1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ፈረንሳውያን ድምፅ ሲሰጡ ዋሉ

እሑድ፣ ሚያዝያ 29 2009

የፈረንሳይ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ድምጽ አሰጣጥ ተጠናቋል። ቅድመ ትንበያዎች እንደሚያመለክቱት በግላቸው የተወዳደሩት ኤማኑኤል ማክሮ አሸንፈዋል። መገናኛ ብዙኃን የቀድሞው የኢኮኖሚ ሚንስትር 65.5 በመቶ ድምጽ ማግኘታቸውን ዘግበዋል። ተፎካካሪዋ ማሪ ለ ፔን ያገኙት 34.5 በመቶ ነው።

https://p.dw.com/p/2cZI3
Frankreich Präsidentschaftswahl 2017 | Élysée-Palast
ምስል Reuters/E. Gaillard

ፈረንሳውያን ከግል ተወዳዳሪው ኤማኑዌል ማክሮ እና ከቀኝ አክራሪዋ ማሪን ለ ፔን አንዳቸውን ለመምረጥ ድምፅ ሲሰጡ ዋሉ። የፅንፈኞች ጥቃት ሥጋት የገባት ፈረንሳይ ለምርጫው ደኅንነት ጥበቃ 50,000 ጸጥታ አስከባሪዎች በመላ አገሪቱ አሰማርታለች። ምርጫውን ያሸንፋሉ ተብለው የሚጠበቁት የቀድሞው የኤኮኖሚ ሚኒሥትር ኤማኑዌል ማክሮ ደጋፊዎች ድላቸውን ለማክበር ከተዘጋጁበት ቦታ በጸጥታ ሥጋት ምክንያት እንዲበተኑ ተደርጓል። ከቤተ-መንግሥትነት ወደ ቤተ-መዘክርነት የተቀየረው የሉቭ ሙዚየም ቆየት ብሎ መከፈቱ ተሰምቷል።

እንደተተነበየላቸው የ39 አመቱ ማክሮ ካሸነፉ በፈረንሳይ ታሪክ ወጣቱ ፕሬዝዳንት ይሆናሉ። የፈረንሳይ አገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒሥቴር ከጎርጎሮሳዊው 2012 ዓ.ም. አኳያ አነስተኛ መራጮች ወደ ድምፅ መስጫ ጣቢያዎች አምርተዋል ብሏል። መምረጥ ከሚችሉ ዜጎች መካከል 65.3 በመቶ ብቻ ድምፅ ሰጥተዋል ሲል የፈረንሳይ ዜና አገልግሎት ዘግቧል።  ፈረንሳውያን በኢትዮጵያ አቆጣጠር እስከ ምሽቱ ሁለት ሰዓት ድምፅ ይሰጣሉ።

Großbritannien - Frankreich Präsidentschaftswahl 2017 | Stimmabgabe in London
ምስል picture-alliance/AP Photo/M. Dunham

የሕዝብ አስተያየቶች ኤማኑዌል ማክሮ ከፈረንሳውያን ድምፅ ከ61.5 እስከ 63 በመቶ ያገኛሉ ሲሉ ተንብየዋል። እስካሁን በተሰጡ ድምፆች የአውሮጳ ኅብረት ሊጠናከር ይገባል የሚል አቋም ያላቸው ማክሮ ተቀናቃኛቸውን እየመሩ መሆኑን የጀርመን ዜና አገልግሎት ዘግቧል። በፈረንሳይ እና ከፈረንሳይ ውጪ በተሰጡ ድምፆች ማክሮ ከ60 በመቶ በላይ ድምፅ ማግኘታቸውን ዜና ወኪሉ የቤልጅየም ቴሌቭዥን ጣቢያን ጠቅሶ ዘግቧል። የዛሬው ምርጫ ውጤት በአውሮጳ ኅብረት ኅልውና ላይ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ከፍ ያለ ተፅዕኖ ስለሚኖረው የአኅጉሩ መሪዎች እና ባለሥልጣናት በጉጉት ይጠብቁታል። 

በምርጫ ድምፅ ለመስጠት 47,58 ሚሊዮን ሰው ተመዝግቧል። ከጠዋቱ ሁለት ሰአት ጀምሮ በኢትዮጵያ ሰአት አቆጣጠር ከምሽቱ 2 ሰአት ከ45 ደቂቃ በሚጠናቀቀው ምርጫ ሂደቱ ምን ይመስል ነበር? የጸጥታ ጥበቃውስ ምን ይመስላል? 

ሃይማኖት ጥሩነህ

እሸቴ በቀለ

ማንተጋፍቶት ስለሺ