ኬንያ፣ የምርጫ ዝግጅትና ያለፈዉ ምርጫ ቅሪት
ዓርብ፣ የካቲት 22 2005
የኬንያ ሕዝብ በመጪዉ ሰኞ የወደፊት ፕሬዝዳንቱን፥ የምክር ቤት እንደራሴዎቹንና ያካባቢ አስተዳዳሪዎቹን ይመርጣል።ኬንያዊዉ ባሁኑ ምርጫ ድምፁን የሚሰጠዉ ከአምስት ዓመት በፊት የተደረገዉ ምርጫ አወዛጋቢ ዉጤት የቀሰቀሰዉ ደም አፋሳሽ ግጭትን እያሰላሰለ ነዉ።የጎሳ መልክና ባሕሪ በተላበሰዉ ግጭት ከአንድ ሺሕ አንድ መቶ በላይ ሰዎች ተገድለዋል።ከ650 ሺሕ በላይ ቤት ንብረታቸዉ ወድሞባቸዋል።ሪፍት ቫሊ የተሰኘዉን የኬንያን ግዛት የጎበኘቺዉ የዶች ቬለዋ ማያ ብራዉን እንደዘገበችዉ የያኔዉ ግጭት መዘዝ እስካሁንም የብዙ ኬንያዎችን ኑሮ እንዳወከ ነዉ።ዝር ዝሩን አጠናቅሬዋለሁ።
«ሱቄ እዚሕ ነበር።» አሉ ፔተር ንጀቺያ የዛገዉን የብረት መዝጊያ እየቆረቆሩ።«ተመልከቺ ዕቃዎቹ በሙሉ እዚሕ ነበሩ።» ቀጠሉ ሰዉዬዉ «አንድም ነገር ማምዉጣት አልቻልንም።» ያኔ---በመደብሩ መስኮት የተወረወረዉ ችቦ ሁሉንም አጋየዉ።
የቤቱ ምሰሶዎች እንደቆሙ ናቸዉ።የሚደግፉት ጣራ ግን የለም።ወለሉም አረም በቅሎበታል።ከጠፉ ቤት ጓሮ ሌላ የጋየ ቤት መሠል ነገር አለ።«እዚሕ ሰባ ፍየሎችና ሁለት መቶ ዶሮዎች ነበሩን» ቀጠሉ ንጄቺና « ሁሉም ባንድ ቀን ጠፉ» እያሉ።
የትንሺቱን የንዴፎ ከተማን አዉራ መንገድ ጠርዝ ታከዉ ቆመዉ የነበሩት የትንሿ መደብር ግራ-ቀኝ አጎራባች ቤቶች በሙሉ ነደዋል።ከናይሮቢ አንድ መቶ ሰማንያ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የምትገኘዉ ንዴፎ አንድ አዉራ መንገድ ነዉ ያላት።መንገዱ ወሰንም ነዉ።ባንደኛዉ በኩል የኩኩዩ፥ በሌለኛዉ የካሌንጂን ጎሳ አባላት ይኖራሉ።ኩኩዩ የኬንያ ትልቁ ጎሳ ነዉ።ካሊንጂን ደግሞ ከአምስት የኬንያ ትላልቅ ጎሳዎች አንዱ ነዉ።
ከአምስት ዓመት በፊት የተደረገዉ ምርጫ ዉጤት ፖለቲካዊ መሠረቱን ለቅቆ የአንዱን ጎሳ ተወላጅ ከሌላዉ ጋር ሲያጋጭ ንዴፎም በነዋሪዎችዋ ደም ትጨቀይ፥ በእሳት ትጋይ ገባች።ብዙ ሰዉ አለቀባት።አንድ ሺሕ አምስት መቶ ቤቶች ጋዩ።አሁን ኩኩዩዎቹ በሚኖሩበት መንደር በቆሎ ተስጥቶ፥ ይታል።ልጆችም አረዳ ላይ ይጫወታሉ።
የመንደሩ ምክትል ተጠሪ ግራሲ ዋንጅሩ እንደሚሉት ጠብ-ቁርቁሱ እየበረደ፥ ሠላምም እያጎነቆለ ነዉ።«ጭራሽ አንነጋገርም ነበር።አሁን እንደገና እየተጀመረ ነዉ።ብዙ ስብሰባዎች አድርገናል። ከሌለኛዉ ወገን ጋርም ሐሳብ ተለዋዉጠናል።ሁሉም ወደነበረበት እየተመለሰ ነዉ።»ፒተር ንጄቺያ ግን ተቃራኒዉን ነዉ-የሚናገሩት።
«ከማን ጋር ነዉ የምንታረቀዉ።የትና መቼ? እንድንታረቅ የሚጠይቅ ሳይኖር እንዴት ነዉ እርቅ የሚኖረዉ? እንዲሕ አይነት ነገር የታለና?»
እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር በሁለት ሰባት ማብቂያ በተደረገዉ ምርጫ ካሌኒጂንዎች ድምፃቸዉ የሰጠዉ ለያኔዉ ተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ለራይላ ኦዲንጋ ነበር።ድምፅ ከመሰጡ ጥቂት ሳምንታት በፊት በተደረገዉ ጥናት መሠረት ኦዲንጋ ከካሌኒጂን፥ ከሉዎ፥ ከኪስና ከሌሎች አነስተኛ ጎሳዎች ጋር የመሠረቱት ጥምረት ተቀናቃኛቸዉን በሰፊ ልዩ ይመሩ ነበር።ድምፅ በተሰጠ በሰወስተኛዉ ቀን በሕዋላ የታወጀዉ ዉጤት ግን የዚሕ ተቃራኒዉ ነበር።ፕሬዝዳት ምዋዪ ኪባኪ የሚመሩትና ኩኩዩዎች የሚበዙበት ገዢ ፓርቲ ማሸነፉን ያመለክታል።ዉጤቱ ያበሳጫቸዉ የካሌኒጂን እና የሌሎቹ ጎሳ ተወላጆች በኩኩዮቹን ላይ ዘመቱ።ከጥቂት ሳምንታት በሕዋላ ደግሞ ኩኩዮች ሌሎቹን ይበቀሉ ያዙ።
ጎረቤት ከጎረቤቱ ጋር ተጋደለ። አንዱ የሌላዉን ሐብት፥ ንብረት ይዘርፍ፥ያጋይ ያዘ።በግጭት ጥፋቱ ማግሥት የተመሠረተዉ የኬንያ ተጣማሪ መንግሥት ደም የተቃባዉን ሕዝብ የሚያስታርቅ የእርቀ ሠላም ኮሚሽን መስርቷል።ከወጣት የኮሚሽኑ አባላት አንዱ ማርቲን ብራዉን እንደሚለዉ ግን ተጎጂዎችን ለመርዳት ብዙም ጥረት አልተጣረም።
«በእኔ እምነት ከምርጫዉ በሕዋላ የተፈጠረዉን ግጭትና ቂም ለማብረት የተከተልነዉ መንገድ የተሳከረና ጨርሶም ቅድሚያ ያልሰጠነዉ ጉዳይ ነዉ።ሕንፃዎችንና ኢኮኖሚዉን ዳግም ለመገንባት ተሞክሯል።የሕዝቡን የልብ ሥብራትና ቁስል ግን አላዳንነዉም’።»
የምሥራቅ አፍሪቃ የሰላም፥ የልማት ተምሳሌይቱ ሐገር በነፃነት ታሪኳ አይታ ከማታዉቀዉ እልቂት በቅጡ ሳታገግም ዘንድሮ-ሰኞ ሌላ ምርጫ ታስናግዳለች።
ነጋሽ መሐመድ
አርያም ተክሌ