1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ዓለም እና ጥፋት ተንባዮችዋ

ሐሙስ፣ ታኅሣሥ 11 2005

ስለ ዓለም ኅልፈት የተነገረዉን ትንቢት ይዘን በፊስ ቡክ አስተያየታቸዉን እንዲያካፍሉን የጠየቅናቸዉ ታዳሚዎች አብዛኞቹ ከፈጣሪ በቀር ይህን የሚያዉቅ የለም ወግዱ በሏቸዉ ሲሉ ሃሳባቸዉን ፅፈዋል። አንዳዶች ደግሞ ብቻችንን መቅረታችን ነዉ ያሉንም አሉ።

https://p.dw.com/p/176NS
ምስል picture-alliance/dpa

የጎርጎረሳዉያኑን ቀመር የሚከተሉ በሂሳብም ሆነ በስነ-ፈለግ እንዲሁም በፒራሚድ ሥራዎቻቸዉ የሚደነቁትና ሥልጣኔን ለዓለም አበርክተዉ ያለፉት ማዕከላዊ አሜሪካ ይኖሩ የነበሩት ጥንታዊያኑ፤ የማያ ጎሳዎች የዘመን ቀመር በመጠናቀቁ ዓለም የምትጠፋበትን ቀን ተንብየዋል። በትንበያቸዉ መሰረት ይህ ቀን አርብ በ 21.12.12 ይዉላል ነዉ የተባለዉ። በምዕራቡ ዓለም የሚገኙ የተለያዩ የብዙሃን መገናኛዎች በጉዳዩ ሰምዎኑን የመዝናኛ ርዕሳቸዉ አድርገዉት ሰንብተዋል። እኛም ይህን ሃሳብ ይዘን በፊስ ቡክ ገፃችን አስተያየታቸዉን እንዲያካፍሉን የጠየቅናቸዉ የዶቸ ቬለ ታዳሚዎች አብዛኞቹ ከፈጣሪ በቀር ይህን የሚያዉቅ የለም ወግዱ በሏቸዉ ሲሉ፤ ሌሎች ተገላገልን ነበር ከማይረባዉ ዓለም ሲሉ የተለያየ ሃሳባቸዉን አካፍለዉናል።
ኅልፈተ ዓለም አለመከሰቱን የሚያሳየዉ መዝገብ እዚህ በድሪስደን ከተማ ይገኛል ይላል ሰምወኑን ይህንኑ የማያ ቀን ቀመር ተከትሎ የተነገረዉን ትንበያን አስታኮ የተፃፈዉ ዘገባ። የ4000 ዓመት እድሜን የያዘዉ የማያ ማለት ጥንታዉያኑ የማዕከላዊ አሜሪካ ነዋሪዎች፣ የቀን ቀመር ብቸኛዉ ዋንኛ ቅጅ በሚገኝዉ በጀርመን በድሪስደን ከተማ ዉስጥ ባለዉ የአንድ ዩንቨርስቲ ቤተ-መፃህፍት እና በከተማይቱ በሚገኘዉ የመፅሃፍ ዓዉደ ርዕይ ማዕከል ነዉ፤ በርግጥ ይህንን የሰዉ ልጅ የዕድገት ታሪክን የሚያሳየዉ መዝገብ እንዳይበላሽ በከርሰ ምድር ቀዝቃዛ እና ጨለማ ክፍል መስታወት ሳጥን ዉስጥ መቀመጡም ተገልጾአል። 39 ቦታ የተጣጠፈዉና 3 ሜትር ከ 50 ሳንቲ ሜትር ርዝመት ያለዉ በስስ ቆዳ ላይ የተጻፈዉና የማያን ባህል ታሪክ ስለሚያሳየዉ የቀን ቀመር ጀርመናዊዉ የቤተ መጻሕፉ አስተዳዳሪ ቶማስ ቡርገር ይህ የቀን ቀመር ይላሉ።
«የቀን ቀመሩ ገበሪዎች ለእርሻ ግዜያቸዉ እንዲሆናቸዉ የሰሩት የቀናት መከታተያ የነበረና ቆየት ብሎ የማያ ጎሳ እዉቀት እና ችሎታ የሚንፀባረቅበት ነገር ሆኖ ተገኘ»
የማያ የቀን ቀመር በጎርጎረሳዉያኑ 21.12.12 በመጠናቀቁ ነዉ፤ የዓለም ፋፃሜ ይሆናል፤ የተባለዉ። በዚህ በምዕራቡ ዓለም ያሉ የተለያዩ ብዙሃን መገናኛዎች በጉዳዩ ባለሞያዎችን በማነጋገር እንዲሁም በቀልድ የተለያዩ ዘገባዎችን በማቅረብ የመወያያ ርዕሳቸዉ አድርገዉ ሰንብተዋል። ታዋቂዉ የዩናይትድ ስቴትስ የአየር እና የህዋዉ ምርምር መስርያ ቤት {NASA}በበኩሉ ጉዳዩ በሳይንስ ያልተረጋገጠ እና በኢንተርኔት የማህበረሰብ መገናኛ ስለ ዓለማችን የወጣ የተጋነነ ዘገባ ሲል አጣጥሎታል። እንደ NASA ዘገባ በርካቶች በመስርያ ቤቱ እየደወሉ ስለ ዓለም ኅልፈት ማብራርያን በመፈለጋቸዉ፤ መስርያ ቤቱ ኅልፈተ ዓለም ይከሰታል ከተባለበት ቀን ማግስት ጀምሮ ያለዉን፤ የዓለማችንን ነባራዊ ሁኔታ ከወዲሁ በዩ-ቲዩብ አጠር ያለ በምስል የተቀናበር ዘገባዉን ማሰራጨቱን በመገናኛ ብዙሃኖች ይፋ አድርጎአል።

