1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሐይማኖቶች አክራሪነት ዉጥረት በእስራኤል

ሰኞ፣ ጥቅምት 24 2007

እስራኤል ዉስጥ አንድ አክራሪ አይሁዳዊ ላይ ጥቃት ከተጣለ በኋላ በሀገሪቱ ከብሔራዊ ማንነት አኳያ ከፍተኛ ክርክርን ቀስቅሶአል። እስራኤል ዉስጥ ሐይማኖትን የለሾችና አክራሪ ሐይማኖተኞች እርቅ ላይፈፅሙ ተፋጠዉ ይገኛሉ። ዉጥረትና ክርክሩም እየጠጠረ ነዉ።

https://p.dw.com/p/1Dg8c
Jerusalem Al Aksa Moschee
ምስል picture alliance/landov

እስራኤል ዉስጥ የሁዳ ግሊክ የተባሉ አይሁዳዊ አክራሪ ሐይማኖተኛ «የሰለሞን ቤተ መቅደስ ታማኝ» "Temple Mount Faithful" በተሰኘዉ በድርጅታቸዉ ድረ-ገፅ ላይ የሰለሞን ቤተ መቅደስ በሚገኝበት ኮረብታ ላይ ከአይሁዳዉያን የፀሎት ቤት በስተቀር በሙስሊሞች ዘንድ እጅግ እንደሚከበር የሚነገርለት የዑመር ከሊፋ መስጂድ «The Dome of the Rock» እና አል አክሳ መስጂድ መካተት የለበትም የሚል አንድ ፁሑፍ ያስነብባሉ። በእሳቸዉ ጽሑፍ መሠረትም ይህ ባይሆን እንኳ የሰለሞን ቤተ መቅደስ ይገኝበት በነበረዉ ኮረብታ ላይ በሶስተኛነት የአይሁድ ቤተ ፀሎትም ሊገነባ ይችላል። ይህን ያነበቡ በርካታ ፍልስጤማዉያን የግሊክ አስተሳሰብ ተቀባይነት የሌለዉ እና እጅግ ፀብ አጫሪ ድርጊት ብለዉታል። ይህን ተከትሎም እኝህ ቀኝ አክራሪ የአይሁድ ሐይማኖት መሪ የዛሬ ሁለት ሳምንት ረቡዕ ምሽት በአንድ ፍልስጤማዊ በርካታ ጥይት ተተኩሶባቸዉ ክፉኛ ቆሰሉ። ይህ ጥቃት በተጣለ በአንድ ሰዓት ግዜ ዉስጥ ደግሞ ጥቃቱን ያደረሰዉ ፍልስጤማዊ በእስራኤል የፀጥታ አስከባሪዎች ጥይት ተገድለ።

Nahost, Israel, Palästinenser, Jerusalem, Tempelberg, Al-Aksa-Moschee, Proteste
ምስል picture-alliance/dpa

ከዚህ በኋላም በካባቢዉ ከፍተኛ ዉጥረት ነግሶአል። አካባቢዉ ላይ ከፍተኛ ግጭት ይነሳል በሚል ሥጋት የእስራኤል ባለስጣናት ባለፈዉ ሳምንት ሐሙስ ወደኮረብታዉ የሚያወስደዉን መንገድ ዘግተዉም ነበር። ፍልስጤማዊዉ ያደረሰዉ ጥቃት «ከልክ ያለፈ አሳሳቢና አወዛጋቢ ጉዳይ ነዉ » ሲሉ የእስራኤሉ የኤኮኖሚ ሚኒስትር ናፍታሊ ቤኔት ተናግረዋል። ሁኔታዉን የተከታተሉት የፍልስጤሙ ፕሬዚዳንት መሃሙድ አባስ በበኩላቸዉ ርምጃዉን « የጦርነት እወጃ ብለዉታል። የዛኑ ዕለት ማለት ሐሙስ ምሽትም የሰለሞን ቤተ-መቅደስ ይገኝበት ወደነበረዉ ተራራ የሚወስደዉ መንገድ ዳግም ተከፈተ።
የተፈፀመዉ ይህ ድርጊትም ለረጅም ግዜ ክርክር ሲደረግባቸዉ የነበሩ ሁለት ጉዳዮችን ዳግም ቆስቁሷል። አንደኛዉ ለሶስተኛ ጊዜ ከፍልስጢሞች ጋር የተካሄደዉን ጦርነት «ኢንትፋዳ» ዳግም ሊነሳ ይሆን? የሚል ሲሆን ፤ ሁለተኛዉ ደግሞ የእስራኤል የህልዉና ጥያቄ ነዉ። ይህም እስራኤል የአይሁዶች ነች፤ መሠረቷም ሐይማኖት ነዉ የሚል ነዉ። ይህ ለሃገሪቱ ማኅበረሰብና ፖለቲካ ምን ትርጉም ይሰጥ ይሆን? በእስራኤል ሐይማኖት የሌላቸዉ፤ አይሁዶች፤ አክራሪ አይሁዳዉያን ወይም የፅንፈኛ እስራኤላዉያን አብሮ የመኖር ህይወት ምን ሊመስል ይችላል?

