የሁለቱ ሱዳኖች ሥምምነትና ገቢራዊነቱ
ሐሙስ፣ መጋቢት 26 2005
04 04 13
የሠሜንና የደቡብ ሱዳን ባለሥልጣናት ባለፈዉ ወር ማብቂያ በተፈራረሙት ዉል መሠረት በአዋሳኝ ድንበሮቻቸዉ ላይ የሠፈሩ ወታደሮቻቸዉን ዛሬ ማንሳት ይጀምራሉ።ሁለቱ መንግሥታት ካለፈዉ ዓመት ጥር ጀምሮ ደቡብ ሱዳን አቋርጣዉ የነበረዉን የነዳጅ ዘይት ምርትና ሽያጭ ለመጀመርም ተስማምተዋል።ከሥምምነቱ በሕዋላ እንዳዲስ የተጀመረዉን ግንኘነት ለማጠናከር የሠሜን ሱዳኑ ፕሬዝዳት ዑመር ሐሰን አል-በሽር ጁባን እንዲጎበኙ የደቡቡ አቻቸዉ ሳልቫ ኪር ያቀረቡላቸዉን ግብዣ ተቀብለዋል።የዶቸ ቬለዉ ዳንኤል ፔልስ እንዘገበዉ የሁለቱ ሱዳኖች አዲስ ወዳጅነት ነዳጅ ዘይት ከሚያፈራዉ የጋራ ጥቅም ባለፍ ዳር መዝልቁ ግን አጠያያቂ ነዉ።ነጋሽ መሐመድ ዝር ዝሩን አጠናቅሮታል።
እንዲያዉ በደፈናዉ ከደቡብ ሱዳን ነፃነት በኋላ ሁለቱን የሚያተከትከዉ ነዳጅ ነዉ።የሚያሰክነዉም ነዳጅ።ደቡብ ሱዳን ባለፈዉ ዓመት ጥር የነዳጅ ምርቷን ለማቋረጥ በርግጥ ሰበብ ነበራት።ሰሜን ሱዳንን በግዛቷ ከተዘረጋዉ የነዳጅ ቧምቧ፥ ነዳጅ ሰረቀቺኝ የሚል ዉንጀላ-አለበት።ሰበቡ ምክንያት መሆኑ ሳይረጋገጥ ግን የነዳጅ ምርቱን ለማቋረጥ መጣደፏ-እንጂ ግራዉ።
አሁን በተቃራኒዉ ፔልስ እንደሚለዉ፥ ሁለቱም ሐራራ ያናወዘዉ ሰዉ ምሱን እሲኪያገኝ እንደሚቅበዘበዘዉ የነዳጅ ምርቱ እሲከጀመር እየተጣደፉ ነዉ።በሱዳን የቀድሞዉ የዩናይትድ ስቴትስ ልዩ መልክተኛ አንድሪዉ ናትሲዮስ እንደሚሉት ሱዳኖች የነዳጅ ምርቱን ለመጀመር ቢጣደፉ አይበዛባቸዉም።ሁለቱም የዚያ «ጥቁር ፈሳሽ» ጥገኛ ናቸዉ።
«የነዳጅ ፍሰቱ ሲቆም የሁለቱንም ምጣኔ ሐብት ክፉኛ ነዉ የጎዳዉ።ሁሉቱ ቢጠላሉምና የረጅም ጊዜ የግጭት ታሪክ ቢኖራቸዉም፥ በምጣኔ ሐብቱ መስክ ካልተባበሩ ሁለቱም መንግሥታት፥ ሁለቱም ማሕበረሰቦች በጣም አሳሳቢ ድቀት ይገጥማቸዋል።»
ቁጥሩ ሁሉንም ይለዋል።የነዳጅ ዘይት ምርት ከተቋረጠ በሕዋላ የሰሜን ሱዳን ምጣኔ ሐብት ለሁለት ተከታታይ ዓመታት እያሽቆለቀለ ነዉ።በጎርጎሮሳዉያኑ ሁለት ሺሕ አስራ-ሁለት ብቻ በአስራ-አንድ ከመቶ አሽቆልቁሏል።መንግሥት ለነዳጅ ዘይት የሚያደርገዉን ድጎማ በማቋረጡ ለተቃዉሞ አደባባይ የወጣዉ ሕዝብ በተለይም ተማሪዎች ከፀጥታ አስከባሪዎች ጋር ሲጋጩ ነበር።
የደቡብ ሱዳን ደግሞ ከሰሜንዋም የባሰ ነዉ።የአዲሲቱ ሐገር፥ አዲስ መንግሥት ዘጠና በመቶ በጀቱ የሚሸፈነዉ ከነዳጅ ሽያጭ ነዉ።ነዳጅ የለም፥- ትምሕርት ቤት፥ ሐኪም ቤት፥ መንገድ ሌላም የለም።ከሁሉም በላይ ነዳጁ ናትስዮን እንደሚሉት ለሌላ ትልቅ አላማም ይፈለጋል።ለጦሩ።
ድምፅ
«በእኔ ግምት ደቡብ ሱዳን ዉስጥ ከአራት መቶ ሺሕ በላይ ደሞዝተኞች አሉ።አንድ መቶ ሺሕ ሲቢል የመንግሥት ሰራተኞች ናቸዉ።መደበኛዉ ጦር ሐይል አንድ መቶ ሐምሳ ሺሕ አባላት አሉት።አንድ መቶ ሐምሳ ሺሕ ሚሊሺያዎችም አሉ።ሚሊሺያዎቹ ድሮ ለሰሜን ሱዳን የሚያግዙ ቢሆንም ሠላሙን እንዳያኩ በሚል ደቡብ ሱዳን እንደ ተጠባባቂ ጦር ደሞዝ ይከፍላቸዋል።ደቡብ ሱዳኖች ሠላማቸዉን ለማስከበር እንደ ብልሐት ያዩት ሁሉንም ደሞዝ መክፈል ነዉ።»
ሁለቱ ሱዳኖች የነዳጅ ዘይት ምርትና ሽያጭ እንዲቀጥል ከመስማማታቸዉ በተጨማሪ በአዋሳኝ ድንበራቸዉ ላይ ከወታደራዊ እንቅስቃሴ ጥብቅ ቀጣና ለመመስረት ተስማምተዋል።ጦራቸዉን ከአዋስኝ ድንበሩ ማንሳታቸዉ ግን ሱዳናዊዉ ምሁር ማግዲ አል-ጊዙሊ እንዳሚሉት የፀጥታ ክፍተት ሊያስከትል ይችላል።
«ይሕ በጣም ረጅምና አስቸጋሪ ድንበር ነዉ።የሁለቱ ሐገራት ጦር መንቀሳቀሻ ብቻ ሳይሆን የተለያዩ አማፂ ሐይላት፥ ባንድ ወይም በሌላ ጊዜ ካንዱ ወገነዉ ሌላዉን የወጉ ሸማቂዎች መናኸሪም ጭምር ነዉ።የሁለቱ ወገኖች ስምምነት መሳካቱ የሚለካዉም ሁለቱ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሚያዟቸዉን ሐይላት በመቆጣጠር ብቃታቸዉ ነዉ።»
ደቡብ ሱዳን ስምምነቱ ካልተሳከ ሌላ አማራጭ እያማተረች ነዉ።ነዳጅ ዘይቷን በኬንያ እና በጅቡቲ ወደቦች በኩል ወደ ዉጪ ለመለካ ቧምቧ ለመዝርጋት ማቀዷ ባለፈዉ ሳምንት አስታዉቃለች።
ነጋሽ መሐመድ
አርያም ተክሌ