Maya Kalender Weltuntergang Dezember 2012 Guatemala
ምስል DW/A. Boueke
Codex Dresdensis
ምስል SLUB

አንድን ነገር ከማህበራዊ ክስተት ጋር በማያያዝ እንዲህ ሲሆን እንዲህ ይሆናል ወደፊት ሊመጣ የሚችልን መጥፎ እድል ወይም ጥሩ ነገርን የመተንበያ ልማድ ምልኪ ይባላል። እንዲህ አይነቱ ሳይንሳዊ ጭብጥን ያልተመረኮዘ ትንቢት በ21ኛዉ ክፈለ ዘመን ዛሪ በታዳጊዎቹ አገራት ብቻ ሳይሆን በሳይንስ ቴክኖሎጂም የረቀቁት አገራት ይታያል። ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ገልጾልናል።
ማያ ጎሳዎች አሁንም ቢሆን በማዕከላዊ አሜሪካ በተለይ በጓቲማላ በብዛት እንደሚገኙ ተገልጾአል። የእነዚህ ህዝቦች ባህል በአኗኗር እና ጥንታዊ ግኝቶችን ለማየት ከተለያዩ የዓለም ክፍሎች የሚመመጣዉ ህዝብ እንዲሁ በርካታ እንደሆነ ነዉ የሚነገረዉ። ማያዎች የራሳቸዉ የሆነ ቋንቋ ባህል ያላቸዉና ከሽ አመታት በፊት ቅም ቅም አያቶቻቸዉ ይሰሩበት እንደነበረዉ አይነት የግብርና ዘዴ ዛሪም በአፅናፋዊዉ ትስስር በግሎባላይዜሽኑ የኤሌክትሮኒክስ ዘመን ጋር ትግል ገጥመዉ ይታያል። የቀድሞዎቹ ማያ ጎሳዎች ከዛሪ 1300 ዓመት በፊት በሃያ አንድ 12 ኛ ወር 2012 የቀን ቀመሩ እንደሚያልቅ የመዘገቡበት ዓለት ድንጋይ በማዕከላዊ አሜሪካ በኮስታሪካ ዉስጥ በሚገኝ ገጠር ዉስጥ ነበር የተገኘዉ። የዓለም ኅልፈት ትንበያ ምዕራቡን ዓለም አብዛኞችን ሲያነጋግር፤ የጓቲማላ የሚገኙትን ማያዎችን ግን ያስጨነቀ አይመስልም፤ ማሪያ ማቴዎ የተባለች አንዲት የማያ ጎሳ ገበሪ ስለ ትንቢቱ
«በእርግጥ የሆነ ለዉጥ እንደሚከሰት እናምናለን፤ ግን መቼ ሊሆን እንደሚችል ግን እርግጠኛ ቀኑን አናዉቅም። እያንዳንዱ ሰዉ ለዚህ ለዉጥ አንድ የሆነ ነገር አስተዋፅኦ ሊያደርግ ይችላል። ስለዚህም የሰዉ ዘር በሙሉ ተፈጥሮን እና አካባቢን መጠበቅ አለበት። የማያ ጎሳዎች በተለይ ደግሞ ሴቶች በደጋገፍና በጋራ፤ ሃይላቸዉን አሰባስበዉ ለአለማችን መቆም፤ እና መታገል ይኖርባቸዋል»
የማያ ትንቢት አላችሁ መቼ ኖርን እና ነዉ የምንጠፋዉ፤ ብሎ በፊስ ቡክ አድራሻችን መልክት ያስቀመጡ አድማጫችንን ሃሳብን እጋራለሁ! አንድ ህብረተሰብ የአስተሳሰብ አድማሱ እየሰፋ በሄደ ቁጥር የሚያስቀራቸዉ እየተዋቸዉ የሚሄዱ ምልኪዎች በርካቶች መሆናቸዉ ግን እሙን ነዉ። በድሪስደን ዮንቨርስቲ የቤተ መጻሕፉ አስተዳዳሪ ቶማስ ቡርገር በአጠቃላይ ይላሉ ስለ ማያ የቀን ቀመር መዝገብ ሲገልጹ «በአጠቃላይ ከዚህ መዝገብ የምንረዳዉ ፤ ለተፈጥሮ ክብርና ጥንቃቄ መዉሰድ እንዳለብን ነዉ። በነዚህ አስርተ ዓመታት ያሳለፍነዉን የባህር ነዉጥ ፣ ጎርፍ የመሳሰሉ በርካታ የተፈጥሮ አደጋዎች በሙሉ፣ በጥንት ግዜ የማያ ጎሳዎችም እንዲሁ ችግሩን ቀምሰዋል»
ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ይህ አይነት ትንቢት የሚሰማዉ በዙርያችን ከሚከሰተዉ ነገር ጋር በተያያዘ ነዉ ሲል ገልጾልናል።

