1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አስፈሪና አሳሳቢ የረሃብ አደጋ በኬንያ፣

ሐሙስ፣ ጥር 28 2001

ሰብሉ አልያዘም፣ አትክልቱ ደርቋል። የአርሻ ማሳዎች አቧራ ለብሰዋል። ምሥራቅ አፍሪቃዊቷ ሀገር፣ ኬንያ፣ ዘንድሮ መቅሠፍት ነው ያንዣበበባት!። የረሃብ ዕልቂት የሚያሠጋቸው ሰዎች አኀዝ ከ 10 ሚልዮን ቢበልጥ እንጂ አያንስም።

https://p.dw.com/p/Gnv5
ብርቱ ረሃብ በተደቀነባት ኬንያ፣አንዲት ሴት ማሣ ላይ፣ምስል picture-alliance/ dpa

በመሆኑም ፕሬዚዳንት ምዋይ ኪባኪ፣ ከ 3 ሳምንት ገደማ በፊት፣ የአስቸኳይ ሁኔታ አዋጅ ከማውጣታቸውም፣ ለተራቡት ወገኖች የገንዘብ እርዳታ እንዲቀርብ ጠይቀዋል።

ድርቁ ክፉኛ ያጠቃው ደቡብ ምሥራቃዊውን ኬንያ ሲሆን፣ በዚያ የሚኖሩት አርሶ-አደሮች፣ ዘንድሮ ከማሳቸው የሰበሰቡት አዝመራ አልነበረም ፣ ባዶ እጃቸውን ነው የቀሩት። የአገሪቱ ቴሌቭዥን እንዳሳየው፣ የአርሶ አደሮቹ ቤተ-ሰቦች፣ የረሃብን ሥቃይ ለማስታገስም ሆነ ህይወታቸውን ለማትረፍ፣ በዱር ከሚገኘው የማይበላ ፍሬ፣ እየሸመጠጡ በመቀቀል መመገብ ግድ ብሏቸዋል።

ኪዋንዛኒ በተባለችው መንደር የሚኖሩት ፣ 13 ቤተሰብ የሚያስተዳድሩት ወይዘሮ ሞኒካ ሳካዮ፣ አንድ የፕላስቲክ ኬሻ እንደያዙ በሰጡት ቃል ላይ እንዲህ ነበረ ያሉት----

«ይመልከቱ፣ ከረጢቱ ባዶ ነው። ዛሬ፣ በቀጭኑ አፍልቅልቀን የምንምገበው ሾርባም እንኳ የለንም።»

በአርግጥም ይላል ይህን ዘገባ የላከልን ጋዜጠኛ ዊም ዶረንቡሽ፣ ሴትዮዋ በከረጢታቸው ከዱቄት ብናኝ በሰተቀር ምንም የላቸውም። ወይዘሮ ሞኒካ ሳካዮ፣ በእርሻ መሬታቸው ላይ የተዘራው እህል በቡቃያው መድረቁን በጎተራ ተቀምጦ የነበረው እህል ተሟጦ ማለቁን ፣ የሚላስ የሚቀመሰ ለመግዛትም፣ ገንዘብ እንደሌላቸው ነው ያስረዱት ።

እንደ ሳካዮ ቤተሰብ ፣ በምሥራቅና በሰሜን ኬንያ፣ በዝናብ ፍጹም መጥፋት ለችጋር የተዳረጉት እጅግ በዛ ያሉ ናቸው። በዙዎቹ ቢበዛ፣ በቀን አንድ ጊዜ ይሆናል ትንሽ የሚቀመስ የሚያገኙት። ችግሩ ደግሞ ይበልጥ እየተባባሰ በመሄድ ላይ ነው። ለዚህም ሳይሆን አልቀረም የአገሪቱ ርእሰ-ብሔር ማዋይ ኪባኪ የሚከተለውን አዋጅ እንዲነገር ያደረጉት።

«መንግሥቴ፣ በአገሪቱ የተከሠተውን ረሃብ ብሔራዊ ድቀት መሆኑን፣ ከዛሬ ጀምሮ በሚጸና አዋጅ፣እንዲታወቅ ያደርጋል።»

