1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኢትዮጵያ በአመፅ ማግሥት

እሑድ፣ ጥር 1 2008

ተቃዉሞ-ግጭቱ ቆመም-ተዳፈነ እስካሁን በነበረዉ ግጭት ከ100 በላይ ሰዎች ተገድለዋል። የተገደሉት ሰዎች ቁጥር የታሠሩና ብዛት፤ የጠፋዉ ሐብትና ንብረት መጠን ብዙ እንዳከራከረ ነዉ። መንግሥት ግጭቱ በተቀሰቀሰ ሰሞን አምስት ሰዎች መገደላቸዉን ከማሳወቁ ባለፍ በሰዉ ሕይወት፤ አካልና ንብረት ላይ ሥለደረሰዉ ጥፋት እስካሁን ይፋ ያደረገዉ ነገር የለም

https://p.dw.com/p/1HaWJ
ምስል DW/N. Adugna

ኢትዮጵያ በአመፅ ማግሥት

የኢትዮጵያ መንግሥት «የአዲስ አበባ የተቀናጀ ማስተር ፕላን» ያለዉን ዕቅድ በመቃወም ካለፈዉ ሕዳር አጋማሽ ጀምሮ በተለያዩ የኦሮሚያ ከተሞች፤ ዩኒቪርስቲና ትምሕርት ቤቶች ለአንድ ወር ያክል ሲደረግ የነበረዉ የአደባባይ ሠልፍ፤ አመፅና ግጭት ዛሬም እንደ መሰንበቻዉ የኢትዮጵያ አብይ ርዕስ እንደሆነ ነዉ።

የኢትዮጵያ የፌደራልና የኦሮሚያ መንግሥታት ባለሥልጣናት፤ ፀረ-ልማት፤ ፀረ-ሠላም እና ድብቅ ዓላማ ባላቸዉ ወገኖች የተቀሰቀሰ እያሉ ያወገዙትን ተቃዉሞ ሙሉ በሙሉ መቆጣጠራቸዉን እያስታወቁ ነዉ። በባለሥልጣኑ መግለጫ መሠረት ድብቅ ዓላማ አላቸዉ በሚሏቸዉ ወገኖች ተታትሎ ለተቃዉሞ አደባባይ የወጣዉ ሕዝብ ከአካባቢዉ ባለሥልጣናት ጋር እየተወያየ ሥለዕቅዱ የሚያደርግለትን ገለፃና ማብራሪያ እየተቀበለ ነዉ።

ተቃዋሚ ፖለቲከኞች፤ የመብት ተሟጋቾችና ታዛቢዎች ግን ተቃራኒዉን ነዉ የሚሉት። እነዚሕ ወገኖች እንደሚሉት የአደባባይ ሠልፍና ተቃዉሞዉ ተዳፈነ እንጂ መንግሥት እንደሚለዉ ሙሉ በሙሉ አልጠፋም። የመዳፈን ወይም የመርገቡ ሠበብም የመንግሥት ፀጥታ ሐይሎች በወሰዱት «መጠን ያለፈ» የሐይል እርምጃ እንጂ ሕዝቡ የመንግሥትን ዓላማ ተቀብሎ ወይም አምኖበት አይደለም ባዮች ናቸዉ።

ዘገባዎች እንደሚጠቁሙት ተቃዉሞዉ አሁንም በአንዳድ አካባቢዎች በተለይም በከፍተኛ የትምሕርት ተቋማት ዉስጥ ብልጭ ድርግም እያለ ነዉ።ተቃዉሞ-ግጭቱ ቆመም-ተዳፈነ እስካሁን በነበረዉ ግጭት ከ100 በላይ ሰዎች ተገድለዋል።የተገደሉት ሰዎች ቁጥር የታሠሩና የሚታሠሩት ብዛት፤ የጠፋዉ ሐብትና ንብረት መጠን ብዙ እንዳከራከረ ነዉ። መንግሥት ግጭቱ በተቀሰቀሰ ሰሞን አምስት ሰዎች መገደላቸዉን ከማሳወቁ ባለፍ በሰዉ ሕይወት፤ አካልና ንብረት ላይ ሥለደረሰዉ ጥፋት እስካሁን ይፋ ያደረገዉ ነገር የለም። ተቃዋሚ ፖለቲከኞች እና የመብት አቀንቃኞች በመቶ የሚቆጠሩ ሰዎች መገደላቸዉን፤ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ምክትል ሊቀመንበር በቀለ ገርባን ጨምሮ ወደ አራት ሺሕ ያሕል ሰዎች መታሠራቸዉን ይዘግባሉ።

የጠፋዉ ንብረት አይታወቅም። ዉጪ የሚኖሩ ኢትዮጵያዉን ገዳዮች ለፍርድ እንዲቀርቡ፤ የታሠሩት እንዲፈቱ፤ የሕዝቡ ጥያቄ ሕጋዊ መልስ እንዲያገኝ፤ ምዕራባዉያን መንግሥታት ደግሞ በኢትዮጵያ መንግሥት ላይ ጫና እንዲያደርጉ በአደባባይ ሠልፍ፤ በደብዳቤና በመግለጫ መጠቃቸዉን እንደቀጠሉ ነዉ። ተቃዉሞ-ግጭቱ የደረሰበት ደረጃ፤ያሳደረዉ ሥጋትና እንድምታዉ የዛሬ ዉይይታችን ትኩረት ነዉ። ሰ ዎስት እንግዶች አሉን።

ነጋሽ መሐመድ

ሸዋዬ ለገሠ