1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አዲሱ የተመድ የልማት ዕቅድ

ሰኞ፣ መስከረም 17 2008

ለቅዱ ገቢራዊነት 2500 ቢሊዮን ዶላር ያስፈልጋል።አምና አዲስ አበባ ላይ በተደረገዉ ድርድር የግል ባለሐብቶችም ገንዘብ ያዋጡ የሚል ሥምምነት ላይ ተድርሷል።የቦኑ ጥናት ድርጅት ሐላፊ የንስ ማርቴንስ ግን የግል ባለሐብቶች መሳተፋቸዉን ሲበዛ ይጠራጠራሉ።

https://p.dw.com/p/1GdpT
ምስል UN

[No title]

አሥራ-አምስት ዓመታት ያስቆጠረዉ የተባበሩት መንግሥታት የዓመአቱ የልማት ግቦች (MDG) ዘንድሮ በአዲስ ተቀይሯል።ባለፈዉ አርብ የተጀመረዉ የድርጅቱ የመሪዎች ጉባኤ ያፀድቀዋል ተብሎ የሚጠበቀዉ «ዘላቂ የልማት ግቦች» (SDG-በምሕፃሩ) የተሰኘዉ አዲሱ ዕቅድ እንደ ስሙ ሁሉ ዘላቂ እና የሁሉንም ዓለም ልማት ለማሳደግ ያለመ ነዉ።የሔለ የፕሰን ዘገባን ነጋሽ መሐመድ እንደሚከተለዉ አጠናቅሮታል።

«ይሕ የሕዝብ አጀንዳ ነዉ።ድሕነትን በሁሉም መልክና ባሕሪዉ፤ ማንም ሳይቀር፤ በሁሉም ሥፍራ የማጥፋት የድርጊት መርሐ-ግብር።» አሉት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ ፓን ጊ ሙን።ተዘመረለትም።የተባበሩት መንግሥታት የሴቶች ጉዳይ ድርጅት ሐላፊ ፉምዚሌ ማላምቦ-ንግኩካ ደግሞ ባቃጅ፤ ተግባሪዉ በትዉልዳቸዉ ይኮራሉ።«ድሕነትን የማጥፋቱ ዕድል ያለን የመጀመሪያዉ ትዉልድ ነን።በሴቶችና በወንዶች መካካል ያለዉን የሥልጣን ግንኙነት ለመለወጥም የመጀመሪያዉ ትዉልድ ነን።»

እየተዘመረ፤ እየተጨበጨበለት፤እየተደነቀ-እየተወደሰም ነዉ።ዘላቂ የልማት ግቦች። SDG።አስራ-ሰባት ግቦች ያሉት አዲሱ ዕቅድ በቀዳሚዉ (MDG) ከግብ ያልደረሱ ማስፈፀምን ያካትታል።ከአሮጌዉ ከሚለይባቸዉ አንዱ-እንደቀዳሚዉ ለአዳጊ ሐገሮች ብቻ ሳይሆን ለበለፀጉትም ያለመ መሆኑ ነዉ።«አዲሶቹ ዕቅዶች ሁለንተናዊ ናቸዉ።ይሕ ማለት ጀርመንን ጨምሮ ሐገራት በሙሉ መካተት የሚችሉበትና መካተት ያለባቸዉም ነዉ።»

David Donoghue Irischer UN-Botschafter
ምስል Permanent Mission of Ireland to the United Nations, New York / Department of Foreigh Affairs and Trade

