1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በኮትዲቯር የተመድ የሰላም ተልዕኮ ፍጻሜ 

ረቡዕ፣ ሰኔ 28 2009

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የኮትዲቯር ተልዕኮ ባለፈው ሳምንት መጨረሻ አብቅቷል። የተመ ድርጅት ወታደሮች ከኮትዲቯር ሲወጡ በሀገሪቱ ለዓመታት የቀጠለው ቀውስም ያበቃ ይመስላል። ይሁን፣ ግጭቱ እንደቀጠለ ነው ።

https://p.dw.com/p/2fzxB
UN Mission UNOCI
ምስል picture-alliance/Photoshot/D. Haitao

Ende ONUCI MMT_ - MP3-Stereo


በኮትዲቯር የመጨረሻዎቹ የተባበሩት መንግሥታት ወታደሮች ከ13 ዓመት በኋላ ባለፈው ሳምንት አርብ ሀገሪቱን ለቀው ወጥተዋል። በኮትዲቯር የተመድ ልዩ ልዑክ አይቻቱ ሚንዳውዱ እንደተናገሩት በተልዕኮው ዘመን 67 ሺህ ተዋጊዎች ትጥቃቸውን እንዲፈቱ እና ከህብረተሰቡ ጋር እንዲዋሀዱ ተደርጓል። ከዚህ በተጨማሪም በሐገሪቱ በጎርጎሮሳዊው 2016 ተቃዋሚዎች ለመጀመሪያ ጊዜ የተሳተፉበት ምክር ቤታዊ ምርጫን ጨምሮ  የተለያዩ ምርጫዎች ተካሂደዋል። ሚንዳውዱ ባለፉት ዓመታት የተመድ ለኮትዲቯርየተለያዩ ድጋፎችን መስጠቱን ያስታውሳሉ።
« በሀገሪቱ የሰብዓዊ መብቶች ጉዳይ ትኩረት እንዲሰጠው ብዙ ድጋፍ አድርገናል። በኮት ዲቮር የተመ ድርጅት ተልዕኮ ማለትም በፈረንሳይኛ ምህፃሩ የONUCI የኤፍ ኤም ራድዮ ጣቢያን በተመሳሳይ መርህ  እና ሙያዊ ደረጃ እንዲቀጥል እና የሰላም ጉዳይንም እንዲያካትት ለፌሊክስ ቧኚ የሰላም ተቋም አስረክበናል።  »
የተመድ የኮትዲቯር የሰላምተልዕኮ ማብቃት በአፍሪቃ ልዩ ቦታ ይይዛል። የተመድ በተለያዩ የአፍሪቃ ሀገራት ከሚያካሂዳቸው የሰላም ተልዕኮዎች አብዛኛዎቹ ይራዘማሉ፤ ወይም ደግሞ በሌላ አዲስ ተልዕኮ ይቀየራሉ። ፍሬድሪሽ ኤበርት የተባለው የጀርመኑ የሶሻል ዴሞክራቶች ፓርቲ የጥናት ተቋም የኮትዲቯር የቢሮ ሃላፊ ቲሎ ሾነ  የተመድ ሰላም አስከባሪ ኃይል ከአይቮሪኮስት ከወጣ በኋላ ሰላም ይሰፍናል ብለው አይገምቱም። ተልዕኮውም በጥድፍያ እንዲያበቃ የተደረገ ይመስላል ይላሉ።
«አሁን በሀገሪቱ የተመድ ወታደሮች መውጣት በጥድፊያ የተደረገ ተብሎ ነው የሚታሰበው። የተመድ ተልዕኮ ሠራተኞች ሳይቀሩ በከፊል በጣም ተገርመዋል። እርምጃው አንዳንድ የሎጂስቲክ  ችግሮችን አስከትሏል።  ተልዕኮው በፍጥነት እንዲለቅ በመደረጉ በሀገሪቱ ውስጥ የተመድ በርካታ ቁሳቁሶች እና ገንዘብ ይገኛል።»