Bildgalerie Heilige Stätten Jerusalem Al Aksa Moschee Flash-Galerie
ምስል picture-alliance/ dpa

"The Economist" በተሰኘዉ ጋዜጣ ላይ ዓምደኛ የሆኑት አቭራሃም ቡርግ ፤ በእስራኤል የሐይማኖት አክራሪነትና ፅንፈኝነት ሥር እየሰደደ እንደሄዷል የሚል ስጋታቸዉን ገልጸዋል። ለዚህም ጠብ አጫሪነት የተላበሰዉና ከዘመኑ የስልጣኔ ባህልና የፖለቲካ አስተሳሰብ ጋ የማይራመደዉ የአይሁድ የሃይማኖት ምሁራን አስተሳሰብ ተጠያቂ መሆኑን ጠቁመዋል። ከዚህም ሌላ ራሳቸዉን የአይሁድ ተሟጋች አድርገዉ የሚቆጥሩ ወገኖችም በሚከተሉት ብሔርተኝነትም የምዕራብ ዮርዳኖስ ዳርቻን በኃይልም ቢሆን የራሳቸዉ አድርገዉ ማጠቃለል ነዉ። እነዚህ ሁለቱም ቡድኖች በዚህ ርምጃቸዉ ፍሬ ያገኙ ይመስላል። የአይሁድ ምሥረታ ተብለዉ የሚጠሩትና በምዕራብ ዮርዳኖስ የሚገኙት የአይሁዳዉያን ሰፈራዎች ም እስራኤል ዉስጥ ያለዉን ዴሞክራሲዊ መንግሥት እነሱ በሚፈልጉት ሁኔታ አፍነዉ ይዘዉ እየተጠቀሙበት ይገኛሉ። በዚያም ላይ ቡድኖቹ በጎረቤት ሃገሮች ይደርሳል ተብሎ የሚፈራዉን ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ እስራኤላዉያን ላይ ያሳደረዉን ስጋትም መጠቀሚያቸዉ አርገዉታል። ላለፉት ሶስት ዓመታት ተኩል በጎረቤት ሃገራት ሳይቋረጥ በተካሄደዉ የፖለቲካ ተቃዉሞ አክራሪ ሙስሊሞች እንዲደራጁ መንገድ ፈጥሯል። ይህ ደግሞ ደግሞ በአብዛኛዉ እስራኤላዊ ላይ ትልቅ ስጋትን ፈጥሮአል።
ዩቫል ኤሊዙርና ላዉረንስ ማልኪን የተባሉ ሁለት ደራሲዎች በጎርጎረሳዊዉ 2013 ዓ,ም «የዉስጥ ጦርነት» በተሰኘ ለአንባቢያን ባቀረቡት መፅሐፋቸዉ በአክራሪነት ምክንያት ሊከሰት ስለሚችለዉ አደጋ አስጠንቅቀዋል። ደራሲዎቹ በመፅሐፋቸዉ ንዑስ ርዕሥም በእስራኤል የሚታየዉ አክራ አይሁዳዉያን ተግባር ለዴሞክራሲና ለሀገሪቱ ስጋት መሆኑን አመልክተዋል። የእስራኤላዉያኑ መጽሐፍም እስራኤል ከፍልስጤማዉያን ጋር ብቻ ሳይሆን በዉስጧም ጦርነት ዉስጥ መሆኗን ለማመልከት ሞክሯል ። ይህ የእስራኤል ዉስጣዊ ጦርነት ደግሞ በዓለማዉኑ እና በ አክራሪ አይሁዳዉያን መካከል መሆኑን አመላክተዋል።

