ዉይይት- ኢትዮጵያና የካቢኔዉ ሹም ሽር
እሑድ፣ ጥቅምት 27 2009የመንግሥት ተቃዋሚዎች የመብት ተሟጋቾች እና አንዳንድ የፖለቲካ ተንታኞች የኢትዮጵያ መንግሥት የሚወስዳቸዉ ርምጃዎች የሕዝቡን ጥያቄ ለመመለስ የሚጠቅሙ አይደሉም፤ መሰረታዊ ለውጥ እንጂ የግለሰቦች ሹም ሽር ሀገሪቱ አሁን ያለችበትን የፖለቲካ ቀውስ አይፈታም ሲሉ አዲሱን የሚኒስትሮች ሹመት አልተቀበሉትም። እነዚህ ወገኖች እንደሚሉት በተለያዩ አካባቢዎች ተቃዉሞዉን ለመግለፅ አደባባይ የወጣዉ የሕዝብ ጥያቄ፤ የዲሞክራሲ ስርዓት፤ራስን በራስ የማስተዳደር መብት፤ ፍትህ፤ እንዲሰፍን ነዉ። የኢትዮጵያ መንግሥት የሕዝቡን ጥያቄ በቀጥታ ከመመለስ ይልቅ በራሱ መንገድ የአስቸካይ ጊዜ በማወጅ በፊትም የጠበበዉን ዲሞክራሲያዊ መብት ይበልጥ አዳፍኖታል ይባላልም። አሁን የተደረገዉ የካቢኔ ሹም ሽርም ከሕዝቡ ጥያቄ ጋር ምንም ግንኙነት የለዉም ሲሉ ትችት የሚያቀርቡም ጥቂቶች አይደሉም። በዚህ ዉይይታችን የጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ የካቢኔ ሹምሽርንና፤ አዲሱ የካቢኔ ምስረታ በሃገሪቱ የተነሳዉን ፖለቲካዊና ማኅበራዊ ቀዉስ ለመፍታት ስለሚኖረዉ ጥቅምና የተቃዋሚዎችን አስተያየት ለመቃኘት እንሞክራለን። በዚህ ርዕስ ላይ እንዲወያዩልን የጋበዝናቸዉ፤ በልማት ጉዳይ የኤኮኖሚ ምሁር ዶ/ር አክሎክ ቢራራ፣ የአዲስ ስታንዳርድ መጽሔት ዋና አዘጋጅ ፀዳለ ለማ ፤ አምደኛ አብዱል ባሲጥ አብዱልሰመድና የሕግና የፖለቲካ ሳይንስ ምሁር ዶ/ር ለማ ይፍራሸዋ ናቸዉ። አራት ተወያዮች ኃሳብ የሰነዘሩበትን ሙሉዉን የውይይት ቅንብር የድምፅ ማድመጫ ማዕቀፍን በመጫን ይከታተሉ።
አዜብ ታደሰ
ልደት አበበ