1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

Merga Yonas Bula
ማክሰኞ፣ መጋቢት 19 2009

የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት «የግል ቤት ለሌላቸው የክልሉ ተወላጆችና ለኦሮሚያ ዳያስፖራዎች» የመኖርያ ቦታ «በነፃ» ለመስጠት ዝግጅት እያደረገ እንደሚገኝ የአገር ዉስጥ ዘገባዎች ያመለክታሉ።

https://p.dw.com/p/2a9Qi
Äthiopien, Adama
ምስል DW/M. Yonas Bula

mmt Oromia to Offer Housing Plot - MP3-Stereo

እንደዘገባዎቹ የክልሉ መንግሥት ከዚህ ዉሳኔ ላይ የደረሰዉ ነዋሪዎች ላልተፈለገ የቤት ክራይ ወጭ እንዳይጋለጡ እና የመሬት ብዝበዛን ለመቀነስ፣ እንዲሁም ነዋሪዎቹ በከተማ በሚደረገዉ የንግድም ሆነ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ዉስጥ ተሰትፎ እንዲኖራቸዉ ለማድረግ ነዉ።

ይህ እቅድ ተግባራዊ እንዲሆን ከስምንት ወር በፊት መመርያ እንደወጣለት ነዉ የኦሮሚያ የከተማ ቤቶች ልማት ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፍ አቶ ሽመልስ አብዲሳ የሚናገሩት። በዚህ እቅድ ዉስጥ መሳተፍ የሚፈለጉ ግለሰቦች በአካባቢያቸዉ «ለሁለትና ከዚያ ዓመት በላይ የኖሩ»፣ እንዲሁም መንግሥት ብድር ቢያመቻችላቸዉ «ለቤት መሥሪያዉ ገንዘብ መቆጠብ የሚችሉ» እንዲሁም እንዲደራጁ የሚለዉ የመመርያዉ አካል መሆኑን ዘገባዎች ጠቁመዋል። የዚህ እቅድ አላማ «የቤት እጥረትን ለመቅረፍ እንደሆነና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትንም ለማረጋገጥም ነዉ» የምሉት አቶ ሽመልስ የሚወስዱት መሬት በትክክል ሥራ ላይ መዋሉን ስለሚከታተለዉ ርምጃ አክለዉ ተናግረዋል።

በኦሮሚያ ክልል የሆለታ ከተማ ነዋሪ የሆኑ ግን ስማቸዉ እንዳይጠቀስ የፈለጉት ግለሰብ፣ በአካባብያቸዉ እቅዱ ከተጀመረ አራት ወራት ማስቆጠሩንና በእቅዱም እንደተሳተፉ ያስረዳሉ። ከመንግሥት የተላለፈዉ መመሪያም ፎቅ፣ ቪላ፣ አፓርትመንትና የአገር ዉስጥ ግብዓቶችን ተጠቅሞ በአነስተኛ ወጭ መኖርያ ቤት መሥራት የሚፈልግ፤ መጀመርርያ 12 ሰዉ ሆኖ በያዘዉ ቡድን እንዲደራጅ መባሉንም ይጠቅሳሉ።

መንግሥት 40 ሺህ ቅድሚያ ክፍያ ብሎ መስፈርት ማስቀመጡ አቅም የሌላቸዉ ግለሰቦች የእቅዱ አካል እንዳይሆኑ ያደርጋቸዋል በሚል የሚሰጉ አሉ።

ከጥቂት ሳምንታት ወዲህ የኦሮሚያ ክልል ለነዋሪዎች ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍል እንዲኖር ያለመ «የኢኮኖሚ አብዮት» ያለዉን እቅድ ማስታወቁ ተሰምቷል። የክልሉ መንግሥት ነዋሪዎች በመጓጓዣ፣ በማዓድንና በግንባት ዘርፎች እንዲሳተፉ ርምጃ መዉሰድ መጀመሩም ተገልጿል። እነዚህን የመንግሥት እቅዶች በጥርጣሬ የሚመለከቱ ወገኖች በክልሉ የነበረዉን የፖለትካ ዉጥረት ከማርገብ በዘለለ ብዙ ጥቅም እንደማይታያቸው አስተያየታቸዉን ይሰነዝራሉ። የሆለታ ነዋሪዉም መንግሥት ነፃ የመኖርያ ቤት መስጠት መሞከሩ «ቀና» ቢመስልም «ሚዛን የሚደፋዉ» የማኅበረሰቡን ተቃዉሞ «ለማርገብ» ያቀፈዉ ነዉ ይላሉ።

መርጋ ዮናስ

ሽዋዬ ለገሠ