ዓምደኛዉ ዳንኤል ጎርዲስ በኩላቸዉ ይህን አባባል አይቀበሉትም ። በመንግሥት ስር የሚገኙት የሃይማኖቱ ዋና ተጠሪዎችም ብዙዎችን በዚህ ክርክር ዉስጥ እንዳይገቡ ይከለክሉዋቸዋል። ምክንያቱም ይህ ለሐይማኖቱ እድገት የሚያመጣዉ ፋይዳ የለምና። ጎርዲስ ለዚህ ምላሽ በሰጡበት ጽሁፍም አብዛኛዉ አይሁዳዊ ሃሳብ በሚንሸራሸርበት ማኅበረሰብ ዉስጥ እስከኖረ ድረስ ዘመናዊ ና ለዘብተኛ የአይሁድ ሐይማኖት አስፈላጊ መሆኑን አመልክተዋል።

የአይሁድ የሐይማኖት ምሁርና የሰብዓዊ ጉዳይ አቀንቃኙ አሪክ አሸርማን በበኩላቸዉ ይህ ነገር ይሆናል ብለዉ አያምኑም። የእስራኤል ፖሊሲ የአክራሪዎቹን አይሁዳዉያን ሰፋሪዎች ለሚፈፅሙት ስህተት ለረጅም ጊዜ እርምት ሳያደርግበት ቆይቶአል ሲሉ ከዶቼ ቬለ ጋር ባድረገዉ ቃለ-ምልልስ ገልጸዋል።

Israel - Sperrung des Tempelbergs
ምስል Getty Images/J. Guez

« የደጉትና የኖሩትየምንፈልገዉ ነገር ሁሉን ማድረግ እንችላለን ብለዉ በሚያምኑበት ሁኔታ ዉስጥ ነዉ። ለዓመታትም የእስራኤል የፀጥታ ኃይላት ከጎናቸዉ ቆመዉላቸዋል። ከዚያ ሌላ አክራሪ አይሁዳዉያን ጽንፈኛ የሆነ ፅሑፎችን ያስነብባሉ።»

ይህ እንቅስቃሴ በተለይም በምዕራብ ዮርዳኖስ ዳርቻ ለሚኖሩ ፍልስጤማዉያንን ህይወት ሲያከብድባቸዉ ኖርዋል። እስራኤል ዉስጥም ራሱ ይህ እንቅስቃሴ ከጥቂት ጊዚያት ጀምሮ ይታያል። አክራሪ እስራኤላዉያን ፍልስጤማዉያንን ብቻ ሳይሆን የሚጎነትሉት የእስራኤል የግራ ፖለቲከኞችን፤ ጦር ሰራዊቱን ፖሊስን እንዲሁም ክርስቲያኖችንም ጭምር በመሆኑ የሚመጣዉን አደጋ ጠንቅቀዉ በማወቅ አብዛኞቹ እስራኤላዉያን እንደሚቃወሟዉ አሸርማን ገልፀዋል። እንደ አሸርማን አንድ የእስራኤላዉያን አነጋገር አለ፤

«አብዛኛዉ ማኅበረሰብ ይህን እንቅስቃሴ የወደደዉ አልመሰለኝም። ሁኔታዉ በትክክል ትኩረት ዉስጥ የገባዉ ከፍልስጤም ጎን ሆነዉ ወታደሮች ላይ ጥቃት ሲጀምሩ ነዉ። አንድ የአይሁድ አነጋገር አለ፤ «አንድ አይሁዳዊ ያልሆነ ሰዉን ሊመታ የሚችል እጅ፤ አይሁዳዊ የሆነን ለመምታት ወደኋላ እንደማይል ማመን አለብህ» ይህ ሁኔታ በአሁኑ ወቅት እስራኤል ዉስጥ ተከስቶ የምናየዉ ነዉ»

ኬርስቲን ክኒፕ / አዜብ ታደሰ

ሸዋዬ ለገሰ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