1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አዳጊ ሀገሮችና የተ መ የንግድና የልማት ድርጅት ጉባዔ

ሐሙስ፣ የካቲት 18 1996

በንግዱ መስክ ሲታይ አውሮጳዊው ዓመት 2003 ጥሩ አልነበረም። ባለፈው መስከረም በካንኩን ሜክሲኮ የተካሄደው የዓለም ንግድ ድርጅት ድርድር የከሸፈበት ሁኔታ በዓለም አቀፍ ደረጃ ነፃ ንግድን ለማስፋፋት በተጀመረው ጥረት ላይ ትልቅ እክል መደቀኑ የሚታወስ ነው። ይሁን እንጂ፡ ክሽፈቱ ያስከተለው ዓይነት ቀውስ በሚፈጠርበት ጊዜ ሁሉ፡ ከቀውሱ ለመውጣት የሚቻልበትን ዘዴ የማፈላለጉ አሠራርም ይነቃቃል። በአህፅሮት ኡንክታድ በመባል የሚታወቀው የተ መ የንግድና የል

https://p.dw.com/p/E0fw

��ት ድርጅት፡ የፊታችን ሰኔ በሳዎ ፓውሎ ብራዚል በሚያካሂደው አሥራ አንደኛው ዓቢይ ጉባዔውም ላይ የዓለም ንግድ ድርጅት ወደፊት የሚያደርጋቸውን ድርድሮች ከክሽፈት ለመጠበቅ ስለሚቻልበት ጉዳይ ይመክራል። የጀርመናውያኑ የልማት ድርጅትም ለሳዎ ፓውሎው ጉባዔ ዝግጅት እዚህ ቦን ውስጥ የሁለት ቀናት ስብሰባ አካሂዶ ነበር።

