1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ተቀናቃኞቹ የጀርመን እጩዎች

ዓርብ፣ መስከረም 15 2002

የጀርመን አጠቃላይ የፓርላማ ምርጫ ሊካሄድ በጣት የሚቆጠሩ ቀናት ናቸው የቀሩት። ወደ 62 ሚሊዮን የሚጠጉ ጀርመናውያን ድምፃቸውን ይሰጣሉ ተብሎ በሚገመትበት በዚህ ምርጫ 29 ፓርቲዎች ተካፋይ ናቸው።

https://p.dw.com/p/JoFw
ሽታይንማየር እና ሜርክልምስል picture-alliance/ dpa

ከነዚህ ውስጥ ግን ዋነኛዎቹ አምስት ሲሆኑ እነርሱም ወግ አጥባቂዎቹ ክርስቲያን ዲሞክራቶች ማለትም የክርስቲያን ዴሞክራት ህብረት ፓርቲ በምህፃሩ CDU እና የክርስቲያን ሶሻል ህብረት ፓርቲ CSU ፣ የመሀል ግራው ሶሻል ዴሞክራት ፓርቲ SPD ፣ የገበያ መርህ የሚያራምደው FDP ፣ ለአካባቢ ጥበቃ የሚሟገተው የአረንጓዴዎቹ ፓርቲ እንዲሁም የግራዎቹ ፓርቲ ናቸው ። ታዲያ የፊታችን እሁድ መስከረም 17 የሚካሄደው የዚህ ምርጫ አሸናፊ የክርስቲያን ዴሞክራት ህብረት ፓርቲ በጀርመንኛው ምህፃር የCDUዋ እጩ መራሂተ መንግስት አንጌላ ሜርክል እንደሚሆኑ በሰፊው መነገር ከጀመረ ከራረመ ። ይህ ያለቀለት ጉዳይ ነው ለሚሉት አስተያየት ሰጭዎች ፣ ከምርጫው በኋላ ሜርክል ከየትኛው ፓርቲ ጋር ተጣምረው መንግስት ይመሰርታሉ የሚለው ነው አሁን አአሳሳቢ ጉዳይ። ይኽውም ክርስቲያን ዴሞክራቶቹ እንደሚመኙት በጀርመንኛው ምህፃር FDP ከተሰኘዉ ከነፃ ዴሞክራት ፓርቲ ጋር መንግስት መመስረት የሚያስችላቸውን በቂ ድምፅ ያገኛሉ አያገኙም አንዱ አነጋጋሪ ነጥብ ሆኗል። ያ ካልሆነ ደግሞ አሁን አገሪቱን የሚመራው የእህትማማቾቹ ማለትም የክርስቲያን ዴሞክራት ህብረት CDU እና የክርስቲያን ሶሻል ህብረት CSU እንዲሁም የሶሻል ዴሞክራት ፓርቲ SPD ትልቁ ጥምር መንግስት ለሁለተኛ የስልጣን ዘመን ይቀጥላል አይቀጥልም እንዲሁ ሌላው ሰሞኑን ጀርመን ውስጥ ሲነሳ ሲጣል የሰነበተ ጉዳይ ነው ። ምርጫው ከመካሄዱ በፊት እንደሚያሸንፉ በሰፊው የተነገረላቸውን የCDU እጩ ተወዳዳሪ የመራሂተ መንግስት አንጌላ ሜርክልንና የተቀናቃኛቸውን የSPD እጩ ተወዳዳሪ የምክትል መራሄ መንግስትና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፍራንክ ቫልተር ሽታይንማየርን ማንነት በአጭሩ እንመልከት።

ሂሩት መለሰ/ሸዋዬ ለገሠ