ፕሬዚዳንት ምዋይ ኪባኪ፣ 10 ሚልዮን የተራቡ ዜጎችን መመገብ ይቻል ዘንድ፣ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ አሁን 300 ሚልዮን ዩውሮ እርዳታ እንዲያቀርብ ጠይቀዋል። ይሁንና የደረሰውን ብርቱ የረሃብ አደጋ በተመለከተ የአገሪቱ ጠበብት እየተከራከሩበት ነው። ኬንያዊው የኤኮኖሚ ምሁር ጀምስ ሺክዋቲ ፣ ረሀቡ ሰው-ሠራሽ ነው ባይ ናቸው።

«ይህ የፖለቲካ ችግር ነው። ከድርቅ ጋር፣ ከምግብ እጥርት ጋር በምንም ዓይነት የሚያገናኘው ጉዳይ አይደለም። »

ሺክዋቲ የተናገሩት ውሸት አይደለም። ከፍተኛ ሥልጣን ያላቸው ፖለቲከኞችና ሥውር ነጋዴዎች፣ ለክፉ ቀን የተቀመጠ እህል እያስወጡ፣ ዋጋውንም ሆን ብለው በርካሽ ዋጋ እየገዙ መልሰው በውድ ዋጋ እንዲሸጥ ማድረጋቸው አልቀረም። የኬንያ አርሶ አደሮች ማኅበር ሊቀመንበር እንዳዋቲ ካሪዩኪ----

«በዚህ የቀውስ ጊዜ እንኳ ፣ ስንጥቅ የሚያተርፉ ሰዎች አልታጡም። ለተራቡ ኬንያውያን ተብሎ የተቀመጠ እህል አየገዙ፣ ወደ ውጭ በማውጣት፣ ትርፍ በሚያስገኝ ዋጋ ይሸጡታል።»

እንደተባለው፣ የኬንያውያን መደበኝ ምግብ የሆነውን በቆሎ ፣ መጠኑ 40,000 ቶን ያህል ወደ ደቡብ ሱዳን በመላክ ለእርዳታ ድርጅት እንዲሸጥ ያደረጉ አሉ። እዚህም ላይ የምዋይ ኪባኪ መንግሥት፣ በሙስና ስለመዘፈቁ ፣ እርዳታ ለጋሽ መንግሥታት በሚገባ እንደሚያውቁ አላጠራጠረም። በጀርመን ዓለም አቀፍ የረሃብ መከላከያ ድርጅት Welthungerhilfe የሚሠሩት የግብርና ኢንጂኔር ኤሊያ ሙሊ፣ ለረሀቡ መንስዔዎች ናቸው ሳላሏቸው ዋና- ዋና ምክንያቶች ሲያስረዱ-----

«የአየር ንብረት ለውጥ -ይህ አንዱ ነው። የዝናም መጥፋት ዐቢይ ድርሻ አለው። ለመስኖ የሚውል ውሃ መታጣቱም ሌላው ችግር ነው። ህዝብ እንዲዘጋጅ ማድረግ የማያስችል መጥፎ የመንግሥት አመራር ዘይቤም አስተዋጽዖ አለው። አመራሩ፣ በየጊዜው ለሚደርሰውና ለሚያጋጥመው የድርቅም ሆነ የረሃብ አደጋ ፣ ህዝቡ ተዘጋጅቶ እንዲጠባበቅ አላስቻለም። »

ኬንያ ፣ በምርጫ ውዝግብ ሳቢያ፣ 1,500 ያህል ህዝብ ከተገደለባት፣ በመቶ ሺ የሚቆጠር ህዝብ ፣ ከቀየው ከተፈናቀለባትና አንድ ቢልዮን ዶላር ያህል የንብረት ኪሣራ ከደረሰባት ወዲህ ፣ ከዚያ ፣ እንደ እሳተ-ገሞራ ከፈነዳው ችግር እስካሁን አላገገመችም።

ይሁንና፣ ከኬንያዊ አባት የተወለዱት አዲሱ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ዖባማ፣ ኬንያውያን ከጠባብ የጎሣ ስሜት ወጥተው በኩራትና በአንድነት መንፈስ እንዲተባበሩ፣ አርአያ ሳይሆኑላቸው አልቀሩም።

T Y,NM

Quellen: AP,RTR,DW

►◄