1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ተፈናቃዮችን ለመርዳት ወጣቱ የሚያሳየው ተሳትፎ

ዓርብ፣ ጥቅምት 24 2010

ከኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ለተፈናቀሉ በብዙ ሺ የሚቆጠሩ የኦሮሚያ ክልል ተወላጆች መርጃ የሚሆን ድጋፍ የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች እየለገሱ እንደሆነ ይነገራል። በዛሬው የወጣቶች ዓለም ዝግጅት ወጣቶች የሚያደርጉትን ተሳትፎ በመጠኑ እንቃኛለን።

https://p.dw.com/p/2mueO
Hyänen Äthiopien
ምስል Reuters/T.Negeri

ተፈናቃዮችን ለመርዳት የወጣቱ ተሳትፎ

በኦሮሚያ እና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል አዋሳኝ አካባቢዎች በተካሄደው የጎሳ ግጭት ምክንያት ቁጥራቸው በውል የማይታወቁ ሰዎች ከሁለቱ ወገኖች ተገድለዋል፣ ከ 55 000 በላይ ሰዎች ከቀያቸው ተፈናቅለዋል። እነዚህን ተፈናቃዮች ለመርዳት ደግሞ በግልም ሆነ በተቋም ደረጃ የተለያዩ ተሳትፎዎች ሲካሄዱ ይስተዋላል። ከዚህም መካከል የወጣቱ ተሳትፎ አንዱ ነው።

ከሁለት ወር ገደማ በፊት የኦሮሞ ተወላጆች ከሶማሌ ክልል ከተፈናቀሉባቸው ከተሞች አንዷ በሆነችው የሐረር ከተማ እንደሚኖር እና ስሙ እንዳይጠቀስ የፈለገ አንድ ወጣት እንደገለፀልን፤ በወቅቱ ወጣቱ ተረባርቦ ተፈናቃዮቹን ለመርዳት ሞክሯል። « እስካሁን ግን በተጨባጭ የተደረገ ነገር የለም። እቤታቸውን ጥለው እንደመጡ ናቸው። ዘመድ ጋር ነው ያሉት።

የጅማ ዮኒቨርሲቲ ተማሪ የሆነው ሌላው ወጣትም የሚደረገው ድጋፍ ተጎጂዎቹ ጋር ስለመድረሱ ብዙም አያውቅም። የሚያውቀው እሱ እንደሚለው የጅማ ዩኒንቨርሲቲ ተማሪዎች የበኩላቸውን ድርሻ እየተወጡ መሆኑን ብቻ ነው። ወጣቱ እንደገለጸልን የገንዘብ ማሰባሰብ ነው ሲካሄድ የነበረው፤ ሌላው የዚሁ ዩኒቨርሲቲ ተማሪ የሆነው ወጣት ደግሞ ለሦስት ቀናት በተካሄደ አስቸኳይ ስብሰባ የተጠራን ተማሪዎች የምንጠጣውን ውኃ ለግሰን ነበር ይላል። « ስብሰባ ስንገባ የተሰጠን የኃይላንድ ውኃ ነበር። እሱ  ተሸጦ ብሩ ለእነሱ ይሰጥ ወይም ውኃው እራሱ ያሉበት ቦታ ተወስዶ ይሰጥ ብለን ነው ያልነው።»

Äthiopien Stadt Harar
ምስል DW/T. Waldyes

የኦሮሚያ ክልል ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አዲሱ አረጋ ከዚህ ቀደም ለዶይቸ ቬለ እንደተናገሩት የአሮሚያ ክልል ከሶማሌ ክልል ጋር በሚዋሰንባቸው ቦረና፣ ጉጂ፣ ባሌ፣ ምሥራቅ እና ምዕራብ ሐረርጌ ዞኖች በ2009 ዓ.ም ቁጥራቸው 416‚807 የኦሮሞ ተወላጆች ከቀያቸው ተፈናቅለዋል።

