ቻድና የነዳጅ ዘይት ሀብት ሚናዋ
ቅዳሜ፣ ጥቅምት 2 2006በውጭው ዓለም ዘንድ ርዳታ በማቅረብ እና በምዕራብ እና በማዕከላይ አፍሪቃ ለሚካሄዱ ውዝግቦች መፍትሔ በሚፈለግበት ድርጊት ላይ ጉልህ ሚና በመጫወትዋ ብቻ እንድትታወቅ አድርገዋል። ፕሬዚደንት ኢድሪስ ዴቢ እነዚህን ሁለት ሚናዎች እንዴት ማዛመድ ቻሉ?
ቻድ ምንም እንኳን በነዳጅ ዘይት ሀብት ብትታደልም የተመድ ባወጣው የ187 ሀገራት የልማት ደረጃ መለኪያ መዘርዝር ላይ 184ኛውን ቦታ ይዛለች። ከቻድ ያነሰ ልማት ያላቸው ሀገራት ሞዛምቢክ፣ ዴሞክራቲክ ሬፓብሊክ ኮንጎ እና ኒዠር ብቻ ናቸው። በቻድ አማካዩ የኑሮ ዕድሜ 50 ሲሆን፣ በሀገሪቱ ከየሦስቱ ለአካለ መጠን ከደረሱት ዜጎች መካከል አንዱ ማንበብና መፃፍ አይችልም። ከ62 ሚሊዮኑ የቻድ ሕዝብ መካከልም 11 ከመቶው በቀን ከአንድ ዩሮ ባነሰ ገነዘብ ነው የሚኖረው። የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች እንደሚሉት፣ ለሀገሪቱ መንግሥት የማይመቹ ግለሰቦች በሆነ መንገድ ድምፃ አልባ እንደሚደረጉ የቻድን ጉዳይ የሚከታተሉት የልማት ጉዳዩች አማካሪ የሆኑት ማርቲን ፔትሪ ገልጸዋል።
« ቻድ ውስጥ አሁንም ተቃዋሚዎች ይታሰራሉ ወይም ለማስፈራራት ተግባር ይጋለጣሉ። ብዙዎች በዘፈቀደ ይታሰራሉ። በፖሊስ እና በጦር ኃይሉ ውስጥም ሙስና እና በሥልጣን አላግባብ መጠቀም ይታያል። በዚችው ሀገር አንድ ሰው መብቱን ቢገፈፍ ይህንኑ መብቱን በሕጋዊ መንግድ የማስከበር ዕድሉ የመነመነ ነው »
ቻድ ከአፍሪቃ በስተደቡብ ካሉት የአፍሪቃ ሀገራት መካከል በትጥቅ እና በጥንካሬ የታወቀ ጦር ያላት ሀገር ናት። ለዚሁ ተግባራቸውም ዴቢ ከአሥር ዓመት በፊት በተገኘው የነዳጅ ዘይት ሽያጭ ገቢ መጠቀማቸውን በፍራይቡርግ ዩኒቨርሲቲ በሚገኘው የአርኖልት ቤርግሽትሬሰር ተቋም የቻድ ተመራማሪ ሄልጋ ዲኮቭ አስታውቀዋል።
« የቻድ መንግሥት በሚቆጣጠረው በነዳጅ ዘይቱ ገቢ የጦር ኃይላቸውን ማጠናከራቸው ባንድ በኩል የሀገሪቱን የውጭ ፖለቲካ በሌላ በኩል ደግሞ በሀገር ውስጥ ሥልጣናቸውን ለማጠናከር ረድቷል። የምርጫ ዘመቻንም እንዲያውሉት አስችሏቸዋል። ገነዘቡ የሚጠቅሙዋቸውን ለማሠልጠን እና የፖለቲካ ተቀናቃኞቻቸውን ለመደለሉ ተግባር በይበልጥ ተስፋፍቷል። »
በዚህ አንፃር የቻድ መንግሥት በሀገሪቱ የሚታየውን ድህነት ለማጥፋቱ ወይም የመሠረተ ልማቱን ለማስፋፊያው ተግባር የመደበው ገንዘብ ንዑስ ሆኖ ነው የተገኘው።