Flash-Galerie 11.11 2011 Symbolbild Weltuntergang
ምስል picture-alliance/landov

አዉሮጳ ሜክሲኮን በተቆጣጠረችበት ዘመን ከክርስቶስ መወለድ 900 ዓመት በኋላ የነበሩ የማያ ባህልን ገላጭ የሆኑ እጅግ ብዙ ታሪክ አዘል ጽሁፍዎች መቃጠላቸዉ ተነግሮዓል። ይኸዉም በዝያን ዘመን አዉሮጳዉያኑ የጣኦት ዓምላክን ባለማወቃቸዉ አዉሮጳዉያኑን ለማስደሰት ሲሉ ነበር ከ5000 ሽህ በላይ መፃህፍትን ያቃጠሉት። «ኢንዶስ የተሰኙት የማያ ጎሳዎች፤ ምንም እንኳ ድሃ ሆነዉ ርዳታ ቢሹም፤ የሚለዩበትን ላባ የተሰካካበትን ባህላዊዉን ባርኔጣቸዉን አጥልቀዉ ሲታዩ፤ አንዳንዴ የደላቸዉ መስለዉ በፍቅር ይገለጻሉ። በላቲን አሜሪካን ማያ ጎሳዎች ገበያ መድረክም፤ በዓለማችን በሚታየዉ በአጽናፋዊዉ ትስስር ምክንያት፤ በሸቀጥ አቅራቢ ቡድኖች እጅ ወድቋዋል። እንደ ሰልክ፤ ላፕቶት(ተንቀሳቃሽ ኮንፒዉተር)ያሉ ነገሮችን ይሸጡላቸዋል። በሌላ በኩል በአዉሮጳ ስለ ላቲን አሜሪካ መታሰቡ አብቅቶለታል። ምንም እንኳ ለማያ ጎሳዎች ባህል መጥፋት አዉሮጳ ተጠያቂ ቢሆኑም። » እዚህ በድሪስደን ከተማ የሚገኘዉ ብቸኛዉ የማያ ዝጅግ ጥንታዊ የቀን ቀመር በድሪስደኑ የመፅሃፍ ቤት ዉስጥ ሊገባ የቻለዉ በአጋጣሚ ነበር። በጎ,አ 1739 ዓ,ም በድሪስደን ያለ አንድ የቤተ-መንግስት አገልጋይ ለገበያ ወደ ቬና ሄዶ ሳለ ገበያ ቦታ ስላገኘዉ ብቻ ነበር ገዝቶ አምጥቶ በዝያን ዘመንም በነበረዉ በድሪስደኑ ቤተ መፅሃፍት ዉስጥ ያስቀመጠዉ። ከዝያም ይህ የቀን ቀመር በመፅሃፍ ቤቱ 100 ዓመት ከተቀመጠ በኋላ ነበር የማያ ጎሳዎች የቀን ቀመር መሆኑ የታወቀዉ እና ይህ ህልፈተ ዓለም ይደርሳል የተባለበት ቀን በመጥገቡ የተገኘዉ። በዓለማችን በተለያዩ አህጉሮች የሚኖረዉ ህዝብ መካከል የተለያዩ እምነቶች አሉ። የሰዉ ልጅ ይህን አጉል እምነት የሚከተለዉ ደግሞ ተፈጥሮ የፍርሃት ተገዥ ስላደረገዉ ይሆናል የሚሉ ጥቂቶጥ አይደሉም።

Guatelala Quirigua Archäologische Fundstätte
ምስል JOHAN ORDONEZ/AFP/Getty Images

ባለንበት 21ኛዉ ክፍለ ዘመን ሀገረሰባዊ ልምዶች፤ ትንቢቶች በኤኮኖሚ እንዲሁም በማህበረሰብ እድገት ላይ ምንም ዓይነት መሰናክል መፍጠር እንደሌለባቸዉ እሙን ነዉ በምዕራቡ ዓለም፤ የሚሰሙ ትንቢቶች ማህበረሰቡ በጠረቤዛ ዙርያ ተቀምጦ ለምን ትንቢቱ ከየት መጣ መነሻዉ ምንድን ነዉ ሲል ተወያይቶ፤ ነገሩን በቀልድ ወስዶ፣ በቀልድ ዉስጥ ግን ትንሽም ቢሆን እዉነት አይታጣም ብሎ በማሰብ ጥንቃቄ ሲያደር ይታያል። ሙሉዉን ቅንብር ያድምጡ!

አዜብ ታደሰ

ተክሌ የኋላ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