ምሥራቅ ወለጋ አንገርጉቴ ከተማ ነዋሪ የሆኑ አንድ ስማቸው እንዲገለጽ የማይፈልጉ ሰው እንደነገሩን በግልም ሆነ በድርጅት አካባቢያቸው ለመርዳት የአቅሙን ያህል እየሞከረ ነው።« ወገን ነው ለወገን ደራሽ ብለን ወጣቶች አሰባስበን  ኮሚቴ አቋቁመን እያሰባሰብን ነው።»አስተባባሪው የሚሰባሰበው የገንዘብ መጠንን 100,000 ለማድረስ እቅድ እንዳላቸው ይናገራሉ።  አስተባባሪውም ቢሆኑ ግን ገንዘቡ ተጎጂዎቹ ዘንድ በምን መልኩ እንደደረሰ አያውቁም። የሚያውቁት ማስረከባቸውን ነው።

የወለንጪቲ ነዋሪ እንደሆነ የነገረን እና ስሙን መጥቀስ ያልፈለገው ወጣት፤ እንደሚለዉም እሱም በሚኖርበት አካባቢ ለተፈናቃዮች ገንዘብ እየተሰበሰበ ነው። ከመንግሥት እና የግል ሥራ ከሚሰሩ ወጣቶች የተወጣጣ አምስት ሰዉ የያዘ ኮሚቴ ተቋቁሞ ገንዘብ እያሰባሰቡ ይገኛሉ። ገንዘቡ ሲሰበሰብ የሰጠዉ ሰዉ ስምና ምን ያህል ገንዘብ እንደሰጠ ይመዘገባል ይላይ ወጣቱ። እሱ እንደሚለው በአንድ ቀን ከ8,000 እስከ 10,000 የሚንሰበስብበት ቀን አለ።  «መንገድ ላይ እየዞርን ነዉ የምንሰበስበዉ። መኪና መንግሥት ይተባበረናል፣ ድምጽ ማጉያ እንከራያለን። ከዛ በማስታወቂያችን ዜጋ ለዜጋዉ እጁን እንዲዘረጋ እንጠይቃለን፣ ሁሉም አቅሙ የቻለዉን ያህል እና የኦሮሞነት ግዴታውን እንዲያወጣ እንጠይቃለን። እንዲህ አድርገን ነዉ ገንዘብ የምንሰበስበዉ። ከፍተኛ ገቢ የሚገኘዉ የገበያ ቀን ነዉ።»

Symbolbild US-Botschafter bei den UN - in Äthiopien
ምስል DW/E. Bekele

የገበያ ቀናቱ ቅዳሜና ማክሰኞ ናቸው። ለመሆኑ የተሰበሰበዉን ገንዘብ ለማን ነው የሚያስረክቡት? ለተፈለገዉ አላማም መዋሉንስ እንዴት ነዉ የሚያረጋግጡት? «በኦሮሚያ ኅብረት ሥራ ባንክ የተከፈተ የቁጠባ ደብተር አለ። እኛ እያደረግን ያለነዉ የማስተባበር ሥራ ነዉ። ከዛ ባለፈ ሌላ ከፍተኛ አካል አለ፣ ማለትም ባንኩና ችግሩን ለመፍታት የሚንቀሳቀሰዉ የመንግሥት አካል፣ እነሱ ናቸዉ ይህን ገንዘብ ወደ ተቸገረው ሕዝብ የሚያደርሱት ማለት ነዉ። እኛ ገንዘቡ ወደ ተፈለገዉ ቦታ መድረሱንና አለመድረሱን አጣርተን መቶ በመቶ የምናዉቅበት መንገድ የለም።» 

አሰላ ውስጥ ገንዘብ ከሚያሰባስቡ ወጣቶች አንዱ የሆነውና ከኮሚቴዎቹ አንዱ ነኝ ያለን ወጣት እንደገለፀልን ደግሞ ሰው በዉዴታ ከሚለግሰው በተጨማሪ በግዳጅ የሆነበትም አጋጣሚ እንዳለ እና ሁኔታው እንደማያስደስት ይናገራል። «

ከሶማሌ ክልል ለተፈናቀሉ የኦሮሚያ ክልል ተወላጆች ወጣቶች በግልና በቡድን ሆነው ለመርዳት የሚያሳዩትን ተሳትፎ የቃኘው  የወጣቶች ዓለም ዝግጅትን በድምፅ መከታተልም ይችላሉ።

ልደት አበበ

ሸዋዬ ለገሰ