1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አሜሪካ ፣ ኤርትራን በሃይማኖት ጨቋኝነት መክሰሷና የኤርትራ ምላሽ፣

ሐሙስ፣ ጥቅምት 19 2002

የዩናይትድ እስቴትስ መንግሥት ው, ጉ, ሚ, መ/ቤት፣ ባቀረበው የሃይማኖት ነጻነት ይዞታ ዓመታዊ ዘገባው፣ የሃይማኖት መብት ከሚነፍጉ አገሮች አንዷ ኤርትራ ናት በማለት ከትናንት በስቲያ ወቅሶ ነበረ።

https://p.dw.com/p/KIqf

ኤርትራ ምን ምላሽ እንዳላት፣ ተክሌ የኋላ ፣ የሀገሪቱን የማስታወቂያ ሚንስትር አቶ አሊ አብዱን አነጋግሮ የሚከተለውን ዘገባ አጠናቅሯል።

የዩናይትድ እስቴትስ መንግሥት የውጭ ጉዳይ ሚንስቴር በይበልጥ፣ ሰሜን ኮሪያንና፣ ኢራንን፣ በተጨማሪም ምያንማርን ፣ ቻይናን ፣ ዑዝቤኪስታንን፣ ስዑዲ ዐረቢያን፣ ሱዳንና ኤርትራን ፣ የሃይማኖት ነጻነት የገፈፉ አገሮች ናቸው ሲል በዓመታዊ ዘገባው ላይ ከሷል። በሃይማኖት ረገድ ፣ በተለይ ኅዳጣን፣ የባሰ ጭቆና ይደርስባቸዋልም ብሏል። በዚህ ጉዳይ የመንግሥታቸው አስተያያት ምን እንደሆነ ያነጋገርናቸው አቶ አሊ አብዱ እንዲህ ነበር ያሉን--

«እንደውነቱ ከሆነ ኤርትራ፣ አብሮ፣ ተቻችሎ በመኖርና በሃይማኖት መጣጣም ፣ ለዓለም አርአያ የሆነች(በምሳሌነት ልትጠቀስ የምትችል) ሀገር ናት። ግልፅ የሆነ ኅብረተሰብ ነው ያለን። ኤርትራ ፣ ኅብረተሰቧም ጥንታዊ ሃይማኖት የሚያመልክ (ያለው)ነው። ስለዚህ፣ በአንጻሩ ኤርትራ የአብሮነትና የሃይማኖት መቻቻል ተምሳሌት ናት»።

ኤርትራ፣ ባለፉት ጊዜያት ፤ የአፍሪቃን ቀንድ አካባቢ እንዳይረጋጋ፣ የምታደርግ ሆናለች የሚል ዓይነት ክስ ፤ ከአሜሪካም ከተባበሩት መንግሥታትና ከአንድ አካባቢዎች ክስ ሲሠነዘርባት መቆየቱም ይታወሳል፣ ይህም ቢሆን ፣ አቶ አሊ እንደሚሉት «መሠረተቢስ ክስ ነው»።

«ይህ እንዲያው እጅግ የተጋነነ የኤርትራን ደኅንነት ከማይሹ የመነጨ አገላለጽ ነው ። እኛ ቀላል ጥያቄዎችን ስናቀርብ ነበር። ማረጋገጫ ካላችሁ አቅርቡ ብለን! እስቲ፣ በጠራራ ፀሐይ፣ በግልፅ መረጃችሁን አቅርቡና አሳዩን በማለት ባለፉት 4 እና 5 ዓመታት ጠይቀናቸዋል። የመገናኛ ብዙኀንም ሁሉ፣ እ ጎ አ በ 2006 ዓ ም፣ በመቅዲሹ፣ ሶማልያከ 2000 በላይ ኤርትራውያን ወታደሮች ይገኛሉ የሚለውን የፈጠራ ወሬ ሲያስተጋቡ ነበር። ይህን የተከታተለና ፣ ወሬውን ያናፈሱትን ወገኞች ተከታትሎ የጠየቀ ግን የለም። እንደገናም፣ በተለያየ ደረጃ በኤርትራ ላይ ጣታቸውን እየቀሠሩ ጥፋተኛ ሊያደርጓት ይሞክራሉ። በማንኛውም መለኪያም ሆነ ደረጃ ይህ የማይታመንና ስንኩል ምክንያት ነው።»

ክሱ መሠረተቢስ ከሆነ ለምን ተሠዘነረ!?

«ምክንያቱ በጣም ቀላል ነው። ኤርትራ፣ ነጻ የፖለቲካ መሥመር መከተልን መርጣለች ኤርትራ ገንቢ በሆነ መልኩ ሰላም መቻቻልና መረጋጋት እንዲሠፍን ነው ባካባቢው ጥረት የምታደርገው።»

የተለያዩ ኅዳጣን የሃይማኖት ተከታዮች፣ የባሰ ጭቆና ይደርስባቸዋል ነው የሚባለው። እርስዎ ምን ይላሉ?

«የፖለቲካ ሃይማኖትን፣ በኅዳጣን ወይም በአፈንጋጭ ወገኞች ስም አንቀበለም። ከኅብረተሰቡ የሚያፈነግጡ ወገኖችን፣ በግልፅ፣ የገቢ ምንጫቸውን እንዲያሳውቁ ጠይቀናቸው ነበር። ይህ፣ «የትም ቢሆን አይሆንም» ብትለኝ፣ በመቶ የሚቆጠር ምሳሌ ላቀርብልህ እችላለሁ። በምትኖርበት አገርም ሆነ በዩናይትድ እስቴትስ፣ እንዲሁም ትናንት፣ አፈንጋጭ የሆኑ ወገኞች በፈረንሳይ የደረሰባቸውን ሰምተናል። የጠየቅነው፣ እንዲያስመዘግቡ፣ ያልተገለጠ ወይም ድብቅ የውጭ እርዳታ እንዳይኖራቸው ነው። አለበለዚያ፣ ይህ የፖለቲካ ሃይማኖት ነው፣ ማለት ነው።»

ተክሌ የኋላ/አርያም ተክሌ