1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኢትዮጵያዉያን እስረኞች እና የአምደ መረብ ዘመቻ

ሐሙስ፣ የካቲት 17 2008

የዘመቻዉ መሪ መፈክር «ዘላላም ይፈታ፤ ዮናታን ይፈታ፤ ባሕሩ ይፈታ---»-ይልና የሕሊና እስረኞች በሙሉ ይፈቱ ይላል።ዓላማዉ እስረኞቹ የተከሰሱት በሐሰት መሆኑን ለማሳወቅ፤ እንዲፈቱም ግፊት ለማድረግ ነዉ።

https://p.dw.com/p/1I2QC
ምስል Tony Karumba/AFP/Getty Images

[No title]

የኢትዮጵያ መንግሥት ሕዝባዊ ዓመፅን በማነሳሳት እና መንግስትን በመገልበጥ ሴራ ያሠረዉ ዘላለም ወርቃ አገኘሁ፤ ጓደኞቹ እና ሌሎች የ«ሕሊና እስረኞች» እንዲፈቱ በመጠየቅ የተካሔደዉ የማሕበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ዘመቻ ዛሬ ማታ ይጠናቀቃል።ከትናንት ጀምሮ ለሁለት ቀናት በፌስ ቡክ፤በትዊተር፤ ኢንስታግራም እና በመሳሰሉት በተደረገዉ ዘመቻ በርካታ ተጠቃሚዎች መሳተፋቸዉን ከአስተባባሪዎቹ አንዱ አስታዉቀዋል። የዘመቻዉ አስተባባሪ ዶክተር ተድላ ደስታ እንደሚሉት እስረኞቹ የታሠሩት በሕገ-ወጥ መንገድ ነዉ። የተመሠረተባቸዉ ክስም መሠረተ ቢስ ነዉ።

ዘላለም ወርቅ አገኘሁ እስከታሠረበት እስከ ሐምሌ 2006 ድረስ ደ-ብርሐን የተሰኘዉ አምደ-መረብ ተባባሪ አምደኛ (ብሎገር) ነበር።ታሠረ።ሁለት ጓደኞቹም።ከነገ ወዲያ ስድት መቶኛ ቀናቸዉ-እንደ ዶክተር ተድላ ደስታ ስሌት።

ተከሠሱም።በተለይ በዘላለም ላይ የተመሠረተዉ ክስ ሕገ-መንግሥቱን እና ሕገ-መንግስታዊዉ ሥርዓቱን ለማፍረስ፤ ሕዝብን ለአመፅ ለማነሳሳት በማሴር እያለ ይቀጥልና የግንቦት ሰባት የፖለቲካ ማሕበር አባል በመሆን ይላል።ግንቦት ሰባት የኢትዮጵያ መንግስት በአሸባሪነት ከፈረጃቸዉ የፖለቲካ ማሕበራት አንዱ ነዉ።ዶክተር ተድላ እንደሚሉት በዘላለምም ሆነ በሌሎቹ ላይ የተመሠረተዉ ክስ «የሐሰት» ነዉ።

Gefangener Gefängnis
ምስል Fotolia/jtanki

የዘመቻዉ መሪ መፈክር «ዘላላም ይፈታ፤ ዮናታን ይፈታ፤ ባሕሩ ይፈታ---»-ይልና የሕሊና እስረኞች በሙሉ ይፈቱ ይላል።ዓላማዉ እስረኞቹ የተከሰሱት በሐሰት መሆኑን ለማሳወቅ፤ እንዲፈቱም ግፊት ለማድረግ ነዉ።እንደገና ዶክተር ተድላ።

ዶክተር ተድላ እንደሚሉት በዘመቻዉ እስካሁን ድረስ በተለያ ሙያ፤ እድሜና አካባቢ ያሉ በርካታ ሰዎች ተካፍለዋል።ዘመቻዉ በዘላለምና ጓደኞቹ ላይ አተኮረ እንጂ ሌሎችንም አላአግባብ የታሠሩትን ሁሉ እንዲለቀቁ የሚጠይቅ ነዉ።

ዘመቻዉ፤ አስተባባሪዎቹ እንደሚሉት እስረኞቹ ፍትሕ እስኪያገኙ ድረስ ወደፊትም ይቀጥላል።

ነጋሽ መሐመድ

አዜብ ታደሠ