ይላሉ የንስ ማርቴንስ።ቦን የሚገኘዉ ዓለም አቀፍ የፖሊሲ መድረክ የተሰኘዉ መያድ ሐላፊ ናቸዉ።ድርጅታቸዉ ከ1985 ጀምሮ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትን ሥራና አሠራር ይተነትናል።የተባበሩት መንግሥታት የልማት መርሐ-ግብር (UNDP) የበላይ ፖዉል ላድ በበኩላቸዉ ዕቅዱን ሁሉንም ያቀፈ፤በተሳሰረችዉ ዓለም የተወሳሰበዉን የሰዎች ኑሮ ለማሻሻል ያለመ ይሉታል።«በመላዉ ዓለም ከሚኖሩ ሰዎች ጋር ባደግነዉ ምክክር የነገሩን ነገር ምድነዉ አንዳቸዉ ከሌላቸዉ ተነጥለዉ በየሰንዱቁ እንደማይኖሩ ነዉ።ድሕነታቸዉ ከፀጥታቸዉ ጋር፤ በጣሙን ከተፈጥሮ ሐብታቸዉ ጋር የተቆራኘ መሆኑን ነዉ።ሥለዚሕ ያሉባቸዉን ችግሮች ለመፍታት ትንሽ ረቀቅ፤ጠለቅ፤ ወሰብሰብ ያሉ (እርምጃዎች) ያስፈልጋሉ።»

አሥራ-ሰባቱ ግቦች 169 ንዑስ ግቦች አሏቸዉ።«Targets» ብለዋቸዋል ንዑሳኑን ግቦች።የግቦቹ አፈፃፀም በየደረጃዉ እና በየጊዜዉ ይገመገማል።የአጠቃላይ ዕቅዱን የመጨረሻ ድርድር ከኬንያዊ አቻቸዉ ጋር ሆነዉ የመሩት በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአየርላንዱ አምባሳደር ዴቪድ ዶንጎሕ እንደሚሉት የዕቅዱን አፈፃፀም በከፍተኛ ደረጃ የሚገግም ጉባኤ በዓመት አንዴ ይደረጋል።

«በዓመት አንዴ፤ አባል ሐገራት ዕቅዱን ገቢራዊ ያደረጉበትን የአፈፃፀም ዘገባ የሚቀበልና የሚገመግም ከፍተኛ የፖለቲካ መድረክ የሚባል አካል ይኖራል።»

አዲሱን የልማት ዕቅድ በማርቀቁና ማዘጋጀቱ ሒደት ትልቁ ጥያቄ ለዕቅዱ ገቢራዊነት የሚያስፈልገዉን ገንዘብ ማግኘቱ ነበር።ለቅዱ ገቢራዊነት 2500 ቢሊዮን ዶላር ያስፈልጋል።አምና አዲስ አበባ ላይ በተደረገዉ ድርድር የግል ባለሐብቶችም ገንዘብ ያዋጡ የሚል ሥምምነት ላይ ተድርሷል።የቦኑ ጥናት ድርጅት ሐላፊ የንስ ማርቴንስ ግን የግል ባለሐብቶች መሳተፋቸዉን ሲበዛ ይጠራጠራሉ።

Mosambik Project Everyone / Radio Everyone
ምስል privat

በአዲስ አበባዉ ጉባኤ የተደረሰበት ሌላዉ ሥምምነት ከአዳጊ ሐገራት የሚጭበረበዉ ቀረጥን መቆጣጠር ነዉ።የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት እንደሚለዉ የበለፀጉት ሐገራት ኩባንዮችና ድርጅቶች ለድሆቹ ሐገራት መክፈል የሚገባቸዉን በዓመት አንድ መቶ ቢሊዮን ዶላር ቀረጥ አይከፍሉም።

እንደ ጎርጎሪያኑ አቆጣጠር ከጥር 2016 እስከ 2030 የሚቆየዉ ዘላቂ የልማት ግቦች ነባሩን ይትበሐል በመለወጥ የሰዉ ልጅን ኑሮ ለማሻሻል ያለመ ነዉ።ያም ሆኖ የንስ ማርተን እንደሚሉት ዕቅዱ ብቻዉን ዓለምን አይለዉጥም። ያስተሳሰብ ለዉጥ ሲታከልበት እንጂ።

ነጋሽ መሐመድ

አርያም ተክሌ