1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አካል ጉዳተኝነት በአፍሪቃ

ረቡዕ፣ መጋቢት 17 2006

በዓለም ላይ ቁጥራቸው ከአንድ ቢሊዮን የሚበልጥ አካል ጉዳተኞች አሉ ። አብዛኛዎቹም በማደግ ላይ ባሉ ሃገራት ውስጥ ነው የሚኖሩት ። በተለይ በአፍሪቃ አካል ጉዳተኞች ብዙውን ጊዜ አድልዎና መገለል የሚደርስባቸው ሲሆን ብዙዎቹም ስር በሰደደ ድህነት ውስጥ ነው ያሉት ።

https://p.dw.com/p/1BUvV
Südafrika Junge im Rollstuhl
ምስል Getty Images
Rachel Kachaje
ካቻጄምስል DW/Julia Hahn

አካል ጉዳተኛ ባለሥልጣናትና የመብት ተሟጋቾች እነዚህ የህብረተሰብ ክፍሎች እንደ ማናኛውም ሰው መደበኛ ህይወት እንዲመሩ ለማስቻል እየታገሉ ነው ። ፍሬድሪሽ ኤበርት በተባለው ተቋም ግብዣ ከተለያዩ የአፍሪቃ አገራት በቅርቡ በርሊን የመጡ አካል ጉዳተኞች ለዶቼቬለዋ ዩልያ ሃን ልምዳቸውን አጋርተዋል ። በርሊን በሚገኝ አንድ ትልቅ የልብስ ላውንድሪ ውስጥ 25 አካል ጉዳተኛ ሴቶችና ወንዶች ይሠራሉ ። የጠረጴዛ ልብሶች ፎጣዎች እን ልብሶች ይተኩሳሉ ያጣጥፋሉ ። አካል ጉዳተኞቹ የሚሰሩበት ሞሳይክ የተባለው ተቋም አካል ጉዳተኖች ህብረተሰቡ ጋር ተቀላቅለው እንዲሰሩ ሥልጠና የሚሰጥና በስራው ዓለም ብቁ ና ተፎካካሪ ሆነው እንዲቀርቡ የሚያስችል ድርጅት ነው ። ከአፍሪቃ ልምድ ለመቅሰም ተጋብዘው የመጡ አካል ጉዳተኞች ይህን ድርጅት የመጎብኘት እድል አጋችሟቸው ነበር ። ከመካከላቸው አንዷ በማላዊ የአካል ጉዳተኞች መብት ሚኒስትር ራሄል ካቻጄ፣ የተመለከቱት ሁሉ ለአካል ጉዳተኞች

መደረግ የሚገባው መሆኑን ነበር የተናገሩት ። በርሳቸው አስተያየት ለአካል ጉዳተኞች የሚከናወነው ሁሉ ከሰብዓዊ መብታቸው ጋር የተያያዘ መሆን ይኖርበታል ።

«ስለ አካል ጉዳተኞች ጉዳዮች ስንነጋገር የችሮታ ጉዳይ አይደለም ይልቁንም የሰብዓዊ መብት ጉዳይ እንጂ ።ሁሉም ሰው ጉዳዩን ከከሰብዓዊ መብቶች ጋር አገናኝቶ ማሰብ አለበት ። እንደሚመስለኝ ይህ አሁን የምንሰራበት መስክ ነው ብዬ አስባለሁ ። »

ካቻጄ ይህን ሲሉ ሌላዋ አካል ጉዳተኛ ፊታሊስ ዌሬ በተባለው የሚስማሙ መሆናቸውን ራሳቸውን እየነቀነቁ ይገልጹ ነበር ። ኬንያዊቷ ዌሪም በአካል ጉዳተኛ መገልገያ ተሽከርካሪ ወንበር ነው የሚንቀሳቀሱት ። ከ20 ዓመት አንስቶ ለአካል ጉዳተኞች መብት ይታገላሉ ። ችግሩን በግልፅ ማሳወቁ እጅግ አስፈላጊ ነው ይላሉ ። ምክንያቱም ዌሪ እንደሚሉት በብዙ የአፍሪቃ ሃገሮች እንደ ቅጣት ወይም ከሰማይ እንደ ወረደ ቁጣ ተደርጎ ይወሰዳልና ።

