1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኢትዮጵያዉያን ለምን ይሰደዳሉ?

እሑድ፣ ግንቦት 7 2008

ኢትዮጵያ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ፈጣን የኢኮኖሚ እድገት ከሚያስመዘግቡ የአፍሪቃ ሃገራት አንድዋ መሆንዋ እየተነገረ ነዉ። በሃገሪቱ ሰላምና መረጋጋት ከሰፈነ በርካታ ዓመታት ማስቆጠሩን የሃገሪቱ መንግሥትና ደጋፊዎቹ ይናገራሉ። ይሁንና የኤኮኖሚዉ እድገትም ሆነ ሰፈነ የተባለዉ ሰላም ለዜጎች በተለይም ለወጣቶች ትርጉም ያለዉ ለዉጥ ያመጣ አይመስልም።

https://p.dw.com/p/1IoAp
Äthiopien äthiopische Flüchtlinge Rückkehrer im Addis Ababa IOM Transit Center
ምስል IOM Ethiopia

ኢትዮጵያዉያን ለምን ይሰደዳሉ?

በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዉያን ወጣቶች በገፍ ወደ ተለያዩ ሃገራት እየተሰደዱ ነዉ። የተመድ እና ሌሎች የስደተኞች ጉዳይን የሚከታተሉ ዓለም አቀፍ ማኅበራት እንደሚሉት ኢትዮጵያዉያን ወጣቶች ጦርነት እንዳፈረሳት ሶማልያ ወይም ከፍተኛ ጭቆና ይፈጸምባታል ተብላ እንደምትወቀሰዉ ኤርትራ ሁሉ ኢትዮጵያም በርካታ ዜጎችዋ እየተሰደዱ ነዉ። ወደ አዉሮጳ ደቡብ አፍሪቃና ሃረብ ሃገራት ለመግባት የሚሰደዱ ኢትዮጵያዉያን በየአካባቢዉ የሚደርስባቸዉ ግፍና በደል ዘግናኝ መሆኑን በህይወት የተረፉ ስደተኞች ይናገራሉ። ሌሎች ደግሞ በየበረሃዉና በየባህሩ ሞተዉ ይቀራሉ። ለኢትዮጵያዉያን ወጣቶች በገፍ መሰደድ ምክንያቱ ምን እንደሆነ ለማወቅ በየጊዜዉ የሚደረጉ ጥናቶች እና ዉይይቶች ቢኖሩም እስካሁን ድረስ ወጥ ስምምነት ላይ የሚያደርሱ ስምምነቶች የሉም። ወጣቶቹም መሰደዳቸዉን አላቋረጡም። በቅርቡ የሜዲተራንያን ባህር ለማቋረጥ ሲሞክሩ ሰምጠዉ ከሞቱት 500 ያህል ስደተኞች መካከል ከግማሽ የሚበልጡት ኢትዮጵያዉያን ናቸዉ ተብሎ ይታመናል። በዚሁ በያዝነዉ ሳምንት የዛንብያ ፖሊስ 34 ኢትዮጵያዉያን ስደተኞች ግዛቱን አቋርጠዉ ለማለፍ ሲሞክሩ ይዞ ማሰሩ ይታወቃል። ይህ በቅርቡ የሰማነዉና በምሳሌ የምንጠቅሰዉ ብቻ ነዉ። ኢትዮጵያዉያን ለምን ይሰደዳሉ? የዛሬዉ የምንወያይበት ርዕስ ይሆናል?

አዜብ ታደሰ