1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኢትዮጵያን የመታዉ ድርቅ፤ ምክንያቱና መፍትሔዉ

እሑድ፣ ጥቅምት 21 2008

የኢትዮጵያ መንግሥት «ድሕነትን ታሪክ እናደርጋለን» ባለበት፤ የሐገሪቱ ምጣኔ ሐብት በድርብ አሐዝ ማደጉ በሚነገርበት ባሁኑ ወቅት ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዉያን ዳግም ምፅዋት መማፀናቸዉ በርግጥ ግራ-አጋቢ አነጋጋሪም ሆኗል

https://p.dw.com/p/1GxNE
ምስል AP

ኢትዮጵያን የመታዉ ድርቅ፤ ምክንያቱና መፍትሔዉ

ጤና ይስጥልኝ እንደም አመሻችሁ ለዛሬዉ ዉይይታች ኢትዮጵያን የመታዉ ድርቅ፤ ምክንያቱና መፍትሔዉ የሚል ርዕስ ሰጥተነዋል።ድርቅ እና ረሐብ ለኢትዮጵያ አዲስ እንዳልሆነ-ሁሉ የመወያያ ርዕሥ ሥናደርገዉም ይሕ የመጀመሪያችን አይደለም።የመጨረሻ እንዲሆን እንመኛል።ግን ከምኞት ማለፉ አጠራጣሪ ነዉ።ሰሞኑን የኢትዮጵያ መንግሥት እና ዓለም አቀፍ የርዳታ ድርጅቶች በጋራም፤ በተናጥልም እንዳስታወቁት ከ8.2 በላይ ኢትዮጵያዊ ለረሐብ ፤በተለሳለሰዉ አገላለጥ ለምግብ እጠረት ተጋልጧል።

ረሐቡ ወይም ድርቁ እስካሁን ድረስ የሰዉ ሕይወት ባያጠፋም በብዙ ሺሕ የሚቆጠሩ ከብቶች ማለቃቸዉ፤ አንዳድ አካባቢ ሰዎች መፈናቀላቸዉ እየተዘገበ ነዉ።በድርቁ ክፉኛ የተገዱት፤ የአፋር፤ የሶማሌ፤ የኦሮሚያ፤ አንዳድ የአማራ፤ የትግራይና የደቡብ አካባቢዎች ናቸዉ።

ኢትዮጵያ ከ1950ዎቹ ጀምሮ በተደጋጋሚ በድርቅና ረሐብ በመመታትዋ ከሰዉ ልጅ መገኛነቷ እኩል የረሐብና የረሐብተኞች ምሳሌ ሆናለች።

የተባበሩት መንግሥታት የሠብአዊ ርዳታ ማስተባባሪያ ቢሮ (OCHA በምሕፃሩ) እንዳስታወቀዉ ዘንድሮ የተከሰተዉ ድርቅ በሐገሪቱ የሠላሳ ዓመት ታሪክ ከተከሰቱት ሁሉ የከፋ ነዉ።ኤል ኒኞ የተሰኘዉ የአየር ፀበይ ለዉጥ ያስከተለዉ ድርቅ ከዘንድሮ አልፎ በመጪዉ የጎርጎሮሪያኑ 2016 የከፋ ችግር ማስከተሉ አይቀርም-ባይ ነዉ ኦቻ።

የኢትዮጵያ መንግሥት «ድሕነትን ታሪክ እናደርጋለን» ባለበት፤ የሐገሪቱ ምጣኔ ሐብት በድርብ አሐዝ ማደጉ በሚነገርበት ባሁኑ ወቅት ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዉያን ዳግም ምፅዋት መማፀናቸዉ በርግጥ ግራ-አጋቢ አነጋጋሪም ሆኗል።እኛም ላጭር ጊዜ እንነጋገራለን።

ነጋሽ መሐመድ

እሸቴ በቀለ