የህጻናት ሞት መቀነስ በኢትዮጵያ
ረቡዕ፣ ግንቦት 2 2009
የወባ በሽታ በወረርሽኝ መልክ ሊከሰት የሚችል በተለይ በሞቃታማ አካባቢወች በርካቶችን ለህልፈተ ሕይወት የሚዳርግ የኅብረተሰብ የጤና ችግር ነዉ። እንደ ዓለም አቀፉ የጤና ድርጅት ዘገባ ከጎርጎረሳዊ 2001 እስከ 2015 ዓ.ም ባለዉ ጊዜ ዉስጥ ብቻ በዚሁ በሽታ ሳቢያ የ6.8 ሚሊዮን ሰዎች ሞት ተመዝግቧል። ከነዚህም ዉስጥ ቀዳሚዉን ቁጥር የሚይዘዉ ከ 5 ዓመት እድሜ በታች ያሉና ከሰሃራ በታች በሚገኙ የአፍሪቃ ሀገራት ሕፃናት ናቸዉ ።
በኢትዮጵያ የዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ጉዳይ ፈጻሚ የሆኑት ፒተር ብሩማን ሰሞኑን ባወጡት ጽሑፍ የዩኤስ አሜሪካ መንግስት በተለያዩ የረድኤት ድርጅቶቹ አማካኝነት በወባ መከላከልና መቆጣጠር ስራ ላይ እገዛ ከሚያደርግላቸዉ 19 ከሰሃራ በታች ከሚገኙ የአፍሪቃ ሃገራት መካከል በኢትዮጵያ በበሽታዉ የሚደርሰዉ የሕፃናት ሞት ቁጥር መቀነሱ ተገልጿል። በወባ ቁጥጥር ላይ የተገኘዉ ዉጤት የሕጻናትን ሞት ከመቀነስ ባሻገር ድህነትን ለመቀነስና የትምህርት ሁኔታን ለማሻሻል ጠቀሜታዉ የጎላ መሆኑም በፅሁፉ ተመልክቷል።ጉዳዩን በተመለከተ ዶይቼ ቬለ ያነጋገራቸዉ በኢትዮጵያ የጤና ጥበቃ ሚንስቴር የአገር አቀፍ የዉባ መከላከልና መቆጣጠር አስተባባሪ ወ/ሮ ሕይወት ሰለሞን እንደተናገሩት የወባ በሽታ በሃገሪቱ ዋነኛ የጤና ችግር እንደነበረ ጠቁመዉ ባለፉት አስር ዓመታት ግን በሀገር አቀፍ ደረጃ በወረርሽኝ መልክ ካለመከሰቱ በላይ በዚሁ በሽታ ሳብያም ይደርስ የነበረዉ የሕመም እና የሞት መጠንም በእጅጉ ቀንሷል።
በኢትዮጵያ ቀደም ባሉት ዓመታት እድሜአቸዉ ከአምስት በታች ያሉ ሕጻናት ከአጠቃላይ የሞት መጠን ዉስጥ 20 በመቶዉ በወባ በሽታ የሚከሰት ሲሆን በአሁኑ ሰዓት ግን 3 በመቶ ብቻ መሆኑን አስተባባሪዋ ጨምረዉ ገልፀዋል። በአዋቂዎች ዘንድም የሞትና የሕመም መጠን 60 በመቶ የቀነሰ ሲሆን በአጠቃላይ በወባ ሳቢያ ባለፉት ዓመታት በየዓመቱ ይመዘገብ የነበረዉ እስከ 1500 የሚደርስ የሞት ቁጥር በአሁኑ ወቅት ቁጥሩ ወደ 500 ዝቅ ብሎአል። በተገኘዉ ዉጤት ሳቢያም በዓለም አቀፉ የጤና ድርጅት ዘንድ በኢትዮጵያ በከፍተኛ መጠን ሕመምና ሞት ካደርሱ 10 የሽታ ዝርዝር ዉስጥ የወባ በሽታ መሰረዙ ተብራርቷል።
በሽታዉን ለመከላከልና ለሞቆጣጠርም የዓለም አቀፉ የጤና ድርጅት ባስቀመጠዉ ስልት መሰረት የሀገሪቱ መንግስት ከአጋር የረድኤት ድርጅቶችና ከኅብረተሰቡ ጋር ባደረገዉ ርብርብ ዉጤቱ መገኘቱን ወ/ሮ ሕይወት አመልክተዋል።
በኢትዮጵያ የበሽታዉ ቁጥጥር አበረታች ነዉ ቢባልም አሁንም ድረስ በዓለም ላይ በ የ 2 ደቂቃዉ አንድ ሕጻን በወባ በሽታ ሕይወቱን እንደሚያጣ የዓለም አቀፉ የጤና ድርጅት ዘገባ ያመለክታል። በበሽታዉ ከሚደርሰዉ አጠቃላይ የሞት መጠን ዉስጥም ከሰሃራ በታች በሚገኙ የአፍሪቃ ሕጻናት ቁጥር ቀዳሚ ነዉ።
አዜብ ታደሰ
ፀሐይ ጫኔ