Symbolbild Behinderung
ምስል Fotolia/apops

« ዛሬም ማግለል አለ ። አሁንም አካል ጉዳተኛ ልጆቻቸውን የሚደብቁ ወላጆች አሉ ። ሰዎች በአካል ጉዳተኝነታቸው ያፍራሉ ። ስለዚህ አካል ጉዳተኝነት በሚስጥር የሚያዝ መሆን እንደሌለበት ብዙ መረጃዎችን መስጠት አለብን ። የአካል ጉዳት ሊከሰት እንደሚችል ማንኛውም ሰው አካል ጉዳተኛ ሊሆን እንደሚችል ሰዎች እንዲረዱ የተጠናከረ ትምሕርት መስጠት አለብን ።»አፍሪቃ ውስጥ ትክክለኛው የአካል ጉዳተኛ ቁጥር ባይታወቅም ፣ ቁጥራቸው ከ100 ሚሊዮን እንደሚበልጥ ይገመታል ። እጎአ በ2011 በወጣው የዓለም ጤና ድርጅትና የዓለም ባንክ ዘገባ መሠረት እነዚህ የህብረተሰብ ክፍሎች ትምህርት ህክምና እና ሌሎች ማህበራዊ አገልግሎቶች የማግኘት እድላቸው ዝቅተኛ ነው ። ብዙውን ጊዜም ስር የሰደደ የድህነት ህይወት ነው የሚገፉት ።ደቡብ አፍሪቃዊው አካል ጉዳተኛ ሉክስ ማቶቶ መንግሥታዊ ባልሆነውና በአካል ጉዳተኞች በሚመራው በደቡብ አፍሪቃ የአካል ጉዳተኖች ድርጅት ውስጥ ነው የሚሰራው ። በሃገሩ በደቡብ አፍሪቃ አካል ጉዳተኛም ሆነ ሌላው ሰው እኩል የስራ እድል እንዲኖረው ነው ምኞቱ ።

Looks Matoto
ማታቶምስል DW/Julia Hahn

« አካል ጉዳተኞች ሰርተው ገንዘብ ማግኘት ይፈልጋሉ ። በልገሳ ለምን ይደሰታሉ ? ተቀጥረን መሥራት እንፈልጋለን ። አሮጌ ጫማዎችን ለሚጠግኑ ሰዎች መስራት አንፈልግም ። ጫማ የሚያመርቱ ፋብሪካዎች ባለቤት መሆን ነው የምንፈልገው ። »የማታቶ ሃገር ደቡብ አፍሪቃ የአካል ጉዳተኞች መብቶች ጥበቃን በወረቀት አስፍራለች ። ጥበቃ የሚያድርጉላቸው በርካታ ህጎችም አሏት ህገ መንግሥቱም አድልዎን ይገድባል ። እንደ ኬንያና ማላዊ ደቡብ አፍሪቃም የተባበሩት መንግሥትት ድርጅት የአካል ጉዳተኞች መብቶች ጥበቃ ስምምነት ፈርመዋል ። ሆኖም የእነዚህ ሰዎች የእለት ተዕለት ህይወት በችግር የተሞላ ነው ። የአክል ጉዳተኞች መገልገያ ተሽከርካሪ ወንበር መነፅሮች እና ሐኪም ማግኘት ለብዙዎቹ ከአቅማቸው በላይ ነው ። በተለይ በገጠር አካባቢዎች ለነርሱ እንቅስቃሴ ከባድ ነው መንገዶች አስቸጋሪ ሲሆኑ የህዝብ አገልግሎት መስጫ ስፍራዎችም ለእነርሱም ታስበው አይሰሩም ።እነዚህን ሁሉ ችግሮች መወጣት ከባድ ሥራ ይጠይቃል ። ሚኒስትር ካቻጄም ይህ ግዙፍ ችግር ይገታል የሚል ብዥታ የላቸውም ። አካል ጉዳተኞች እንዲፈፀምላቸው ከሚጠብቁት ነገር በአመዛኙ አይሟላም ። ሆኖም ካቻጄም የጀርመን ጉብኝታቸው ብርታት ሰጥቷቸዋል ።

ሂሩት መለሰ

ነጋሽ መሀመድ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