1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኢትዮጵያና የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ጥሪ

ሐሙስ፣ ግንቦት 24 2009

ተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብት ጉባኤ ሰላሳ አምስተኛዉን መደበናኛ ስብሰባ በጎርጎሮሳዊዉ ዘመን አቆጣጠር ከመጭዉ ሰኔ 6 እስከ 23 ያካሂዳል። በጉባኤዉ  ለኢትዮጵያ  የሰብዓዊ መብት አያያዝ ትኩረት ሰጥቶ እንዲመረምር «ሂዉማን ራይትስ ወች»የተባለዉ ዓለም አቀፉ የሰብዓዊ  መብት ድርጅት ለዶቼ ቬለ ገልጿል።  

https://p.dw.com/p/2e0DY
Infografik / Karte Protests and violence in Ethiopia,  2016

The Coming UN HRC session and Ethiopia - MP3-Stereo


በመጭዉ ሳምንት በጀኔቫ ስዊዘር ላንድ በሚካሄደዉ በዚህ ጉባኤ  ከሰብአዊ መብት ጋር የተያያዙ በርካታ አለም አቀፋዊ  ጉዳዮች ይነሳሉ ተብሎ ይጠበቃል። በዚህ ጉባኤ ታዲያ ።«ሂዉማን ራይትስ ወች» የተባለዉን የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅትን ጨምሮ 11  ሌሎች የሰብዓዊ መብት ተሟጋች  ድርጅቶች ለኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት አያያዝ ትኩረት ሰጥቶ እንዲመረምር ከሰሞኑ አቤቱታ  አቅርበዋል።
ስለ አቤቱታው ዶቼ ቬለ ያነጋገራቸዉ የድርጅቱ የምስራቅ አፍሪካ ተመራማሪ ፊሊክስ ሆርን እንደሚሉት የደብዳቤዉ አላማ   በሀገሪቱ   ከጎርጎሮሳዊዉ ህዳር 2015 ጀምሮ በተካሄደዉ ተቃዉሞ ሳቢያ ተፈጽሟል ያሉትን  የሰብዓዊ መብት ጥሰት የተባበሩት መንግስታት የሰብዓዊ  መብት ጉባኤ በገለልተኛ ወገን እንዲጣራ ግፊት እንዲያደርግ   ለመጠየቅ ነው ።
1 «የደብዳቤዉ አላማ የተባበሩት መንግስታት የሰብዓዊ መብት  ጉባኤ፤  በቀጣይ በሚያካሄደዉ  ስብሰባ ላይ በኢትዮጵያ የተፈጸመዉን የሰብአዊ መብት ጥሰት በገለልተኛ ወገን እንዲጣራና የተባበሩት መንግስታት ልዩ ራፓርተር ወደ ሀገሪቱ እንዲገባ  መንግስት ፈቃደኛ ኢንዲሆን በማደፋፈርና በመገፋፋት መግለጫ  እንዲያወጣ ነዉ።»
ኢትዮጵያ የየዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብ ጉልህ አባል ለመሆን የምትፈልግ ሀገር ሆና እያለ  ከጎርጎሮሳዊዉ 2007 ጀምሮ ምንም አይነት የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሊዩ ራፓርተር ወደ ሀገሪቱ እንዳይገባ መከልከሉ ተገቢ አይደለም ሲሉ ተችተዋል። 
በኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ሁኔታ በጉባኤዉም ይሁን በዓለም አቀፉ ማህበረሰብ  ዘንድ በተገቢዉ ሁኔታ ትኩረት ሳይሰጠዉ ችላ ተብሎ መቆየቱን ፊሊክስ አስታዉሰዉ መጭዉ የተባበሩት መንግስታት የሰብዓዊ መብት ጉባኤ ስብሰባ ለአመታት የሰፈነዉን ዝምታና ጉዳዩን ያለማዉገዝ  ሁኔታ  የሚቀይር ይሆናል የሚል ተስፋ እንዳላቸዉ ተመራማሪዉ ገልጸዋል።
በሀገሪቱ  ተከስቶ በነበረዉ የተቃዉሞ አመጽ ሳቢያ በጸጥታ ሀይሎች ተፈጽሟል ያሉትን   እስር ግድያና  እና ሌሎች የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች እንዳሳሰባቸዉ የገለጹት ተመራማሪዉ አሁንም ድረስ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የቀጠለ በመሆኑ ከሀገሪቱ መንግስት ጋር በኢኮኖሚ እድገት ፣በሰላም ማስከበርና በፍልሰት ዙሪያ በአጋርነት የሚሰሩ ዓለም ዓቀፍ ድርጅቶች የሰብዓዊ መብት ጉዳይንም  ትኩረት ሰጥተዉ ሊሰሩበት ይገባል ሲሉ ያሳስባሉ።
 «  እኔ እንደማስበዉ በእነዚህ የሽርክና ስራወች የተነሳ ስለ ኢትዮጵያ ጮክ ብሎ ለመናገር ለነዚህ ዓለም አቀፍ አጋሮች  አስቸጋሪ ሊሆን ይችላል።ነገር ግን እነዚህ  ዓለም አቀፍ አጋሮች የተረጋጋች ኢትዮጵያ ታስፈልጋቸዋለች።ኢትዮጵያ ካልተረጋጋች የኢኮኖሚ እድገቱን ማየት አይቻልም።ወደ አዉሮፓ የሚደረገዉን ፍልሰትም መግታት አይቻልም።ስለዚህ  ኢትዮጵያን የረዥም ጊዜ አጋር ለማድረግ የሰብዓዊ መብት፤ መፍትሄ የሚያሻዉ ጉዳይ ስለመሆኑ በእነዚህ የአለም አቀፍ አጋሮች ዘንድ ግንዛቤ እንደተያዘ ተስፋ አደርጋለሁ»
 የሀገሪቱ መንግስትም ቢሆን  የተቃዉሞዉ ምንጭ  የኢኮኖሚ ችግር ነዉ ብሎ ከሚደመድም ህዝቡን ሊያዳምጥና የፓለቲካ ምህዳሩን ሊያሰፋ ይገባል ሲሉ   አክለዉ ያብራራሉ።
«ለተቃዉሞ የወጡ ሰዎችን እንዲናገሩ ፈቅደህ ብታነጋግር   ስለ ሰብዓዊ መብት  ፣ከእድገቱ ስለተገኘዉ አድሏዊ የጥሪትና የሀብት ክፍፍል  ያላቸዉን ቅሬታ ትሰማለህ። ነገር ግን የኢትዮጵያ መንግስት  ጥያቄወቹን ሁሉ በአንድ ላይ በመጠቅለል የኢኮኖሚ ጥያቄወች ናቸዉ በሚል የስራ ፈጠራ ላይ አተኩሯል።ነገር ግን የኢትዮጵያን ችግር  በዘላቂነት የሚፈታ አይደለም።ጉዳዩ የስራ ፈጠራ ችግር ብቻ አይደለም።በኦሮሚያና በአማራ ጎዳናወች ላይ ለተቃዉሞ ወጥተዉ የነበሩ ሰዎች ቅሬታ ይህ አልነበረም።ስለዚህ መንግስት የፓለቲካ ምህዳሩን ሊያሰፋ ይገባዋል።»
የተለያዩ  ሀገሮች የሰብአዊ መብት ጉዳዮች  በስብሰባዉ እንደሚነሱ  በጉባኤዉ ድህረ ገጽ  አስቀድሞ መርሃ ግብሩ ይፋ ሆኗል ይሁን እንጅ ከኢትዮጵያ  የሰብአዊ  መብት አያያዝ ሁኔታ ጋር የተያያዘ አጀንዳ  በግልጽ አለማካተቱ ተመልክቷል።

Human Rights Watch Logo Symbolbild
ምስል Getty Images/AFP/J. Macdougall

ፀሐይ ጫኔ

ሂሩት መለሰ