የመጀመሪያዎቹ የተመድ ወታደሮች ኮትዲቯር የሰፈሩት በጎርጎሮሳዊው 2004 ነበር። ያኔ ሀገሪቱ በአመጽ ተከፋፍላ ነበር። የተመድ ወታደሮች ከፈረንሳይ ወታደሮች ጋር ተዋጊዎቹን ኃይሎች ከወታደራዊ እንቅስቃሴ ነጻ በሆነ ቀጣና ውስጥ እንዲቆዩ አደረጉ። ሆኖም በ2010 ከተካሄደው ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ በኋላ በፕሬዝዳንት ሎሮን ባግቦ ደጋፊዎች እና በተቀናቃኞቻቸው የአላሳን ዋታራ ደጋፊዎች መካከል ደም አፋሳሽ ግጭቶች ተካሂደዋል። በወቅቱም ቁጥራቸው 3ሺህ የተገመተ ሰዎች ተገድለዋል። ዋታራ ያኔ በሀገሪቱ የሚገኘው ዓለም አቀፍ ኃይል እጩ ተደርገው ነበር የሚቆጠሩት። ብዙዎች የተመድ ወታደሮች የርሳቸውን ሰፈር በጦር መሣሪያ ሲጠብቁ ነበር ይላሉ። እንደ ሾነ ቀውሱ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ በኮትዲቯር እስከዚህም ተለወጠ የሚባል ነገር አይታይም። በርሳቸው አስተያየት ተዋናዮቹ አሁንም የቀድሞዎቹ ሰዎች ናቸው። በዚህ ዓመትም ብዙ አመጾች ነበሩ። ህዝቡ በ2020 የሚካሄደውን ምርጫ ከአሁኑ ፈርተቶታል። ከተመድ ዓላማዎች አንዱ የሆነው ማህበራዊ አንድነትን ማስፈን እጅግ ርቆ ነው የሚገኘው። አሁን ግጭቱ የሚካሄደው በአሁኑ ፕሬዝዳንት በዋታራ መንግሥት ውስጥ ባሉት የተለያዩ ቡድኖች መካከል ነው። ከመካከላቸው  ከአመጾቹ በስተጀርባ ሆነው የሚታዘቡት የዋታራ ተቃዋሚ የሀገሪቱ ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ግዊላሞ ሶሮ አንዱ ናቸው ። ፕየር ዳግቦ ጎዴ የኮትዲቯር የፖለቲካ ሳይንስ ምሁር ናቸው። በርሳቸው አስተያየት የተመድ ተልዕኮ በሀገሪቱ ዘላቂ ሰላም ማምጣት አልቻለም።
«ፓርላማው ፕሬዝዳንት ደጋፊዎች ዘንድ የተገኘው ጦር መሣሪያ ጉዳይ እየተጣራ ነው። ONUCI መጫወት የነበረበት ሚና ምን እንደነበረ ለማወቅ አስቸጋሪ ነው። ተዕልኮው በኮትዲቯር ኮስት ዜጎች መካከል እርቅ እንዲወርድ አልረዳም። አይቮሪኮስትን አንድ ሀገር ማድረግ አልቻለም ።» 
በኮትዲቯር የተመድ ተልዕኮ እንዲያበቃ ዘመቻ ሲያካሂዱ የቆዩትፕሬዝዳንት ዋታራ በበኩላቸው ሀገሪቱ በጥሩ ጎዳና ላይ ነው የምትገኘው ፤ግጭቱ አብቅቷል ፣እርቅ ወርዷል ሁሉም ነገር ስርዓት ይዟል ብለዋል። ሆኖም ከቡዋኬ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስ ምሁር ኦስማን ዚና የተመድ ወታደሮች መውጣት ህዝቡን ከፍተኛ ፍርሀት ላይ እንደጣለው እና ሰዉም ችግሩን በራሱ መፍታት የማይችለውን የኮትዲቯር ዜጋ በገለልተኝነት የሚሸመግለው ማነው የሚል ጥያቄ እያነሳ መሆኑን ተናግረዋል። 

Symbolbild UN Soldaten Elfenbeinküste
ምስል picture-alliance/dpa

ፊሊፕ ዛንድነር/ኂሩት መለሰ 

አርያም ተክሌ