ድርጅቱ ጀርመን በኡንክታድ ዓቢይ ጉባዔ ላይ ይዛው በምትቀርበው አቋም ላይ ከመወያየቱ ሌላ፡ በተለይ፡ አዳጊዎቹን ሀገሮች ለነፃው ንግድ እንዴት ዝግጁ ማድረግ ይቻላል ለሚለው ጉዳይ ትኩረት ሰጥቶ መክሮበታል። ለካንኩን ድርድር ክሽፈት፡ ብራዚልና ሕንድ ጭምር የተጠቃለሉበትና በአንድ በኩል የኢንዱስትሪ ሀገሮች ገበያዎች ለምርቱ ክፍት እንዲሆኑለት፡ በሌላ ወገን ደግሞ የበለፀጉት መንግሥታት ለግብርናው ምርት የሚሰጡትን ድጎማ እንዲያቆሙ በጠየቀው የሀያ አንድ ሀገሮች ቡድን አኳያ በመስከረሙ ጉባዔ ላይ ምን ዓይነት መደራደሪያ ሀሳብ መቅረብ ነበረበት የተሰኘው ትያቄ በሚገባ ያልተጤነበት ድርጊት ተጠያቂ መሆኑን በጀርመን የኤኮኖሚ ሚንስቴር ውስጥ ለዓለሙ ንግድ ድርጅት ጉዳዮች ተጠሪ የሆኑት ካርል ኤርንስት ብራውነር አስታውቀዋል። የኡንክታድ ጉባዔ ታድያ በአዳጊዎቹ ሀገሮችና ለካንኩን ድርድር ክሽፈት የበኩላቸውን ድርሻ ባበረከቱት ኢንዱስትሪ መንግሥታት መካከል ያለውን የመረዳዳት ችግር ለማስወገድ የሚረዳ መድረክ ሆኖ ሊያገለግል እንደሚችል ብራውነር ተስፋቸውን ገልፀዋል። የሰኔው የሳዎ ፓውሎ ዓቢይ ጉባዔ፡ በዓለሙ ንግድ ድርጅት ድርድር አንፃር የግል ጥቅም የማስከበሩ ጥያቄ ስለማይነሣበትም ከአዳጊዎቹ ሀገሮች ጋር በግልፅ ሀሳብ መለዋወጥ እንደሚያስችልም ብራውነር አምነውበታል። እንደ ኡንክታድ ዋና ፀሐፊ ሩብንስ ሪኩፔሮ አባባል፡ ዓቢዩ ጉባዔ ቀጣዮቹ የዓለም ንግድ ድርጅት ውይይቶች ይሳኩ ዘንድ ጠቃሚ ሀሳቦች የሚቀርቡበት መድረክ ይሆናል ተብሎ ተገምቶዋል። ዓለም እስካሁን በንግዱ ድርድር ላይ ብቻ ያተኮረበት አሠራር ልክ ቢሆንም፡ በንግድ ሂደት ላይ ሁለት ገፅታዎች፡ ማለትም ገበያዎች ክፍት የሚሆኑበት ድርጊት ብቻ ሳይሆን፡ የምርት አቅርቦት መሰናክሎችም እንዳሉ ሊረሳ እንደማይገባ ሪኩፔሮ አክለው አስረድተዋል። አንድ ሀገር ምርትና አገልግሎት ወደ ውጭ የመላክ አቅም ከሌላት፡ የንግዱ ድርድርም አያስፈልጋትም ያሉት ሪኩፔሮ በዓለም ንግድ ላይ የፉክክር አቅማቸው ደካማ መሆኑን የሚያውቁት ብዙዎቹ አፍሪቃውያት ሀገሮች ለዓለሙ ገበያ የሚያቀርቡት ምርት ጥቂት በመሆኑ ገበያዎቻቸውን ክፍት ለማድረግ እንደማይፈልጉ አስታውቀዋል። ብዙዎቹ ቡናን፡ የወይራ ዘይትን፡ ወዘተ. በመሳሰሉት ጥሬ አላባዎች ላይ ብቻ ጥገኛ ናቸው፤ ይሁንና፡ እነዚህ ምርቶች የግምሩክ ችግር ስለሌለባቸው አፍሪቃውያኑ መንግሥታት ከነፃው ንግድ ምንም ትርፍ አያገኙም፤ ተጠቃሚዎች ለመሆን ከፈለጉ ጥሬ አላባ ብቻ ሳይሆን ያለቀለትንም ምርት ወደ ውጭ መላክ ይኖርባቸዋል። ወደ ውጭ በንግድ የሚልኩትን የምርት አቅርቦታቸውንም ማስፋፋት የሚፈልጉ ሀገሮች ደግሞ የመሠረተ ልማታቸውን እና የምርምሩን ዘርፍ ማሻሻል፡ እንዲሁም፡ መልካሙን አስተዳደር ገሀድ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል። ከጥሬ አላባው ጎን ያለቀለትንም ምርት ወደ ውጭ በመላኩ ተግባር የደቡብ ምሥራቅ እሥያ ሀገሮችን እንደ ጥሩ ምሳሌ ጠቅሰዋል። በዚሁ ረገድ ችግሩ ያለው አፍሪቃ ውስጥ ቢሆንም፡ ይላሉ ሪኩፔሮ፡ በአህጉሩ እንደ አርአያ ሊጠቀሱ የሚችሉ ሀገሮች መኖራቸውን አልካዱም። ለምሳሌ፡ ቦትስዋና ጥሬ አላባውን አልማዝ ብቻ ሳይሆን ያለቀለትን የአልማዝ ምርትንም ወደ ውጭ መላክ በጀመረችበት አሠራር ራስዋን እጅግ ድሆች ከሚባሉት ሀገሮች መደዳ ልታላቅቅ በቅታለች። ሌሶቶም፡ ምንም እንኳን የሥራ አጡ አሀዝዋ ወደ አርባ አምስት ከመቶ ከፍ ቢልባትምና ከሕዝብዋ መካከልም አንድ ሦስተኛው ከኤድስ አስተላላፊው ተኅዋሲ ጋር ቢኖርም፡ ከጥቂት ጊዜ በፊት ባወጣችው ሕግ አማካይነት፡ ቡዑላንን ወደ ሀገርዋ በመሳብ ሀምሳ ሺህ አዳዲስ የሥራ ቦታዎችን ለመክፈት መቻልዋን ሪኩፔሮ በመግለፅ፡ ሌሎቹ ከሰሀራ በስተደቡብ ያሉ አፍሪቃውያት ሀገሮች ችግር የበዛባቸውን የነሌሶቶን ዓይነት ርምጃ መውሰድ የማይችሉበት ምክንያት እንደማይኖር በርግጠኝነት አስረድተዋል።