«ቱታ አብሶሉታ» የቲማቲም ፀር
ማክሰኞ፣ ሰኔ 18 2005ቲማቲም የደሃ ቁርጥ እየተባለ ይወደሳል። ቢጠፋ ቢጠፋ እሱ እንኳ አይጠፋም በሚል። ሰሞኑን ግን ዋጋ መጨመሩ ብቻ ሳይሆን እንደዝዋይ ባሉ አካባቢዎች ከገበያም መሰወሩ ብዙዎችን ያሳሰበ ጉዳይ ሆኗል።
ለረጅም ዓመታት የደቡብ አሜሪካ የቲማቲም አምራች ገበሬዎችን ሲያሳዝን ኖሯል፤ በጎርጎሪዮሳዊዉ 2006ዓ,ም ጀምሮ ደግሞ ወደስፔን ገባና የገበሬዎችን ቲማቲም ያወድም ያዘ። ካለፉት አራት ወራት ወዲህ ደግሞ ኢትዮጵያ ዉስጥ ተመሳሳይ ጥፋቱን በቲማቲም ላይ ያደርስ ጀመር። ቱታ አብሶሉታ ይሉታል በሳይንሳዊ አጠራሩ፤ ፀረ ቲማቲም ነዉ፤ በደቡብ አሜሪካ እና በአዉሮጳ የቲማቲም ተክልን በማዉደም ይታወቃል። ካለፉት ጥቂት ወራት ወዲህ ደግሞ ወደኢትዮጵያ መግባቱ ተደርሶበታል።
በመልካሳ ግብርና ምርምር ማዕከል በእፀዋት ተባይ ምርምር ክፍል በተለይም በአትክልትና ፍራፍሬ ተባዮች ላይ ምርምር የሚያካሂዱት ዶክተር ጋሻዉበዛ አያሌዉ ኢትዮጵያ ዉስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ መከሰቱን እንደተደረሰበት ይገልጻሉ።
ቲማቲምና ሌሎችን እንደድንች፤ በርበሬና ቦሎቄ የመሳሰሉ ተክሎችን እንደሚጎዳ የተነገረለት ይህ ፍጥረት፤ ኢትዮጵያ ዉስጥ ከቦታ ቦታ ተዳርሶ ጉዳት ማድረሱን ባለሙያዎቹ ሲደርሱበት፤ ተባዩን ለማጥፋትና የአምራቾቹን ገበሬዎች የወደፊት ልፋት ለመታደግ ቀጣይ ጥረታቸዉን ቀጥለዋል። ከየካቲት ወር አንስቶ አገር ዉስጥ የሚገኙ የዘርፉ ባለሙያዎችን ከፍተኛ ትኩረት የሳበ ጉዳይ ሲሆን እስከዛሬ ያሉትን ጸረ ተባይ መድሃኒቶች በመላመዱ ፈተና ሳይሆን እንደማይቀር ይገመታል። ኢትዮጵያ ዉስጥ ደግሞ ከዚህ ቀደም ተከስቶ ስለማያዉቅ የተደረገ ዝግጅት አልነበረም። ዶክተር ጋሻዉበዛ ይህ ያህል ጉዳት ያደረሰዉ አስቀድሞ ባለመታወቁ እንጂ በቀጣይ መፍትሄ አያጣም ባይ ናቸዉ።
ሸዋዬ ለገሠ
አርያም ተክሌ