1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ዉይይት፤ የሰብአዊ መብት ጥሰት በኢትዮጵያ

ነጋሽ መሐመድ
እሑድ፣ ሚያዝያ 22 2009

ኮሚሽኑ እንደሚለዉ ለተቃዉሞ ዋና ዋና ከሚባሉት ምክንያቶች ቀዳሚዎቹ ሥር የሰደደ የመልካም አስተዳደር ችግር፤ የመብት ጥሰት፤የሥራ አጦች መብዛት፤ የልማት መርሐ-ግብሮች መታጠፍ፤ኦሮሚያ በአዲስ አበባ ላይ ያለዉ ሕጋዊ ጥቅም አለመከበር፤ የወልቃይት ጠገዴ አካባቢ አስተዳደር በትግራይ ሥር መሆን ናቸዉ።

https://p.dw.com/p/2c6HP
Deutschland Demonstration in Berlin gegen Verletzungen der Menschenrechte in Äthiopien
ምስል DW/Y. H. M. Korri

የኢትዮጵያ መንግሥት የሠብአዊ መብት ኮሚሽን፤ ኢትዮጵያ ዉስጥ ከሐምሌ 2008 እስከ መስከረም 2009 በተለያዩ አካባቢዎች በተደረጉ ሕዝባዊ ተቃዉሞችና ተቃዉሞዎቹን ለመደፍለቅ በተወሰደዉ ርምጃ በሰዉ ሕይወት፤ አካልና ንብረት ላይ የደረሰዉን ጉዳት የሚዘረዝር ጥናታዊ ዘገባ ይፋ አድርጓል።

ከሚሽኑ ባለፈዉ ሚያዚያ 10 ለሐገሪቱ ምክር ቤት ባቀረበዉ ዘገባ እንዳስታወቀዉ በሦስት ወር ዉስጥ በኦሮሚያ፤ በአማራ እና በደቡብ መስተዳድር በጌድኦ ዞን በተደረጉት ተቃዉሞችና ተቃዉሞዎቹን ለማስቆም በተወሰዱት እርምጃዎች 669 ሰዎች ተገድለዋል።በመቶ የሚቆጠሩ ቆስለዋል።በሺሕ የሚቆጠሩ ተፈናቅለዋል። ከሁለት መቶ ሚሊዮን ብር የሚበልጥ ሕብትና ንብረት ወድሟል።

ኮሚሽኑ እንደሚለዉ ለተቃዉሞ ዋና ዋና ከሚባሉት ምክንያቶች ቀዳሚዎቹ ሥር የሰደደ የመልካም አስተዳደር ችግር፤ የመብት ጥሰት፤የሥራ አጦች መብዛት፤ የልማት መርሐግብሮች መታጠፍ፤ ኦሮሚያ በአዲስ አበባ ላይ ያለዉ ሕጋዊ ጥቅም አለመከበር፤ የወልቃይት ጠገዴ አካባቢ አስተዳደር በትግራይ ሥር መሆን ናቸዉ።

አመፅና ተቃዉሞዉን ለመደፍለቅ አንዳድ ቦታ የተወሰዱትን ርምጃዎች ዘገባዉ ተመጣጣኝ ሲላቸዉ፤ ሌላ ሥፍራ ደግሞ ከመጠን ያለፈ ብሏቸዋል።ከመጠን ያለፈ እርምጃ የወሰዱ የፀጥታ ኃይል ባልደረቦች እና ባለሥልጣናት ለፍርድ እንዲቀርቡ ኮሚሽኑ ጠይቋል።የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሕግና የአስተዳደር ጉዳይ ኮሚቴ በኮሚሽኑ ዘገባ ላይ ተመስርቶ ለምክር ቤቱ ያቀረበዉን የዉሳኔ ሐሳብ ምክር ቤቱ አፅድቆታል።

በፀደቀዉ ዉሳኔ መሰረት ተጠያቂ የተባሉት የመንግሥት የፀጥታ ሐይል ባልደረቦች፤ ባለሥልጣናት፤ የኦሮሞ ነፃ አዉጪ ግንባር፤ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግሬስ፤ ሰማያዊ ፓርቲንና የኦሮሞ ሚዲያ ኔትዎርክን በሕግ ይከሰሳሉ።የዘገባዉ ይዘት፤ ዉሳኔዉና ገቢራዊነቱ የዛሬ ወይይታችን ትኩረት ነዉ።ሦስት እንግዶች አሉን።

ነጋሽ መሐመድ

ማንተጋፍቶት ስለሺ