎች የአምስት ሀገራት ዜጎች ሲሆኑ 76 ሰዎችን ላጠፋው ጥቃት ተጠያቂ ሆነው ክስ እንደሚመሰረትባቸው ተገልጿል።

https://p.dw.com/p/Orgx
በካምፓላው ጥቃት 76 ሰዎች ተገድለዋልምስል AP

በእርግጥ በካምፓላው ጥቃት ተጠርጣሪዎች ገና እየተለቀሙ ናቸው።ትላንት ናካዋ በሚገኘው ፍርድ ቤት ጉዳያቸው መታየት የጀመረው የ32ቱ ተጠርጣሪዎች ክስ በየትኛው የዩጋንዳ ችሎት መቅረብ እንዳለበት አልታወቀም። የኡጋንዳው ጠቅላይ አቃቤ ህግ ዳይሬክተር ሪቻርድ ቡቴራ ለፍርድ የቀረቡት ተጠርጣሪዎች የሽብርተኝነት ተግባር በመፈጸም ክስ ሊመሰረትባቸው እንደሚችል ገልጸዋል።ትላንት ለፍርድ የቀረቡት የአምስት ሀገራት ዜጎች ናቸው። 14ቱ የኡጋንዳ፤ 10 የኬንያ፤ 6 የሶማሊያ፤ እንዲሁም ከሩዋንዳና ከፓኪስታን አንድ፤ አንድ ይገኙበታል። ከእነዚህ መሃል 4ቱ ዩጋንዳውያን ባለፈው ሳምንት በመገናኛ ብዙኃን ቀርበው ድርጊቱን መፈጸማቸውን ገልጸው ነበር። ጥቃቱን በመሪነት እንዳቀነባበረ የገለጸው የ33ዓመቱ ኢሳ አህመድ ሉይማ ኡጋንዳ ወደሶማሊያ ጦሯን በመላኳ የተነሳ ዒላማ እንደተደረገች ተናግሯል። የዩጋንዳ ፍርድ ቤት ጉዳዩ በየትኛው ችሎት መታየት እንዳለበት ለመወሰን ለመስከረም ሁለት ቀጥሯል።

መሳይ መኮንን

ነጋሽ መሐመድ