የፈረንሣይ ፕሬዚደንት ፍራንስዋ ኦሎንድ ሰሜናዊ ማሊን ተቆጣጥረው በነበሩት ፀንፈኛ ሙሥሊሞች አንፃር በማሊ መንግሥት ጥሪ ወታደራዊ ርምጃ በጀመሩበት ጊዜ ፕሬዚደንት ዴቢ በፈረንሣይ መሪነት ለተላከው ጣልቃ ገቡ ጓድ 2400 ወታደሮችን ማቅረባቸው የሚታወስ ነው። በዚህም ዴቢ በዓለም አቀፉ መድረክ ላይ እውቅና ሲያገኙ፣ በተለይ ግን በሀገር ውስጥ የሚፈፀሙት የሰብዓዊ መብት ረገጣ እንደሚጠበቀው እንዳይተች ለማድረግ ጠቅሟቸዋል፣ ይላሉ ሄልጋ ዲኮቩ፣
« ምክንያቱም ዴቢ ሁሌ ራሳቸውን በአል ቃይዳ እና በቦኮ ሀራም አንፃር፣ እንዲሁም፣ በክርስትና እና በእሥልምና እምነት ተከታዮች መካከል እኩልነት እንዲኖር የሚታገሉ አድርገው ነው የሚያቀርቡት። »
የልማት ጉዳዮች አማካሪ ማርቲን ፔትሪም ይህንኑ አረጋግጠዋል።
« ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ለፀረ ሽብርተኝነቱ ትግል የዴቢን ትብብር ስለሚፈልግ ግዙፍ ጫና አላሳረፈባቸውም። »
በተለይ የቀድሞዋ ቅኝ ገዢ ፈረንሣይ ከቻድ ጋ የጠበቀ ግንኙነት ነው ያላት። ፈረንሣይ ዴቢ እአአ በ1990 ዓም ዴቢ የቀድሞውን ፕሬዚደንት ሂስኔ ሀብሬን ከሥልጣን እንዲያስወግዱ እና በኋላም በ 2008 ዓም በአንፃራቸው የተሰነዘረውን የዓማፅያን ጥቃት እንዲደመስሱ መርዳቷ አይዘነጋም።
ዴቢ በሚከተሉት ሥልት አማካኝነት በአጋሮቻቸው አኳያ ጥቅማቸውን ለማስጠበቅ እንደሚሞክሩ በጀርመን የሀለ ከተማ በሚገኘው የማክስ ፕላንክ ተቋም የሚሰሩት የቻድ ተወላጅ የሆኑት የማህበራዊ ጥናት ተመራማሪ ሬማጂ ዋንቲ ጠቁመዋል።
« የቻድን ወታደራዊ ጥንካሬ በአጋሮቻቸው አኳያ የሚፈልጉትን አቋም ለመቀያየሪያ ይጠቀሙበታል። ለምሳሌ ፈረንሣይ ለተወሰነ ጉዳይ የቻድን ትብብር በምትፈልግበት ጊዜ፣ ለምሳሌ፣ በማሊ ተልዕኮ ላይ በምትረዳበት ጊዜ፣ ያኔ ቻድ አንዳንድ የማይመቹ ጉዳዮችን አታንሱብኝ የሚል የራሷን ጥያቄ በምላሹ ታቀርባለች ማለት ነው፣ ይህ ዓይነቱ አሰራር ቻድ ያካባቢው የጦር ኃያል መንግሥት መሆንዋ ያስከተለው አሳዛኝ መዘዝ ነው »
ይህችው የማዕከላይ አፍሪቃ ሀገር ለፈረንሣይ ኤኮኖሚያዊ ብቻ ሳይሆን ሥልታዊ ትርጓሜዋም ከፍተኛ ቦታ ይዞዋል። የፈረንሣይ ጦር በቻድ መዲና ንጃሜና እና በምሥራቃዊ የሀገሪቱ ከፊል በሚገኘው የአቤቼ አካባቢ ሁለት ዋነኛ የጦር ሠፈሮች አሉት።
ኢድሪስ ዴቢ በሚከተሉት ሥልት በውጭው ፖለቲካ ላይ ለአፍሪቃ ትልቅ ሚና መያዛቸውን ለማጉላት የሚያደርጉት ጥረታቸው ምን ያህል ውጤታማ መሆኑን የአፍሪቃ ህብረት ቻድ በተመድ የፀጥታ ጥበቃ ምክር ቤት ውስጥ ቋሚ መንበር ለመያዝ በ2014 /15 የምታስገባዉን ማመልከቻ ለመደገፍ ያሳለፈው ውሳኔ በግልጸ አሳይቶዋል።
ዲርከ ኮፕ/አርያም ተክሌ
አዜብ ታደሰ