እስራኤል ስደተኞችን አስገድዳ መመለሷ
ሰኞ፣ ጥቅምት 19 2005ከሰሞኑ፣ ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ ስደተኞች፣ መመለስ ግድ እንደሆነባቸው የሰብዓዊ መብት ተሟጋቹ ድርጅት ሂውማን ራይትስ ዎች እና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች አስታውቀዋል። እስራኤል ስደተኞች በቀላሉ ወደሀገሯ እንዳይገቡ አጥር ሰርታለች። ይሁንና ስደተኞች ይህንን አጥር አልፈው ለመግባት ይሞክራሉ። ሰሞኑንም ቁጥራቸው በዛ ያለ ስደተኞች በተለይም ኤርትራውያን የእስራኤልን ድንበር ሊሻገሩ ሲሞክሩ ተይዘው ወደ ግብፅ እንዲመለሱ መደረጉ ተዘግቧል።
ስለነዚህ ተመላሽ ስደተኞች እና በእስራኤል ስለሚገኙ ስደተኞች ጊዜያዊ ሁኔታ፦ በዚያችው ሀገር፣ አፍሪቃውያን ስደተኞችን የሚረዳውና መብታቸውን ለማስከበር የሚንቀሳቀሰው ማዕከል ፤ በምህፃሩ ADRC ዋና ስራ አስኪያጅ፤ አቶ ዮሐንስ ባዩ ማብራሪያ ሰተውናል።
በጠቅላላው 60000 የሚጠጉ ስደተኞች እስራኤል ውስጥ እንደሚገኙ ይነገራል። እስራኤል ህገ ወጥ የምትላቸውን ስደተኞችን ሰብስባ የምታስቀምጥበት ቦታ እንደምታመቻች ከዚህ ቀደም አስታውቃ ነበር። ይህም እስር ቤት በግንባታ ላይ ነው ይላሉ፤ አቶ ዮሀንስ።
በእስር ቤት ያለው ሁኔታ አስቸጋሪ እንደሆነ በተደጋጋሚ ተሰምቷል። አቶ ዮሀንስ እንደነገሩንም ከሆነ እንደ መስራቤታቸው ያሉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾችም ይሁኑ ጠበቆች መግባት አይፈቀድላቸውም። እንደ የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽነር -በምህፃሩ UNHCR ዘገባ 80 ከመቶ የሚሆኑ የኤርትራ ስደተኞች ከለላ በሚጠይቁበት ሀገር እውቅና ያገኛሉ። በእስራኤል ግን ሁኔታው የተለየ ነው።
ምንም እንኳን በቅርቡ በእስራኤል አዲስ ምርጫ የሚካሄድ ቢሆንም መንግስት አላማውን እንደማይቀይር አቶ ዮሀንስ እርግጠኛ ናቸው። ስለሆነም በዋና ስራ አስኪያጅነት የሚያገለግሉበት ADRC ለጊዜው ያለው አማራጭ በፍርድ ቤት ለስደተኞቹ ሙግቱን መቀጠል እና ለእናት እና ልጆች መጠለያ ማቅረብ ይሆናል።
ልደት አበበ
ሒሩት መለሰ