1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኢትዮጵያዊቷ ተመራጭ

ሐሙስ፣ መጋቢት 8 2008

ብዙዎቹ ኢትዮጵያዉን-ጀርመናዉያን ኑሮን ለማሸነፍ ከመፍጭርጨር አልፈዉ ለመብት መከበር በሚታገሉ ድርጅቶች፤ ተቋማት፤ ኮሚቴዎች ወይም ማሕበራት ዉስጥ አይሳተፉም። ምክንያቱ ብዙ ነዉ። አንዱን ግን «ይሉኝታ» ትለዋለች ቃል ኪዳን

https://p.dw.com/p/1IEm9
ምስል privat

[No title]

ለደቡብ ጀርመንዋ ከተማ ኑረንበርግ የዉጪ ዜጎች የዉሕደት ምክር ቤት አባላት በተደረገዉ ምርጫ ትዉልደ ኢትዮጵያዊቱ የከተማዋ ነዋሪ አሸነፈች። ቃልኪዳን በዛብሕ ሰላሳ አባላት ላሉት ምክር ቤት ከተወዳደሩት ሰማንያ አንድ ዕጩዎች ከምድቧ የመጀመሪያዉን ደረጃ በማግኘት ነዉ ያሸነፈችዉ። የዉጪ ሀገር ተወላጆችና የዉጪ ዝርያ ያላቸዉ የከተማይቱ ነዋሪዎች ከጀርመን ማሕበረሰብ ጋር እንዲዋሐዱ ለሚሠራዉ ምክር ቤት የሚደረገዉ ምርጫ በየስድስት ዓመቱ አንዴ የሚካሄድ ነዉ።

«ፖለቲከኛ መሆን ትፈልጊያለሽ።» ከጥያቄዎቹ አንዱ ነበር። መልሷ፤ አይ-አዎ ብጤ ነዉ፤ ከፈገግታ ጋር።ለፖለቲከኝነት በቃችም-አልበቃኝ ለምትኖርበት ከተማ የዉሕደት ምክር ቤት አባልነት ለመወዳደር ያነሳሳት ለመብት መከበር የመታገል ፍላጎትና ቁርጠኝነቷ ነዉ። ለድል ያበቃት ደግሞ አበክራ መጣርዋ፤ ብዙ መራጮችን ማሳመንና ማስተባበሯ።

ጀርመን መኖር ከጀመረች አስራ-ሰወስት ዓመቷ ነዉ። ብዙዎቹ ኢትዮጵያዉን-ጀርመናዉያን ኑሮን ለማሸነፍ ከመፍጭርጨር አልፈዉ ለመብት መከበር በሚታገሉ ድርጅቶች፤ ተቋማት፤ ኮሚቴዎች ወይም ማሕበራት ዉስጥ አይሳተፉም። ምክንያቱ ብዙ ነዉ። አንዱን ግን «ይሉኝታ» ትለዋለች ቃል ኪዳን። ግን አይጠቅምም።

ምክር ቤቱ ኑረንበርግ የሚኖሩ የዉጪ ዝርያ ያላቸዉ ሰዎች የጀርመንን ባሕል፤ ቋንቋ፤ ሕግ እና አስተሳሰብ እንዲያዉቁ ይጥራል። በዉጪ ዜጎች ላይ በደል፤ በተለይ የዘረኝነት ጥቃትና አድሎ ከተፈፀመ ተበዳይ ፍትሕ እንዲያገኝ የሚከታተል ክፍልም አለ-

ያም ሆኖ ምክር ቤቱ ቋሚ የመሰብሰቢያ፤ የሥራ-ቀንና ሰዓት የለዉም። አባላቱም ከባለጉዳዮች ጋር የሚገናኙና የሚነጋገሩበት የተወሰነ ጊዜ የላቸዉም።አመራረጡም ወሰብሰብ ያለ ነዉ። አራት ቡድን አለ። -በሁለተኛዉ የዓለም ጦርነት ወቅት ከጀርመን ተሰድደዉ በቅርቡ የተመለሱ ጀርመንዉያን ወይም ዝርያቸዉ ቡድን አንድ። የአዉሮጳ ሕብረት አባል ሃገራት ተወላጆች-ቡድን ሁለት። የተቀሩት አዉሮጳዉያን-ቡድን ሰወስት እና የተቀረዉ ዓለም ተወላጆች-ቡድን አራት።

ነጋሽ መሐመድ

ሸዋዬ ለገሠ