1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አነስተኛ የኃይል ማመንጫዎች የማምረት እቅድ

ረቡዕ፣ ሰኔ 22 2008

በኢትዮጵያ አዳዲስ የንግድ ሐሳብ ይዘው ወደ ገበያ የሚገቡ ጀማሪ ኩባንያዎች በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ፤ባህላዊ አልባሳት እና የቆዳ ውጤቶች ላይ ትኩረት ሲያደርጉ ይታያል። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኤሌክትሪክ ምህንድስና ወጣት መምህር አማረ አሰፋ ደግሞ ከንፋስ፤ ኃይል የሚያመነጩ ቁሶችን በገጠራማ አካባቢ ለሚገኙ ዜጎች ለማቅረብ አቅዷል።

https://p.dw.com/p/1JFnY
China Windenergie
ምስል Getty Images/AFP/L. Jin

አነስተኛ የኃይል ማመንጫዎች የማምረት እቅድ


ወጣት መምሕር አማረ አሰፋ ከንፋስ «ኢነርጂ ሶሉሽን» የተባለ ጀማሪ ኩባንያ መስራች ነው። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቴክኖሎጂ ኢንስቲቲዩት የኤሌክትሪሲቲ ምህንድስና መምህር የሆነው አማረ ከጓደኛው ጋር የመሰረተው ኩባንያ እስከ አንድ ኪሎ ዋት የሚደርስ የኤሌክትሪክ ኃይል ከንፋስ የሚያመርቱ ቴክኖሎጂዎችን በገጠራማ አካባቢዎች ለሚኖሩ ዜጎች የማቅረብ እቅድ አለው። ድርጅታቸው በርካታ ውጣ ውረዶችን ማለፍ የሚጠበቅበት ጀማሪ ነው። እቅዱም ዛሬ የተጀመረ አይደለም።

ኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ኃይል ልታመነጭ ከምትችልባቸው ፀሀይ፤ንፋስ እና ጄኦተርማል የኃይል ምንጮች የተጠቀመችው 1 በመቶ ያክሉን ብቻ ነው። በዓለም ባንክ መረጃ መሰረት ከጎርጎሮሳዊው 2009 . እስከ 2012 ዓ.ም ባሉት አመታት አምስት ግድቦች የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጨት ጀምረዋል። አሁንም በርካታ የኃይል ማመንጫ ግድቦች እዚህም እዚያም ግንባታ ላይ ናቸው። ይህ ግን ፈጽሞ የአገሪቱን ፍላጎት የሚያሟላ አልሆነም። በገጠራማ አካባቢዎች የሚኖሩ ዜጎች ይህ እድል አልደረሳቸውም። እነ አማረ የኤሌክትሪክ ኃይል ማግኘት ያልቻሉ ኢትዮጵያውያንን ኢላማ አድርገዋል።

የኢትዮጵያ ዉስጥ አዳዲስ የፈጠራ ሐሳቦች ይዘው ብቅ ለሚሉ ጀማሪ ኩባንያዎች በርካታ ፈተናዎች አሉት። የመንቀሳቀሻ ካፒታል እጥረት፤ የመንግስት ድጋፍ አለመኖር፤የመስሪያ ቦታ እጦት እና አበረታች ያልሆነ የገበያ ሥርዓት ቀዳሚዎቹ ናቸው። እነ አማረም የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫውን ለማምረት የሚያስችላቸውን በቂ ገንዘብ አላገኙም። ኃይል ማመንጫውን ለማምረት የሚያስፈልጉት ግብዓቶች ወይም ቁሳቁሶችን ከገበያ ማግኘት ሌላው ፈተናቸው ነው።

የወጣት አማረ አሰፋ ድርጅት ወደ ፊት በጸኃይ ኃይል የሚሰሩ አነስተኛ ኪዮስኮችን በማምረት በገጠራማ አካባቢዎች ለማቅረብም አቅደዋል። ሸቀጦችን ለመሸጥ በሚያገለግሉት አነስተኛ ሱቆች ጣሪያ ላይ የኤሌክትሪክ ኃይል የሚያመርቱ ቁሳቁሶች ይገጥምላቸዋል። በዚህ መንገድ የሚመረተው አነስተኛ ኤሌክትሪክ ለተንቀሳቃሽ የእጅ ስልኮች የታቀደ ነው። አማረ አሰፋ ኩባንያቸው እቅዱን ለማሳካት ሊገጥሙት የሚችሉ ፈተናዎችን አጥንተዋል።

እሸቴ በቀለ
ነጋሽ መሐመድ